Friday, May 24, 2013

የ‹‹አጥማቂው› መምህር ግርማ ስራ በቤተክርስቲያን ስርዓት እይታ



(አንድ አድርገን ግንቦት 16 2005 ዓ.ም)፡- መምህር ግርማ የማጥመቅ ስራቸውን ከጀመሩ ዓመታት ማስቆጠራቸው  ይታወቃል ፤ በየሄዱበት ብዙ ተከታይ ከማፍራታቸው በተጨማሪም ብዙ ነቃፊ ፤ ትምህርታቸውም ይሁን የማጥመቅ ስርአታቸው ከቤተክርስቲያን ውጪ ነው የሚሉ ሰዎች አልታጡም ፤ ‹‹አጥማቂው›› በተለይ በቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን ሲያካሂዱት የነበረው ተግባር 17 ክፍል ያለው ፊልም ወደ ሲዲ በመለወጥ ለህዝበ ክርስቲያኑ ለገበያ አቅርበዋል፡፡ ምዕመኑ ቤተክርስቲያን ሄዶ ከማስቀደስ ይልቅ የእሳቸውን ሲዲ ከፍቶ ቤቱ ቁጭ ብሎ ‹‹ይገርማል›› እያለ የሚያይበት ጊዜም ነበር ፤ ከሀገር ውጪ ያሉ አብያተክርስቲያናት ‹‹አጥማቂውን›› አምጡልን በማለት የቤተክርስቲያኖቻቸው አስተዳዳሪዎች ያስጨነቁበት ጊዜም ነበር ፤ በአሁኑ ሰዓት በሀገር ውስጥም ሆነ ከሀገር ውጪ በብዙ ምዕመናን ቤት የ‹አጥማቂው›› ፊልሞች ይገኛሉ፡፡ ከቀናት በፊት የቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተክርስቲያን ካገዳቸው በኋላ ቤተክህነቱ እንዲህ በማለት ድጋፉን ገልጾላቸዋል ‹‹መምህር ግርማ ወንድሙ በደብረ ሰላም ቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን ቅጥር ግቢ ውስጥ በሕገ ወጥ መንገድ የሚፈጽሙት ሕገ ወጥ የማጥመቅ ሥርዐትና የወንጌል አገልግሎት መኾኑን እየገለጽን የእምነታችን ተከታይ ሕዝበ ክርስቲያኑ ከዚህ እግድ ጋራ በተያያዘ የጸጥታ ችግር እንዳይገጥመው የሰበካ ጉባኤ /ቤት ጥብቅ ክትትል በማድረግ ውሳኔውን ተግባራዊ እንዲያደርግ እያሳሰብን የሚመለከታቸው የመንግሥት የጸጥታ አካላትም የቤተ ክርስቲያኒቱን ውሳኔ ተግባራዊ በማድረግ ረገድ አስፈላጊው ትብብር እንዲያደርጉልን በአክብሮት እንጠይቃለን፡፡››
 
ይህ በእንዲህ እያለ የ‹አጥማቂው›› የሲዲ ስራዎች በቤተክርስቲያ እይታ ምን ይመስላሉ ? እውን ትምህርታቸውም ሆነ የአጥምቆት ስርዓታቸው የቤተክርስቲያን ስርዓትን የተከተለ ነውን? ምዕመኑ ለምን አላስፈላጊ ንትርክ ውስጥ በ‹‹አጥማቂው›› አማካኝነት ሊገባ ቻለ? ‹‹መምህር›› ግርማስ ማን ናቸው ? እና በ‹‹አጥማቂው›› ዙሪያ የሚነሱ ጉዳዮችን ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ባሉበት ግንቦት 20 2005 ዓ.ም ከጠዋቱ 3፡00 ጀምሮ በአራት ኪሎ ግቢ ገብርኤል አዳራሽ በምዕመናን ታላቅ መልስ የመስጠት ጉባኤ ተዘጋጅቷል፡፡ በ‹‹አጥማቂው›› ግራ ለገባችሁ ፤ ግራ ለተጋባችሁ ፤ ግራም ያጋባችሁ ሁላችሁም በጉባኤው ላይ ተጋብዛችኋል፡፡

ጥንተ አብሶ እና ተዋሕዶ




በሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው

(አንድ አድርገን ግንቦት 16 2005 ዓ.ም)፡- በነገረ ሃይማኖት ውስጥ እስከ አሁን ድረስ ሆኖ እንዳየነው፣ እንደሚያታወቀው፣ እየሆነም እንደምናየው ከባለቤቱ ከመድኀኔዓለም ክርስቶስ አንሥቶ መትሕተ ፈጣሪ መልዕልተ ፍጡራን በሆነችው በቅድስት ድንግል ጽዮን ማርያም፣ በቅዱሳን መላእክት፣ በአበው ጻድቃን ሰማዕታት /ቅዱሳን/ በሁሉም ላይ ክሕደት ወይም ኑፋቄ ያልተነሣበት ማንም የለም፡፡ በወላዲተ አምላክ ላይም ከሚነሡ ኑፋቄዎች ሁሉ የከፋውና ከባዱ ኑፋቄ ደግሞ ይህ ከላይ በርእስ የተጠቀሰው የኑፋቄ ወይም የክሕደት ዓይነት ነው፡፡ ክሕደት ወደነው አይመጣም በቦታና በጊዜም አይወሰንም፡፡ አሳች ሰይጣን እስካለ ጊዜ ድረስም ይቀጥላል፡፡ የሥጋ ሞት ለሰው ልጆች ሁል ጊዜ እንግዳ እንደሆነ ሁሉ የነፍስ ሞት ኑፋቄ ወይም ክሕደት ደግሞ ሁል ጊዜ እንግዳ ነው፡፡ 


ምንም እንኳን ክሕደት ወይም ኑፋቄ በየዓይነቱ እንደሚነሡ እንደሚመጡ ከክርስቶስ ጀምሮ ደቀ መዛሙርትም በወንጌልና በየመልእክቶቻቸው አስቀድመው ያስጠነቀቁና ያሳሰቡ ቢሆንም ጉዳዩ በቅዱሳት መጻሕፍት በግልጽ ይቀመጥም አይቀመጥ ኑፋቄ ወይም ክሕደት ያልተነሣበት የጉዳይ ዓይነትም የለም፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ወይም መጽሐፍ ቅዱስ በቁሙ የምሥጢር መጽሐፍ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ሲናገርም በቀጥታ ግልጽ ባለ ቋንቋ ከመናገር ይልቅ በምሳሌ ማስረዳትን ይመርጣል፡፡ ወንጌልን ስናነብ ማለትም የጌታን ትምህርት ያየን እንደሆነ ያለ ምሳሌና ምሥጢር የተናገረው ቃል የለም ማለት ይቻላል፡፡ አስቀድሞ ‹‹አፌን በምሳሌ እከፍታለሁ›› ተብሎ ተጽፏልና፡፡ 

Monday, May 13, 2013

የዲሞክራሲን ሥርዓት ምንነት ያለመረዳት ችግር የፈጠረው መወናበድ በፌዴራል ጉዳዮች ሚንስቴር የእምነት ተቋማትን ለመቆጣጠር በወጣ መመሪያ ሲገለጽ፡-



ሠዓሊ አምሳሉ /ኪዳን አርጋው
amsalugkidan@gmail.com

ከጽሁፉ የተወሰደ

  • የዚህ መመሪያ ግብም እንደመመሪያው አርቃቂዎች እምነት የእምነት ተቋማቱን እግዚአብሔር (ፈጣሪ) ከሚባለው ምናባዊ ነገር እንዲራራቁና እንዲረሳሱ በማድረግ የእነሱ ጉዳይ ፈጻሚዎችና አምላኪዎች እንዲሆኑ በማድረግ ሊፈጥሯት የሚፈልጓትን ከማንነቷ ፣ከታሪኳ ፣ከመለያዎቿ ተለያየችና የተካካደች አዲስ ሀገርና ሕዝብ መፍጠር ነው፡፡
  •  ስናያቸው ኢትዮጵያዊያን ይመስላሉ ወይም ናቸው ምን ነው ታዲያ በገዛ ማንነታቸው ላይ የጥፋት ዘመቻ ላይ መጠመዳቸው? ምን የሚሉት በሽታ ነው ይሄ? ይሄን ሁሉ ጉድ እውን የራስ ዜጋ ያደርገዋል ብሎ ማሰብ እንዴት ይቻላል?
  • የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን የኢትዮጵያዊነት መገለጫ እና መለያ ናትና፡፡ የኢትዮጵያዊነት መገለጫዎችን፣እሴቶችን ጠልቶ ኢትዮጵያዊ ነኝ ማለት አይቻልም ፤ይህች ቤተክርስቲያን ለሀገራችን ብቻ ሳይሆን ከራሷ አልፋ ለመላው ዓለም የዋለችው ቁም ነገር ሁሉ እጅግ ብዙና ውለታን ለሚያስብ ኅሊናም ላለው የሰው ፍጡር ሁሉ ውለታዋ ከክብደቱ የተነሣ የሚያስጨንቅና ዕረፍት የሚነሳ ነው
  • ኢትዮጵያ ሃይማኖት ከየትም አልመጣላትም፡፡ የመጣለት ነገር ቢኖር ኪዳናቱ ብቻ ናቸው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ኢትዮጵያ ከመቼ ጀምሮ በእግዚአብሔር እንዳመነች አልተገለጸም፡፡ የሚታወቀው ነገር ቢኖር ከቀደሙት የቀደምን መሆናችን ብቻ ነው፡፡


(አንድ አድርን ግንቦት 5 2005 ዓ.ም)፡- መሰንበቻውን የፌዴራል ጉዳዮች ሚንስቴር የእምነት ተቋማትን ለመመዝገብ (ለመቆጣጠር) አንድ መመሪያ ማውጣቱና እያነጋገረ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ይህ መመሪያ የተረቀቀውና ተግባራዊ ሊደረግ ታስቦ የነበረው በተመሳሳይ ዓላማና አንቀጾች በተለያዩ ሰብአዊና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ተሰማርተው ይሠሩ የነበሩትን መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን (NGOs) ያሽመደመደው ፣ መፈናፈኛ ያሳጣውና ከአገልግሎት ውጪ ያደረገው ደንብ ወይም መመሪያ ወጥቶና ተግባራዊ ሆኖ ለዓላማቸው አመርቂ ውጤት እንዳስመዘገበላቸው ባወቁ ጊዜ ነበር፡፡ ይህንን ውጤት በማየትም በተመሳሳይ መልኩ ደንቡን ወይም መመሪያውን በሃይማኖት ተቋማትም እንዲፈጸም ቢያደርጉ የልባቸው ሊደርስ እንደሚችል እምነት አሳድረው በመንቀሳቀስ ላይ እንዳሉ በመሀሉ ያልታሰቡ ሁለት የሞት አደጋዎች በመከሰታቸው እስከአሁን ሊቆይ ቻለ፡፡ አሁን ቀጥታ ወደ መመሪያው ዝርዝር ጉዳዮች ገብቼ ይሄ ይሄ ከማለቴ በፊት ለዚህና መሰል የቤተክርስቲያንን ጥቅም ለሚጋፉ መመሪያዎች መውጣትና መተግበር መሠረት ወደ ሆነው የተሳሳተ አስተሳሰብ ተመልሼ ጥቂት ብል ነገሩን በሚገባ ግልጽ ያደርገዋልና መለስ አድርጌ ልያዛቹህ፡፡

Friday, May 10, 2013

የአሰበ ተፈሪው አጥማቂ

(ይህ ጽሁፍ በአሰበ ተፈሪ ተከስቶ የነበረውን አጥማቂ ብቻ ይመለከታል)

(አንድ አድርገን ግንቦት 2 2005 ዓ.ም)፡- የዛሬ ሁለት ዓመት አንድ ሰው ከሰሜኑ ክፍል ይነሳና የማጥመቅ ስራውን እያከናወነ  ወደ ምስራቅ ክፍል ሐረር መንገድ አሰበ ተፈሪ ጉዞውን ይቀጥላል፡፡ አሰበ ተፈሪ ሲደርስ የማጥመቅ ጸጋ እንዳለው ለቤተ ክርስቲያን አባቶች እና ለአካባቢው ሊቀ ጳጳስ አስረድቶ ፤ የማጥመቅ አገልግሎት እንዲሰጥ ህጋዊ ፍቃድ አግኝቶ ሰዎችን ሊያጠምቅ ስራውን በይፋ ይጀምራል፡፡ ቅዳሜ እና እሁድ ከቅዳሴ በኋላ ስራውን ሲጀምር ለመጠመቅም ሆነ ለመመልከትም የመጡ ሰዎች እያጓሩ ፤ እየጮሁ ፤ ሌሎች እንደሚያደርጉት መውጣት ጀመሩ ፡፡ መንፈስ ተብዬው ሲለፈልም ‹‹ሟርት ነኝ›› ፤ ‹‹መተት ነኝ›› ፤ እገሌ ነኝ ማለቱን ቀጠለ፡፡ ማነው ያደረገብህ ? ተብሎ ሲጠየቅ ፤ የሚታዘዘው መንፈስ የደብሩን አስተዳዳሪ ፤ ቄሶችን ፤ ዲያቆናትን ፤መምህራንን ስም መጥራት ተያያዘው ፡፡ እዛ ያለው ሰው ግራ ገባው ፤ ግማሹ ‹ይሄ ሰውዬ ትክክለኛ እጥማቂ አይደለም ፤ እነዚህን ዲያቆናትና ፤መምህራንን  እናውቃችዋለን ንፁህ ናቸው›› ሲል ፡፡ ሌላው ክፍል ደግሞ ‹ያው መንፈሱ እኮ ተናገረ ፤ ከዚህ በላይ ምስክር አያሻንም›› ብለው ስማቸው የተጠራውን ቀሳውስ ዲያቆናት ፖሊስ አስጠርተው አፍሰው እስር ቤት ከተቷቸው፡፡ ይህ ሰው መሰል ተግባሩን በተለያዬ ቦታዎች ውስጥ እየዞረ በመስራት መሰል ነገሮች በሶስት ቤተ ክርስትያኖች ላይ ተከሰተ፡፡ ቀሳውስቱ ፤ዲያቆናቱ ሁሉም ዘብጥያ ወረዱ፡፡
ቤተ ክርስቲያን ማን ይቀድስ? ማንስ ቀድሶ ያቁርብ?  ነገሩ በጣም አስቸጋሪ ሆነ የአካባቢው ምእመን እነዚህን ቀሳውስቱንና ዲያቆናቱን ደግመን ማየት አንፈልግም ስላለ የአካባቢው ሀገረ ስብከት አስተዳዳሪ ሊቀ ጳጳስ  መንፈሱ መሰከረባቸው የተባሉትን አባቶች ወደመጡበት ማሰናበት እና አዲስ አገልጋዮችን በማምጣት ሂደት ውስጥ ከአንድ ወር በላይ ቤተክርስትያኑ ተዘጋ ፤ አገልግሎቱም ተስተጓጎለ፡፡ ይህ በእንዲህ እያለ ይህ ሰው ብር መሰብሰቡን ማጥመቁን የከለከለው አካል አልነበረም፡፡ አንዳንድ ቦታ ላይ እሱን ለመጋበዝ እስከ 7000 ሺህ ብር ድረስ ከምዕመናን ይሰበሰብ እና ይጋበዝ ነበር፡፡ እዛው አካባቢ ያሉ አብያተ ክርስቲያናት በጧፍ እጥረት አገልግሎቱ ማከናወን ሲገዳደራቸው እየተመለከቱ ለአንድ ህገ ወጥ አጥማቂ ግን 7000 ብር በቀናት ጊዜ ውስጥ እንዴት መሰብሰብ እንደቻሉ ለተመለከተ ይገረማል

ይህ በእንዲህ እያለ ሰውየው ሌላ ቦታ ላይ ተጋብዞ ለማጥመቅ ሄደ፡፡ እዚያ ቦታ ላይ ደግሞ የተከሰተው ነገር ከአሰበ ተፈሪው የተለየ ነበር፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ ባልታወቀ ምክንያት ከዓመታ በፊት ተቃጥላ ነበር ፤ የአካባቢውም ምዕመን በቻለው መጠን የበፈት ይዞታዋን ሳትለቅ እንደገና መስራት ችሎ ነበር ፡፡ ይህ ‹‹አጥማቂ›› ነኝ ባይ እዚች ቤተ ክርስቲያን ላይ እያጠመቀ ሳለ አንዱ መንፈስ የያዘው ሰው ይነሳና መለፍለፍ ይጀምራል፡፡‹‹ቤተ ክርስቲያኗን ያቃጠላት መምህሬ እገሌ ነው›› ብሎ መሰከረ፡፡ ሰው እውነት መስሎት ያን መምህር ካልገደልነው ብሎ ተነሳ፡፡ በመሀል አንድ አባት ይነሱና እረፉ ‹መንፈስን ሁሉ አትመኑ›› ነው የተባለው፡፡ አንተም ማጥመቅህን አቁም ፤ ‹‹በችግር የተያዙትን እስራታቸውን እግዚአብሔር ይፍታ ስንል አንተ ደሞ ሌላ ብጥብጥ አመጣህብን›› ብለው በሰላም ሸኙት፡፡ 
ለቤተ ክርስትያን መቆርቆራች ባልከፋና ጥሩ ሆኖ ሳለ እንዴት እንደምናስብላት አለማወቃችን ደግሞ ሌላ ችግር እየፈጠርን መሆኑን ተገንዝበነው አናውቅም፡፡  አሁንም የአካባቢው ሰው አቃጠለ የተባለውን መምህር ይዘው ለፖሊስ አስረከቡ ፡፡ ፖሊስም እስኪጣራ ብሎ መምህሩን አሰረው ፤ ፖሊስ ምንም አይነት ተጨባጭ ማስረጃ ስላላገኝ መምህሩን ፈትቶ ሀገር ለቆ እንዲሄድ ያሰናብተዋል፡፡ ህዝቡም አይንህን እንዳናይህ ቤተክርስትያናችን አቃጥለህብን  ብለው ‹‹አይንህ ለአፈር›› አሉት፡፡
ይህ ሁሉ እየሆነ ማስተዋል የሚችል ሰው በመጥፋቱ በሌላ ጊዜ ፤ ሌላ ቦታ ላይ ሰውየው መንፈስ ያወጣል ፤ ተዓምረኛ ነው ሲባል የሰሙ ምዕመኖች ይምጣልን ብለው የጠየቃቸውን ብር ከማህበረሰቡ ላይ ፤ ከሀላፊ አግዳሚው ላይ መሰብሰብ ይጀምራሉ ፡፡ አሁንም የዚህ ሰውዬ ማንነት ለማወቅ ሰው አይነ ልቦናው አልበራለትም ነበር  ፤ ራሱ መተተኛ በመተት የተያዘ ሰው እፈታለሁ ፤ ከዲያቢሎስ ቁራኛነት እገላግላችዋለሁ ብሎ ማወራቱን ማጥመቁን ተያይዞታል ፡፡ አባቶች እዚህ ጋር ተሰብስበው መከሩ ፡፡ እንቢ አይመጣብ ቢሉ ‹‹የራሳችሁ ጉድ እንዳይወጣባችሁ›› ነው ይባላሉ ፤ ይምጣ ቢሉ ደግሞ ቤተክርስትያኗን ፈትቶ ፤ ያሉትን ካህናት እንዲባረሩ አድርጎ ምዕመኑን ለሌላ እምነት አሳልፎ ሊሰጥ ነው፡፡ ግራ የሚገባ ነገር ሆነ ፡፡ አባቶች ተሰብስበው መከሩ እንዲህም አሉ ፡- በሚቀጥለው ‹‹ እሁድ ጠዋት መምጣት ይችላል ፤ ነገር ግን እኛ ለሊቱን ሙሉ የገብርኤልን ፤ የሚካኤልን ፤ ሁሉን ድርሳናት እንድገም ፤ ሙሉ ዳዊት ደግመን ጸሎት እናድርግ ፤ መልካ መልኮችን እናድርስ ፤ ከዛ እኛ በማኅበር ሆነን ባደረግንበት ፀበል እሱ መጀመሪያ ይጠመቅ ፤ ከዛ እኛ ሁላችንም እንጠመቃለን ፤ ከዛ ምዕመኑን ያጠምቃለል ›› ብለው ቃለ ጉባኤ ይዘው ተፈራርመው ፤ ወስነው ስብሰባን ዘጉ፡፡ 

አጅሬ ለካ ምን እንደተባለ መንፈሱ ይንገረው ማን ይንገረው አልታወቀም፡፡ ቅዳሜ ለእሁድ አጥቢያ በህብረት ሆነው ቃል የገቡትን አድርገው ቢጠብቁት ቢጠብቁት ሊመጣ አልቻለም፡፡ በቃ እሺ ብለው ሌላ ቀጠሮ ያዙለት ፤ አሁንም ሊመጣ አልቻለም ፡፡ የቀረበትን ምክንያት ሲጠይቁት ተልካሻ ነገር ነገራቸው፡፡ ይገርማል !!!! ሰዎች ቀስ እያሉ የሰውየው ማንነት ስለገባቸው ገፍተው ከአካባቢው አባረሩት፡፡ ይህ ሰው ይህን አይነት ስራ ደቡብ አካባቢ ሲሰራ ሌባና አጭበርባሪ መሆኑ ታውቆ በእስር ቤት እንደሚገኝ ከጊዜ በኋላ ሰማ፡፡ እኛ ይህ ሰው በአንድ ቦታ ላይ ብቻ ያደረገውን ብቻ እናውቃለን ፤ በፊት ምን ያህል ቤተ ክርስቲያን ይበትን? ፤ አሁን ምን ይስራ? ፤ በአሁኑ ሰዓት ምንም የምናውቀው ነገር የለም፡፡
እኛ አይናችን ታውሯል ፤ እናያለን አናስተውልም ፤ እንሰማለን አናዳምጥም ፤ በቃ እንደዚህ ነን፡፡ እነሱም እየዞሩ ቤተ ክርስቲያን ያፈርሳሉ ፤ ቤቱን ይፈታሉ ፤ ተከታዮች ያፈራሉ ፤ በሲዲ አድርገው አቀነባብረው ለኛው ይሸጡልናል ፤ እኛም ‹‹ይገርማል›› እያልን እናያለን፡፡ ስራቸው ሳይሆን የሚገርመው እኛ ነን የምንገርመው፡፡
የአካባቢው አባቶች ጠይቀን እንደተረዳነው ፡- ‹‹ይህው እሱ በዚያን ጊዜ አጠምቃለሁ ብሎ ውሀ የረጨባቸው ሰዎች አሁንም ይጥላቸዋል ፤ ምን እንዳሰፈረባቸው እግዚአብሔር ይወቀው ፤ እሱ ሳይመጣ በፊት ጤነኞች ነበሩ ፤ እሱ ካጠመቃቸው በኋላ ግን በሽታ ላይ ጥሏቸው ሄደ ፤ አንዳንዶቹ ቤተክርስትያን እየመጡ እየተጠመቁ እየተሸላቸው ነው ፤ አንዳንዶቹ ግን አሁን በሽተኞች ናቸው››  ብለው ነበር የነገሩን ፡፡ ይህን ሲነግሩን ያለንበት ጊዜ ምን ያህል አስቸጋሪ መሆኑን ነው የተረዳነው፡፡
በቅርብ ጊዜ ደብረ ብርሐን ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን አዲስ አጥማቂ መጥቷል ተብሏል.. እስኪ ነገሩን አጣርተን እንመለሳለን