Thursday, May 3, 2012

በሃይማኖተኝነት ሽፋን የነቀዙ «ሃይማኖተኞች»


(አንድ አድርገን ሚያዚያ 25 2004 ዓ.ም)፡- ከዛሬ ዐሥራ አምስት ዓመት በፊት በጦቢያ መጽሔት ንቅዘትን አስመልክቶ በቀረበ መጣጥፍ ውስጥ በሃይማኖተኝነት ሽፋን «ሃይማኖተኞች» ንቅዘትን እንዴት እንደሚፈጽሙ የምትገልጥ ታሪክ ተጠቅሳ አንብቤያለሁ፡፡ ታሪኩ እንዲህ ነው፡፡ በ፲፱፻፶ዎቹ መጀመሪያ ላይ የየረርና ከረዩ አውራጃ ገዢ የነበሩት ባለሥልጣን ናዝሬት ላይ የቅድስት ማርያምን ቤተ ክርስቲያን በምእመኑ መዋጮ አሠሩ፡ ፡ በወቅቱ የተደነቀውን ቤተ ክርስቲያን ጃንሆይ ከጎበኙ በኋላ ፊት ለፊት የተሠራውን ድንቅ  ኖሪያ ቤትም ተመለከቱና «ይህን ያሠራው ማነው?» ብለው ይጠይቃሉ፡፡ የአውራጃው ገዢ ምንም ዐይነት መልስ እንደማይሰጡ የተረዱት አረጋዊው ነጋድራስ ተሰማ እሸቴ «ጃንሆይ፤ ማርያም ሠራችው» ብለው አግድሞሽ መልስ ሰጡ ይባላል፡፡ ቤተ ክርስቲያን አሠሪ የሆኑ የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴ የሆኑት በገዢነታቸው ሳይሆን በሃይማኖተኝነታቸው ነው፡፡ ምእመኑም ገንዘቡን አውጥቶ በእምነት ሲሰጥ ሃይማኖተኛ ናቸው ብሎ እንጂ ገዢ ናቸው ብሎ አይደለም፡፡ የሆነው ግን ሃይማኖተኝነት ያጎናጸፋቸውን መታመን እንደምቹ አጋጣሚ በመጠቀም «ማርያም ሠራችው» ዐይነት ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ሠርተው፣ በንቅዘት የራሳቸውንም ጎጆ ቀልሰዋል፡፡


ይህ ትናንት ነው፤ ዛሬ አይደለም፡፡ ትርፋማ ንቅዘት ልንለው እንችላለን፡፡ ቢያንስ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑ ተሠርቷል፡፡ ባይሆን ዋናው ጉዳይ ለምልክት እንኳን ታይቷል፡፡ እንደዛሬው «በጠልፎ ኪሴዎች» እጅ ሙሉ በሙሉ አልወደቀም፡፡ በእርግጥ በሃይማኖት የንቅዘት ትንሽና ትልቅ ኖሮ ሳይሆን አሁን ካለው ነቀርሳዊ ንቅዘት /Malignant Corruption/ አኳያ የተሻለ ነው ለማለት ነው፡፡ ምክንያቱም እንደዘመነኞቹ ሃይማኖተኞች ምኑንም ሳይዙ፣ ምኑንም ሳይጀምሩ ለኪስ ማሰብ ብቻ አልታየም፡፡ ከመቶ ዐሥሩን ወስዶ ዘጠናውን ለሥራ የሚያውል ቢገኝ መልካም ነበር፡፡ ይህን እንኳን ማግኘት ቸግሮናል፡፡ ነገር ግን አሁን የሚታየው አዲሱ ንቅዘት ከወትሮው ሁሉ እጅግ የከፋና የተለየ ይመስለኛል፡፡ የንቅዘቱ ደረጃ እንደሻገተ እህል ሆኗል፡፡  ከሃያ ዓመታት ወዲህ ቀስ ብሎ በቤታችን ባሕል የሆነው ነቀርሳዊ ንቅዘት ጫፍ ላይ ከመድረሱ የተነሣ አንድ ጉዳይ ለማስፈጸም በበጎ ፈቃድ ሥራ ለመሥራት ወይም በቤተክርስትያን ለአገልግሎት ለመቀጠር ገና ለገና ለእንቅስቃሴው «የሚጠቅሙኝን ሹማምንት በጡት አባትነት ልያዝ» የሚለው ዕቅድ ከሁሉ ነገር ቅድሚያ ይኖረዋል፡፡ የበጎ ፈቃድ አገልግሎቱን ትተን ነቀርሳዊ በሆነ ንቅዘት በነቀዞቹ የተሾመው ሹም የወደፊት ሁኔታ ስንመለከት እርሱም ያወጣውን ገንዘብ እያሰላና ያወጣውን እስኪያወራርድ በሃይማኖተኝነት ስም ንቅዘትን እየፈጸመ «ሃይማኖተኛ» መስሎ ይኖራል፡፡ የንቅዘታዊ ሙስና ጥቅም በሹማምንት ደም ሥር ውስጥ እንደአስፈላጊ ቅድመ ሁኔታ ይታያል፡፡ ጉቦን፣ ሙዳይ ምጽዋት ማድፋፋትን፣ የሹም ዘረፋንና የመሳሰለውን እንደ ባሕል ይዘው የቀጠሉ ይመስላሉ፡፡

በንቅዘት የተዘፈቁና ሃይማኖታዊ ብኩርናቸውን ለከበርቴም ሆነ ለመንግሥት ሹም እንዲሁም ለአፅራረ ሃይማኖት ጭምር መሸጥን የያዙ የትናንትም ሆነ የዛሬ /በሃይማኖተኝነት ስም የነቀዙ ሃይማኖተኞች/ ሹሞች እውነትን ለመናገር፣ እውነትን ለመወሰንና ትክክለኛ ዳኝነትን ለመስጠት የሞራል የበላይነት አይኖራቸውም፤ ኖሯቸውም አያውቅም፤ ሊኖራቸውም አይችልም፡፡ በቅዱስ ፓትርያርኩ ዙሪያ ተሰልፎና  ተጠግቶ አብረዋቸው ከቤተ ክህነቱም  ማዕድ እንደአሻቸው ሲጐርሱ የነበሩትን ሁሉ ማሰብ ይቻላል፡፡

ኬጂቢያዊ አካሔድ?
የቀድሞዋ ሶቪየት ኅብረት የስለላ ድርጅት የሆነው ኬጂቢ አንድን አገር ለመቆጣጠር በሚፈልግበት ጊዜ የሚጠቀምባቸው «ፍቱን»፤ ዳሩ ግን መልካም ያልሆኑ ስልቶች ነበሩት፡፡ የመጀመሪያው በልዩ የወሲብ መረብ ሰዎችን የማጥመድ ሥልጠና በተሰጣቸው ሴቶችና ወንዶች አማካኝነት የዚያን አገር ባለሥልጣናት ያጠምዳል፡፡ ወሲቡ ሲፈጸም እያንዳንዱ ቅብጠት፣ እያንዳንዱን የአፈጻጸም ሁኔታ በቪዲዮና ፎቶ ግራፍ ይቀርጻል፡፡ እነዚያን ፎቶ ግራፎችና የቪዲዮ ፊልሞችወንዶች ከሆኑ ለሚስቶቻቸውና፤ ሴቶችም ከሆኑ ለባሎቻቸው ለመላክና ለመንግሥቶቻቸውም ለማሳወቅ ያስፈራራሉ፡፡ ራሻዎች በሦስተኛው ዓለም ላይ የርእዮተ ዓለም ወረራና የምጣኔ ሀብት ብዝበዛ ሲያካሒዱ የኖሩት በዚህ ርካሽ ግን «ፍቱን» በሆነ ስልት ነው፡፡ አብዛኛዎቹን የተጠጉአቸውን አገሮች ሹማምንት ደግሞ የአካልም የመንፈስም ምርኮኞች አድርገዋቸው ኖረዋል፡፡ ስለዚህም ጉዳይ ብዙ የስለላ መጻሕፍት ተጽፎአል፡፡ ብዙ ብዙ ዓለም አቀፍ ጋዜጦች መጽሔቶች ወጥተዋል፡

እንዲህ ዓይነቱን ርካሽ ኬጂቢያዊ ስልት  የእኛዎቹ ሽፍቶች ወይም «የጨለማው ሲኖዶስ» አባላት የሚፈልጉትን ውሳኔ ለማስወሰን ሲጠቀሙበት በተደጋጋሚ ታይተዋል፡፡ በተለይ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት የሚወሰኑት ውሳኔ ቤተ ክርስቲያኒቱን ጠቅሞ የእነርሱን ምጣኔ ሀብታዊና አስተዳደራዊ ተጠቃሚነታቸውን የሚጎዳ ሆነው ከአገኙት ተጽዕኖ ፈጣሪ ወደ ሆኑ አባቶች ስልክ በመደወል ማስፈራራት ይጀምራሉ፡፡ «በሚወሰነው ውሳኔ የሚስማሙ ከሆነ እርሱን በተመለከተ የያዝነውን ፎቶ ግራፍና ፊልም ለምእመኑ ይፋ እናደርጋለን አርፈው ይቀመጡ»እያሉ ውሳኔ ለማስቀየር የተሞከሩትን ሙከራዎች ማስታወስ በቂ ነው፡፡

ነቀርሳዊ ንቅዘት ወይስ «ነጭ ለባሽነት»?
በእርግጠኝነት ግን አንድ ነገር መናገር እችላለሁ፡፡ እኚህ መበለት በሃይማኖተኝነት ስም የነቀዙ «ሃይማኖተኛ» ሹማምንትን ተጠግተው በንቅዘት መዘፈቃቸውን ብቻ ሳይሆን በቤተ ክህነቱ ውስጥ ለሚታየው ለኦርቶዶክሳዊ ሞራል መላሸቅ አስተዋፅኦ እያደረጉ መሆናቸውን ፡፡ በእኚህ መበለት ዙሪያ ያሉ ሰዎችን ስንመለከት ቤተ ክርስቲያኒቱን ለማጥፋት በአቋም የተነሡ፤ አሊያም ደግሞ በሥልጣን ማጋጣነታቸው ሊወገዙ የሚገባቸው የመንግሥት ሹማምንት ናቸው፡፡ እናም ሴትየዋ ከምጣኔ ሀብታዊ ተጠቃሚነታቸው ባሻገር በሃይማኖተኝነት ሽፋን ቤተክርስቲያኒቱን የማፍረስ «ነጭ ለባሽነት» ሚና ሊኖራቸው ይችላል፡፡ ከተዘፈቁበት ነቀርሳዊ ንቅዘት በላይ «ነጭ ለባሽነት» ሚናቸው እስከምን ነው? የሚለው ጥያቄ መመለስ እንዳለበት ጽኑ እምነቴ ነው፡፡ ሚናቸው ኢኮኖሚያዊ ድልቦችን በማደለብ ብቻ የተወሰነ አይመስለኝምና፡፡ ይሁንና ቤተክርስቲያኒቱ ከተዘፈቀችበት ችግር፣ ከወደቀችበት አዘቅት ሳትወጣና ሳታገግም እኚህም መበለት ሆኑ ወቅታዊ ገዢዎቿ ለሕዝበ እሥራኤል ከወረደው መና የበለጠ በንቅዘት ከብረው ታይተዋል፡፡

የግፉ ጽዋ ሞልቷል!
ባለፉት ሃያ ዓመታት በሃይማኖተኝነት ስም የነቀዙ «ሃይማኖተኞች» በቤተክርስቲያኒቱ ላይ ጥላቸውን ጥለውባታል፤ አሻራቸውን አሳርፈውባታል፡፡ በበጐም ሆነ በክፉ በትውልድና በታሪክ ፊት ምስክርነት ይቆያቸዋል፤ ፍርድ ይጠብቃቸዋል፡፡ እምነት አጥተው በሠሩበት ሳይከበሩና ሳይወደዱ በሥልጣን በቆዩበት ዘመን ላደረሱት ግፍና ለፈጠሩት ትርምስ እስካሁን የተፈጠረውን ጥላቻ በአይነት እንደመመለስ ብንወስድ እንኳን ውርደቱ ገና ነው፡፡ስለ እነዚሁ መሪዎቻችን ክብር ከእኔ ይልቅ ራሳቸውን ይጭነቃቸው፡፡ ስለ ቤተክርስቲያኔ ክብር ግን እጨነቃለሁ፡፡ የመንግሥት ሹም ወይም ከበርቴ በመሆኑ ብቻ እንደ «ጌታ» በሃይማኖት አባቶቼ ፊት የመታየቱ ጉዳይ ያበሳጨኛል፡፡ በፍርሃት ሲርዱ ከመመልከት በላይ አንገት መድፋት የለም፡፡ የቤተክርስቲያኒቱ ልዕልና መደፈር አንድ ምልክት ይህ ነው፡፡
ይህ ደግሞ ቤተክርስቲያኒቱ የምትመራው ሕይወት ረጋ ያለ የሚመስል ዳሩ ግን በእሳተ ገሞራ ላይ የተቀመጠች ከተማ ሕይወት ነው፡፡ ምክንያቱም በዛሬው ዘመን ያለው መቆርቆዝ፣ በመሪዎቻችን አማካኝነት የቤተክርስቲያኒቱ መዋረድ፣ የቤተክርስቲያን ጥቅም የሚባል ነገር ትርጉም ማጣት፣ የቤተ ክርስቲያን ሀብት ወደ ጥቂት ሰዎች ኪስ የመግባቱ ሒደት አለመገታት፣ የቤተክርስቲያን አንድነትና ሰላም ዋስትና ማጣት ይችን ቤተክርስቲያን ለአዲስ ዓይነት መከራ የሚያዘጋጅ ይመስለኛል፡፡ ግፍ ሲጠራቀም፣ ጊዜው ሲደርስ በቀድሞው መንገድ መቀጠል አይቻልም፡፡

ፕትርክናው በቀረብን ያሰኛል!
በታሪክ የመጀመሪያዋ ገናናዋ ቤተክርስቲያን ሕልምና ዓላማዎች ያጣች ትመስላለች፡፡ የጀግኖች እናት፣ የሰማዕታት ቤት ቤተክርስቲያን ዛሬ የብዙሃን ሰብሳቢነትና ተንከባካቢነት አልተሰማትም፡፡ ካህናቱ፣ ምእመኑና ገዳማቱ ያለባቸው መከራ መጪውን ጊዜ ይጠቁማሉ፡፡ ክርስቶስ «ምልክቱን ከበለስ ፍሬ ታውቁታላችሁ» ነበር ያለው፡፡ የቤተክርስቲያኒተን መጪ ጊዜ ከወቅቱ ጥላ ለማወቅ ይቻላል፡፡ የሚቀጥለው ጉዞ ካለፈው የሚከብድና የሚያስጨንቅ መሆኑንም እገምታለሁ፡፡ እንደ አሁኑ ያለ ክፉ ዘመነ ፕትርክና ይመጣል ብለን ተስፋ መቁረጥ ባይገባንም የአስተዳደሩን ንቅዘት ስንመለከት ምንም ጊዜ የሚያስመኝ አይደለም፡፡ በሃይማኖተኝነት ስም ሙዳይ ምጽዋት ላሽና ጀርባ ነካሽ «ሃይማኖተኛ» እስካሁን አላጣንም፡፡ ከአንዳንድ ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በርካሽ ጥቅም በመዛመድ በአገልግሎታቸው ከማያውቁት ሀገረ ስብከት ወርኃዊ ደመወዝ የሚሰፈረላቸውን መምህራን ባዮችንም አላጣንም፡፡ ሰዎቹ አእምሮ ውስጥ ዘወትር ያለውም ላሽነትና ነካሽነት ነው፡፡ ከትምህርት ትምህርት፣ ከልምድ ልምድ፣ ከሕዝባዊነት ሕዝባዊነት፣ ከሃይማኖት ሃይማኖት የሌላቸው ግለሰቦች ዐውደ ምሕረቱን በገፍ ሲይዙ ምን ያህል ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደ ኋላ እንደሚጎትቱ ፣ ምን ያህልም አንድነቷንና የታሪክ ቅሪቷን እንደሚያፈራርሱ ለመረዳት አያዳግትም፡፡

በዚህ ረገድ ሲታይ ቤተክርስቲያኒቱ ሁነኛ አመራር አጥታ ቆይታለች ብቻ አይባልም፡፡አጥፊ አገዛዝ ሥር ወድቃ ነበር ማለት ያስደፍራል፡፡ የአስተዳደራችን አካሔድ መለወጥና ከነቀርሳዊ ንቅዘት ሥርዐት መውጣት አለበት፡፡ ለዚህ ደግሞ ሥልጣንን የቤተክርስቲያኒቱ ቀኖና በሚፈቅደው አግባብ አግኝቶ ፣ ደረቱን ነፍቶ፣ ራሱን ቀና አድርጎ የሕዝብ አገልጋይነት ሓላፊነትን የሚረከብ ፣ በገዳማዊ ሕይወቱ የተፈተነ መሪ ያሻታል፡፡ ዛሬ ምእመኑ በሙሉ የተሳፈረበትን የአመራር መርከብም እናስብ፡፡ በሃይማኖተኝነት ስም የነቀዙ «ሃይማኖተኞች» ያሰናከሉት መርከብ ነው፡፡በሰፊው ውቅያኖስ ላይ እንደልብ ሊንሳፈፍ አይችልም፡፡ አውሎ ነፋሱ፣ ወጀቡና የባሕሩ ቁጣ ጠንካራ መርከብ ይፈልጋል፡፡ ስለዚህ ይህ የአምስተኛው ዘመነ ፕትርክና መርከብ የተሰናከለ በመሆኑ መልሕቁን ጥሎ መቆም አለበት፡፡ የምእመኑና የሊቃውንቱ ዕድል፣ የቤተክርስቲያን አመራር መጫወቻ ስላልሆነ ከእንግዲህ ንቅዘት ያላገኛቸው ፣ብቃት ያላቸውና ኦርቶዶክሳዊ ፍቅራቸው የተፈተነ ሰዎች ይሞክሩት፡፡

የርእሱ ሚና በአንድ ወታደር ትከሻ ላይ የወደቀው ሓላፊነት ዐይነት ነው፡፡ ቤተክርስቲያኒቱን መጠበቅ፣ የቤተክርስቲያኒቱን ሊቃውንትና ምእመናን አንድነትና እኩልነት መንከባከብ፣ አስተምህሮዋንና ታሪካዊ ቅርሶችዋን አስከብሮ ማቆየትና ግንባታ ነው፡፡ ይህ ሁሉ ከአባቶቻችን ቅዱሳንና ከእናቶቻችን ቅዱሳት የወረስነው ነው፡፡ ይህንን ስናገናዝበው ደግሞ በጊዜና በሁኔታዎች አንጻር የቅዱስ ሲኖዶስ ሞግዚትነትና ውክልና፤ እምነትና ሓላፊነት ዛሬ የተቀበለ የአስተዳደር ሥርዓት የለም፡፡

አብሮ መሥራት፣ አብሮ መሞት
ወቅቱ የሚጠይቀው የሰለጠነ አስተሳሰብ በሕሊናዊ ሁኔታው አለ፡፡ እንዲህ ዐይነት ሥርዐት ነገ በሃይማኖተኝነት ስም ከነቀዘ «ሃይማኖተኛ» ወይም ለገዳማዊ ሕይወት ዋጋ ከሌለው ከሚመ ይልቅ ከሃይማኖተኝነት መርሕ ውስጥ የሚከሰትና በጊዜ ክንፍ ውስጥ የሚገኝ ቢሆን ይመረጣል፡፡ እስከመቼ አስተዳደራችን የነቀዘ? የላዕላይና የታህታይ መዋቅር ሹማምንቶቻችን እምነት የዱር ሆኖ ይቀጥላል? የአመራር አስተሳሰብ በንቅዘት ሲሻክርና ቤተክህነታዊ ሽብር ሲበዛበት ወደ ሕዝባዊ አመፅ፣ ወደ አባታዊ ክብር መንሣት መፍትሔነትና የጉልበት ተግባር ይዛወራልና፡፡ ከዚህ አኳያ በሃይማኖተኝነት ስም የነቀዘው አስተዳደርና አስተዳደሩን የከበቡት ነቀዞች ወይም የንቅዘቱ አጫዋችና አልቢተር ደስተኛ ተመልካች ሆነው ይህን ሁሉ ጨዋታ በድል አድራጊነት መንፈስ ይመለከቱታል፡፡ አንዱ ደስታቸው ለእኔ እንደታየኝ ፣ ለሁላችሁም እንደሚታያችሁ እነዚህን ነቀዞች በቃችሁ ለማለት ከእነርሱ ፈቃድ አስፈልጓል የሚለው አዝማሚያ ነው፡፡ ይህንን በአግባቡ የተረዳነው አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም የምንጋራቸውን ግቦች፣ የምናከብራቸውን ኦርቶዶክሳዊ እሴቶች ተገንዝበን ለተፈጻሚነታቸው ፈቃደኞች መሆናችንን እስካሁን አላረጋገጥንም፡፡ ማረጋገጫው መንገድ ደግሞ አብሮ መሰለፍ፣ አብሮ መሥራት አብሮ መሞት በሆነ ነበር፡፡

አንድ ኦርቶዶክሳዊ አጀንዳ!
ለማንኛውም ግን በእኛዋ ቤተክርስቲያን ነባራዊ ሁኔታ የነቀዘውን አስተዳደር በመቃወም ጉራ ውስጥ ያሉት ቡድኖች እርስ በርስ የሚጨራረሱበት አንዳች ምክንያት የለም፡፡ የቤተክርስቲያናችን ወቅታዊ ሁኔታ፣ የሊቃውንቱና የምእመኑ የችግር ሰለባ መሆን፣ የቤተ ክህነቱ ፖለቲካ ትራጀዲነት የነቀዘውን አስተዳደርንና ሰዎቹን የተቃወሙትን የሚያስተባብር እንጂ የሚለያይ መሆን አልነበረበትም፡፡ የአባት ገዳይ ከሆነ ደመኛ ጠላት ጋርም ያስታርቃል፡፡
በአንድ ጀንበር ባልታሰበ አኳኊን በንቅዘት የበሰበሰው አስተዳደር ሚሊዮን ጠላት ሲያፈራ ያንን ኃይል አስተባብሮ ወደ ድል መትመም ሲቻል በአመራር ድህነትና በራስ መውደድ ምክንያት በአንዲት አጥንት ላይ እንደሚራኮቱ ውሾች መሆንምን ይባላል?

የቤተ ክህነቱን ፖለቲካ አለማወቅ?
ትግሉ የሚጠይቀውን መሥዋዕትነትና ዝግጅት አለመረዳት? ወይስ ሁሉም ፡፡ስለዚህ በእኔ ትዝብት ኦርቶዶክሳውያን የቤተ ክህነቱን የፖለቲካ ጨዋታ ሕግጋት አናውቅም፡፡ የተነሣንለትንና ጨዋታው የሚጠይቀውን ውስብስብ ጉዳይ ሁሉ አናውቅም፡ ፡እርስ በርስ መከባበር የለም፡፡ «ለኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያንና ለኦርቶዶክሳውያን የምናውቅላቸው እኛ ወይም እኔ ብቻ ነኝ» የሚል በሽታ አሁንም አለብን፡፡ ይች ቤተክርስቲያን የጋራችን መሆኗን እስካሁን ያለመንን ብዙዎች ነን፡፡ አሁን እሴታችን የተለያየ ፣ አቅጣጫችንም የተለያየ የሆነ ይመስላል፡፡ በዚህም በዚያም በየማኅበራቱ ውስጥ ብንገባም የቤተ ክህነቱ ፖለቲካ አልገባንም፡፡ እንዲያው በደፈናው የልምድ አዋላጆች ነን ፤ ከአሳባዊ መሪነት ይልቅ ፤ ይቺን ነጥብ ለመቋጠር እፈልጋለሁ፡፡ ለመሆኑ በሰፊውና ጥልቁ ውቅያኖስ ውስጥ ገብቶ በአንድ እጅ ለመዋኘት የሚፈልግ ጤነኛ ሰው አለ እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ልዩ ልዩ መለያልይ (limbs) ሰጥቶአቸዋል፡፡ እኒህንም ለመዋኘት፣ለመኖርና ለመሥራት ሊጠቀሙበቸው ይገባቸዋል፡፡ ሁሉም በየትግሉ በየማኅበራቱ ብቻ ቢሠራ ትልቁን ውቅያኖስ በአንድ እጅ መቅዘፍ አይሆንም? ከአንድ አንጋፋ ማኅበር አንጃ ከሚወጣና ጉልበት ፣ ዕውቀትና ልምድ ከሚበታተን በውስጥ ሆኖ ማኅበራቱን መለወጥ አይቻልም ነበር? ኃይላችንን አጠናክረን ወደማይቀረው ድል ራሳችን ቀና አድርገን ለመራመድ የምንችለው አጽራረ ቤተ ክርስቲያን ዘረፋቸው ብዙ ቢሆንም «የስበት ማዕከሉ» አንድ ብቻ መሆኑን ስናረጋግጥና ኦርቶዶክሳዊው ኃይል ሁሉ መሰባሰቡን ያለማወላወል ስንረዳ ነው፡፡
ኦርቶዶክሳዊ ሥልጣን የሚመጣው ዛሬ በቤተክርስቲያኒቱ ላይ በአምባገነንነት የተሰየሙት እንደሚያምኑት በንቅዘት በሚመጣ ኃይል መሆኑን በማመንና ያንን በመጠበቅ ጊዜያቸውን የሚያሳልፉ አሉ፡፡ ንግርት የሚጠብቁም አልታጡም፡፡ ፊደል ቆጠርን የምንለውም ተራ ተረት ውስጥ ገብተን በሃይማኖተኝነት ስም የነቀዙ «ሃይማኖተኞችን» ከቤተ መቅደሱ ለማስወገድ አንካሣ መሪ ስንጠብቅም ቆይተን ይሆናል፡፡ እንዲህ ዐይነቱን መሪ በየመስኮቱ ስንመለከት የአእምሮና የመንፈስ አንካሳነት ያላቸውን መታደላችንን ደግሞ ረስተነዋል፡፡

ጥናት፣ ጥናት፣ ቅንጅት፣ ቅንጅት
ከሁሉ በፊት የነቀዘውን የቤተ ክህነቱን አስተዳደር እንቃወማለን በሚለው ጐራ መገኘት ያለበት አንድነትና አብሮ መሥራት መቅደምይኖርበታል፡፡ ስለ «አርቴፊሺያል አንድነት»አንነጋገር፡፡ ትከሻ ለትከሻ እየተጋጩ የልብ ግንኙነቱየደቡብና የሰሜን ዋልታ ርቀት የሆነበትንም ጉዳይእናንሣ፡፡ ከእግዚአብሔር ርቆ የቤተ ክርስቲያንአጸድን ማዘውተርን እንርሳው፡፡ ዓላማና መንፈሳዊእሴት የሚያቆራኘው ምእመንና ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን አብረው በመሥራት እነዚህን ባሕርያት ከፍ አድርገው ማሳየት አለባቸው፡፡ ዘለዓለም ምራቅ የማያስውጥ የሌለን ሆነን መቅረት የለብንም፡፡ምሁራንና ቤተ ክርስቲያን ወዳድ ወገኖችም የወቅቱን የቤተክርስቲያኒቱን ሁኔታ በተለይ ቤተክርስቲያን ተረካቢ ለሆነው ለወጣቱ ትውልድ በማስተማርና ምእመኑን ለአማናዊ መነቃቃት በማዘጋጀቱ ሥራ የተለያዩ ጥናታዊ ጽሑፎችንና ወቅታዋ ጉዳዮችን የሚገልፁ መጣጥፎችን በመስጠት የመርዳት ሓላፊነትና ድርሻ ከፍተኛ ነው፡፡

ኦርቶዶክሳዊ ጥቅምን፣ የቤተ ክርስቲያን አንድነትን፣ የአስተምህሮ ጥበቃን ማዕከል አድርገን ከታገልን በአንድነትና በኅብረት በቤተክህነቱ የተንሰራፋውን የንቅዘት ባርነት ቀንበርን ለመስበርና አማናዊውን ሃይማኖተኝነትን አንዲት በሆነች ቤተ ክርስቲያናችን ለማስፈን የሚያግደን ኃይል አይኖርም፡፡ ይህን የምለው መልካም ካለሆኑት ሃይማኖተኛ ሹማምንት የኃይል አሰላለፍና ከቤተክርስቲያኒቱ ወቅታዊ ሁኔታዊ ግንዛቤ አንጻር ብቻ ነው፡፡ ስንነጋገርበት እንደ ባጀነው የቤተ ክህነቱ አስተዳደር ሕመምተኛ መሆኑን ተማምነናል፡፡ ሕክምናውም «አንተ የንቅዘት ርኩስ መንፈስ ልቀቀው ብዬሃለሁ፡፡ ቤተክህነቱን ለቅቀህ ሒድ» ከሚለው ጸሎት ዘዘወትር ባሻገር ሁሉን አቀፍ ትግል ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን፣ ቀናኢ ምእመናንና ልዩ ልዩ ማኅበራት ስልታዊ በሆነ መንገድ ለመቀናጀትና ውጤት የሚያስገኝ አስተዳደር ለማስፈን ከአሁኑ ጀምሮ መንቀሳቀስ ይኖርባቸዋል፡፡ መገፋትን ከመኖር ጋር የመላመድ ባሕሉ መሠበር አለበት፡፡ እዬዬን አርግዞ መቆዘሙ መቆም አለበት፡፡ ተናግሮ ሳይሆን በነቀዘው አስተዳደር ላይ ክፉ አስበሃል እባላለሁ በሚል መጨነቅ መቆም አለበት፡፡ በአጭሩ ቤተክርስቲያኒቱ የሐቀኛ ልጆችዋ እንድትሆን መታገል ይገባል፡፡ ከዚህ አንጻር እነዚህ ኃይሎች ብዙ ሥራ ይጠብቃቸዋል፡፡


ከታደሰ ወርቁ
የአንድ አድርገን ሀሳብ
በአሁኑ ሰዓት በተለያየ ብሎግ ቤተክርስትያኒቱን የሚቃወሙ አስተምህሮዋን የሚሸረሽሩ ብሎጎች በእምነት እና በፍቅረ ነዋይ የነቀዙት ሰዎች እስትናፋቸው መሆናቸውን እንረዳ ፤ ጥቅማቸው የቀረባቸው ወይም ገና ለገና ይቀርብናል ብለው የሚያስቡ ሰዎች ስብስብ ናቸው ፤ ኦርቶዶክሶችም አይደሉም ፤ ስርዓተ ቤተክርስትያንን ቢያውቁም የቆሙለት አላማ ሌላ ስለሆነ ደግ ነገር ከብሎጎቻቸው ማንበብ አይቻልም ፤ እኛስ የማይጠቅመንን ነገር በማንበብ ያለንን እምነት ለምን እንሸረሽራልን ? ስለ ጻድቃን ሰማዕታት አፋቸውን ከፍተው እየተሳደቡ ለምንስ የእነርሱን ነብሎግ እንጎበኛለን ? መጥፎ ነገርን ውስጣችን ለማስቀረት ለምን እጥራለን ፤ ብዙ ጊዜ ስለ ‹‹አንድ አድርገን›› ይጽፋሉ እኛ ግን መጻፋቸውን እንኳን የምንሰማው ከሰው ነው ፤ ይስደቡን አይለጠፍብም፤ አላማችን ስለማይገናኝ ስለስድባቸውም መልስ መስጠት አንፈልግም ፤ እነርሱ በዚህ በኩል ይሳደባሉ መንግስት በዚያ በኩል ብሎግ ይዘጋል ፤ ሁሉም ግን እኛን የነቀዙትን ሰዎች ለመቃወም ብርታት ይሰጠናል ፤ ለምንስ ለማይረባ ጽሁፋቸው መልስ በመስጠት ጊዜያችንን እናጠፋለን ፤ የቤተክርስትያኒቱ ፈተና ስለሚበልጥብን እዚያ ላይ አተኩረን እንሰራለን ፤ ቅድሚያ የሚሰጣቸው በርካታ ነገሮች ከፊታችን አሉ ፤ መረጃዎችም በእጃችን ላይ አሉ እርሱን እናንተ ጋር ለማድረስ እንሰራለን ፡፡ የነቀዙ ሃይማኖተኖችን ከነ ስራዎቻቸው እናንተው ዘንድ እናደርሳለን ፡፡

10 comments:

  1. bravooooooo andadirgen..ewuketinaa migbar..endih newuuuu

    ReplyDelete
  2. Excellent Job Andadrgen

    ሁሉም ግን እኛን የነቀዙትን ሰዎች ለመቃወም ብርታት ይሰጠናል ፤ ለምንስ ለማይረባ ጽሁፋቸው መልስ በመስጠት ጊዜያችንን እናጠፋለን ፤ የቤተክርስትያኒቱ ፈተና ስለሚበልጥብን እዚያ ላይ አተኩረን እንሰራለን ፤ ቅድሚያ የሚሰጣቸው በርካታ ነገሮች ከፊታችን አሉ ፤ መረጃዎችም በእጃችን ላይ አሉ እርሱን እናንተ ጋር ለማድረስ እንሰራለን ፡፡ የነቀዙ ሃይማኖተኖችን ከነ ስራዎቻቸው እናንተው ዘንድ እናደርሳለን ፡፡

    ReplyDelete
  3. Really, an interesting idea which needs our concerted action.
    May God Bless Ethiopia and our religion Tewahedo Orthodox.
    Thanks for the writer and the blogger.

    ReplyDelete
  4. The number of Christian is decreasing while that of muslims is increasing in ETH. The government understood the threat of islamisation for its power and now standing against them. reformists and money minded fellows who are trying to kill our church will also understand about everything late after devastating our mother church. Our church is standing on rocks and our saviour will protect it despite our wickedness. Enante gin bertu andadirgenoch.

    ReplyDelete
  5. መገፋትን ከመኖር ጋር የመላመድ ባሕሉ መሠበር አለበት፡፡ እዬዬን አርግዞ መቆዘሙ መቆም አለበት፡፡ ተናግሮ ሳይሆን በነቀዘው አስተዳደር ላይ ክፉ አስበሃል እባላለሁ በሚል መጨነቅ መቆም አለበት፡፡ በአጭሩ ቤተክርስቲያኒቱ የሐቀኛ ልጆችዋ እንድትሆን መታገል ይገባል፡፡ ከዚህ አንጻር እነዚህ ኃይሎች ብዙ ሥራ ይጠብቃቸዋል፡፡

    ReplyDelete
  6. egziabher yibarkachihu

    ReplyDelete
  7. yale dem bete christian atikomim. silezih rasachinin le semaitinet mazegajet new. lemin eniferalen. 8,000 geberiewoch bezemen Sisinos yemotut leHaymanot meselegn. lemin feran. ahunim ende Semen Gonder gebere eninesa, be Wenchif mengistin maniberkek yichalal.please, let us raise. werie ayitekimim, kefirihat mewutat alebin.

    ReplyDelete
  8. And Adirgen tesasitachhal elalehu yesewochin guday eyawru sewn kemasadedi yemibeltsew lemenafikanu biloggch beki yehone mels eyazegagu mastemar new biye amnalehu tewahedo hayimanote yemilewn sew menafikan eyesheresherut kefi yale fetena lay hono tebaber malet min Malet New? Ahun Yeminayew Neger Papasu -Menkusew- Kahinu -Diyakonu-Sebakiw-Zemariw hulum asmesay tebiloal ahun mehon yalebet melkam neger eymezegebu mastemar new bertu

    ReplyDelete
  9. The article writer was good. But andadregen is full of hate. How ever the
    article is exactly written for mk. From top to botoom, is talking is how mk
    is distrowing our Tewahedo orthodox Church, in the name of the Orthodox.

    That is reliy bad to try to cheet God. Never, never you can ....... look your self mk first, before blaming any body.

    ReplyDelete