Monday, April 29, 2013

ዘሰሙነ ሕማማት




(አንድ አድርገን ሚያዚያ 21 2005 ዓ.ም)፡- ሰሙነ ሕማማት በነብዩ ኢሳያስ ‹‹ነስአ ደዌነ ወፆረ ሕማመነ ፤ በእውነት ደዌአችንን ተቀበለ፤ ሕማማችንንም ተሸከመ ፤ እኛ ግን እንደተመታ ፤ በእግዚአብሔር እንደተቀሰፈ ቆጠርነው፡፡ እርሱ ግን ስለመተላለፋችን ቆሰለ ፤ ስለበደላችን ደቀቀ ፤ የደኅንነታችንም ተግሳጽ በእርሱ ላይ ነበረ ፤ በእርሱም ቁስል እኛ ተፈወስን›› ኢሳያስ 53 ፤4 ተብሎ የተነገረው ቃል ተፈጽሞ ፤ ጌታችን ለድኅነተ ዓለም ሲል በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ የተቀበለውን ጸዋትወ መከራ የሚዘከርበት ሳምንት ነው፡፡ ከሆሳህና ማግስት እስከ ትንሳኤ ያለው የጾመ እግዚእነ መዝጊያ ሳምንት ሰሙነ ሕማማት ይባላል፡፡ 


በማኅበረ ቅዱሳን የሚታተመው የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ልዩ የ2004 ዓ.ም እትም ስለ ሰሙነ ሕማማት ፤ ሥርዓተ ሰሙነ ሕማማት ፤ ሃይማኖታዊና ትውፊታዊ ክንዋኔዎች በሰሙነ ሕማማት ፤ ሕማማተ እግዚእነ በልሳነ አበው ፤ በሰሙነ ሕማማት የሚነሱ ጥያቄዎችና መልሶቻቸው ፤ መጽሐፈ ግብረ ሕማማት እና ፍኖተ መስቀል በሚል አብይ አርዕስቶች የተከፋፈለ ባለ 30 ገጽ ትንሽ መጽሐፍ አሳትሞ ነበር ፡፡ አንድ አድርገን ይህን መጽሐፍ በዚህ ወቅት ማግኝት ላልቻሉ በሀገር ውስጥም ሆነ ከሀገር ውጪ ለሚኖሩ ምዕመናን ወደ ፒዲፍ በመቀየር አቅርባላችኋለች ፡፡ በርካታ እውቀትን ይገኙበታል ያንብቡት…

የሳምንቱ የአንድ አድርገን ስጦታ

አርቲስት ጀማነሽና ግብር አበሮቿ ዘብጥያ ወረዱ


(አንድ አድርገን ሚያዚያ 21 2005 ዓ.ም )፡- ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ራሳቸውን ማህበረ ስላሴ ደቂቀ ኤልያስ የሚል ስም በመስጠት ሲንቀሳቀሱ የነበሩት ሰዎች ባሳለፍነው ሳምንት ውስጥ በተነሳባቸው ተቃውሞ ምክንያት ዘብጥያ ሊወርዱ ችለዋል ፤ አራት ኪሎ አካባቢ በተከራዩት አዳራሽ አማካኝነት ከምሽቱ አንድ ሰዓት እስከ ውድቅት ለሊት ድረስ በሚያካሂዱት ጉባኤ መሳይ ስብሰባ የአካባቢው ማህበረሰብ ስራቸውን በመቃወማቸው  ፤ ሰላማችንን አሳጡን በማለት ለፖሊስ በማመልከታቸውና ይህን ተከትሎ በተነሳው ውዥንብርና ግርግር ፖሊስ አርቲስት ጀማነሽን ፤ አንድን የእምነቱን ፈልሳፊ ሰው እና ቤቱን ለመስብሰቢያ ያከራየውን ሰው እስር ቤት ሊያስገባቸው ችሏል፡፡

Tuesday, April 23, 2013

‹‹ተዓምሯን አንቀብርም›› በሚል አርዕስ ታላቅ የቅኔ ምሽት ተካሄደ ፤ ከእሳት የተረፉት ንዋየ ቅድሳትም ለምዕመኑ ለእይታ ቀረቡ

(አንድ አድርገን ሚያዚያ 15 2005 ዓ.ም)፡- በአጉስታ ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን “ተዓምሯን አንቀብርም”በሚል አርዕስ ታላቅ የቅኔ ምሽት ባሳለፍነው እሁድ ሚያዚያ 13 2005 ዓ.ም የመንፈሳዊ ኮሌጅ መምህራን ፤ ታላላቅ የቅኔ ድጓ እና የአቋቋም ምሁራን በተገኙበት ተካሄደ፡፡ በጊዜው የደብሩ ሰበካ ጉባኤ እና የስብከተ ወንጌል ጽ/ቤቱ አንድ ላይ ሆነው ባዘጋጁት መርሀ ግብር ላይ በርካታ አዲስ አበባ ውስጥ አሉ የሚባሉ በተለያዩ የአገልግሎት ዘርፎች በቤተክርስቲያኒቱ ውስጥ የሚያገለግሉ ሊቃውንት ተገኝተዋል፡፡ የጉባኤው ዋናው ዓላማው ከእሳት ቃጠሎ የተረፉ ንዋየ ቅድሳትን ለምዕመኑ ለማሳየት መሆኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በጉባኤው ላይ በቦታ ሄደን እንደተመለከትነው ባየነው ነገር እጅግ ተገርመናል ፤ የእግዚአብሔርንም ተዓምር አድንቀናል ፤ ከእሳት ቃጠሎ የተረፉ በቦታው ላይ የተደረገው የእግዚአብሔርን ተዓምር የሚመሰክሩ በርካታ መጻህፍት ፤ ወደ ዘጠኝ የሚጠጉ የእንጨት መስቀሎች ፤ መጎናጸፊያ እና መሰል በርካታ ንዋየ ቅድሳትን ለመመልከት ችለናል፡፡ በጊዜው የተገኝው የጉባኤው ተካፋይ ምዕመን በሁኔታ እጅጉን መገረሙን ሲገልፅ አስተውለናል፡፡ የመርሀ ግብሩ አስተባባሪና የደብሩ የቁጥጥር ክፍል ኃላፊ መጋቢ ስርዓት ያዕቆብ እንደገለጸው የእመቤታችን ተዓምር እዚህው ተቀብሮ መቅረት ስለሌለበት ወደፊት ቦታውን የረገጠ ምዕመን ሁሉ ይመለከተው ዘንድ ግቢው ውስጥ ትንሽ ሙዚየም በሰበካ ጉባኤው አማካኝነት በማሰራት ከእሳት የተረፉትን ንዋየ ቅድሳት በውስጡ ለማስቀመጥ እንደታሰበ ገልጿል፡፡በተጨማሪም በአሁኑ ሰዓት ምዕመኑ በዚህ ሳምንት ውስጥ እስከ ሚያዚያ 21 2005 ዓ.ም ድረስ በቦታው ላይ በመገኝት ተዓምሯን ይመለከት ዘንድ አስጎብኚ በመመደብ በደብሩ ቅጥር ግቢ ውስጥ የማሳየት ተግባር እየተከናወነ ይገኛል ፤ እነዚህን ንዋየ ቅድሳት በቪዲዮ የተቀረጹ ሲሆን በቅርብ ቀንም ቦታው ላይ ድረስ ሄደው መመልከት ላልቻሉት ምዕመናን ለማድረስ መታሰቡን ለማወቅ ችለናል፡፡

የተቀረጸው ቪሲዲ ሲለቀቅ ለተመልካች ለማቅረብ እንሞክራለን

ስለ ሁኔታው የተሻለ መረጃ ለማግኝት እና ለተጨማሪ ጥያቄዎች የደብሩን ቁጥጥር ክፍል ኃላፊ መጋቢ ስርዓት ያዕቆብ በዚህ  ቁጥር ማግኝት ይችላሉ፡፡
0912-629177

‹‹በውጭ ሲኖዶስ ሠራን የሚሉት ከአቡነ ጳውሎስ የባሱ ፥ ሃይማኖትን ጭራሽ የቀየሩ፣ ኃይማኖትንም የሚሳደቡና ከእግዚአብሔር መንገድ የወጡ ሰዎች ናቸው››


ከዚህ በፊት የተለያዩ ሰዎችን አስተያየት ብሎጋችን ላይ ምንም አይነት ማስተካከያ ሳናደርግ እንደወረደ ለአንባቢዎች ማቅረባችን ይታወቃል ፤ ከእነዚህ ጸሀፊዎች አንዱ የሆነውን የሰዓሊ አምሳሉ ሶስት ጽሁፎች ይጠቀሳሉ ፤ የሰዓሊ አምሳሉን ፅሁፍ መልስ የሚሆን ጽሁፍ ከሀገር ውጪ ከሚኖር ኃይለሚካኤል ከሚባል አንባቢ ስለደረሰን ጽፉን እንዲህ በማድረግ ለአንባቢያን አቅርበነዋል፡፡

(አንድ አድርገን ሚያዚያ 15 2005 ዓ.ም)፡- ሰዓሊ አምሳሉ ገብረኪዳን አርጋው የተባለ ሰው ባለፈው አንድ ሰውፖለቲከኛ ነው” ሲለው ለካ አውቆት ኖሯል። እኔ እኮ ምንም የእውቀት ችግር እንደነበረበት ባውቅም ከልቡ ለቤተክርስቲያን የሚያስብ ሰው መስሎኝ ነበር። በመጀመሪያ ባለፈው ጊዜ አምሳሉ ፓለቲከኛ ነው ሲል የተቃወምኩትን ሰው ይቅርታ እጠይቃለሁ። ከዛ በተረፈ ግን የአንድ አድርገን ብሎግ አዘጋጆች ከዚህ በታች ያለውን አስተያየት ለአንባቢያን ታደርሱልኝ ዘንድ እጠይቃለሁ።

በአዲስ አበባ 3 ዓመት አገልግሎት ሲሰጥ የነበረው የቅዱስ ሩፋኤል ቤተክርስቲያን ቦታ የኢንደስትሪ ዞን ነው በማለት ፈረሰ



(አንድ አድርገን ሚያዚያ 15 2005 ዓ.ም)፡- በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 11 የሚገኝው የቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን በኢንደስትሪ ዞን ላይ የተሰራ ነው በሚል የወረዳው ዋና ስራ አስፈጻሚ ጽ/ቤት ለቅዱስ ሲኖዶስ በጻፈው ደብዳቤ 24 ሰዓት ሳይሞላው ማፍረሱን የደብሩ ኃላፊዎች አስወቁ፡፡

ሚያዚያ 9 ቀን 2005 ዓ.ም ከምሽቱ አንድ ሰዓት ሲሆን የወረዳው ዋና ስራ አስፈጻሚ ኤልሳቤት መንግስቱ የደብሩን ኃላፊዎች በጽ/ቤታቸው እንዲገኙ የስልክ ጥሪ በማድረግ ቤተክርስቲያን እዲያፈርሱ የነገሯቸው መሆኑን ያስረዱት የደብሩ ኃላፊዎች ቤተ ክርስቲያን የማፍረስ ስልጣን  የእነሱ አለመሆኑን በመግለጻቸው በማግስቱ ጠዋት 3 ሰዓት ወረዳው ለሲኖዶስ የላከው ደብዳቤ ይዘው ከወረዳው ተወካይ ጋር በሲኖዶስ ተገናኝተው እየተወያዩ ሳለ የወረዳው ዋና ስራ አስፈጻሚ በሶስት መኪና ፖሊስ በመታገዝ በሕገ ወጥ መንገድ እንዲፈርስ ማድረጋቸው የደብሩ ኃላፊዎች  አስታወቁ፡፡

Thursday, April 18, 2013

በሕግ አምላክ 5 ሳይባል 6 አይባልም!!


  ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው
 amsalugkidan@gmail.com        
ይህ ጽሑፍ በዕንቁ መጽሔት የወጣው በጥር ወር መጨረሻ ነበር ፡፡ ከዚህ ጽሑፍ ቀደም ሲል የወጣውን የጸሐፊውን ጽሑፍ ‹‹ጉባኤ ኬልቄዶን ለኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን እንደ መልካም አርዓያ ሊወሰድ ይገባልን ?›› በሚል ርእስ የጻፈውን ጽሑፍ በእኛ ብሎግ መለጠፋችንና አንባብያንም በርካታ ጥያቄዎችን ማንሣታቸው ይታወሳል ይሄኛው ጽሑፍ ለጥያቄዎቹ ምላሽ የሚሰጥ ስለሆነ ከወጣ የቆየ ቢሆንም የተለያዩ ሃሳቦችን ከማንሸራሸር  ፤ የተለያዩ የሰዎችን እይታ ከማስተላለፍ አኳያ ይረዳል ብለን ስላሰብን እነሆ ለጥፈነዋል መልካም ንባብ፡፡ (ይህ የአንድ ሰው ሃሳብ ነው)

(አንድ አድርገን ሚያዚያ 10 2005 ዓ.ም)፡- የፈሩት ይደርሳል የጠሉት ይወርሳል እንዲሉ የ4ኪሎዎቹ ግራ ክንፍ አባቶች ቡድን ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስን ወደ መንበረ ፕትርክናቸው እንደማይመልሱ ይፋ አደረጉ፡፡ ምክንያቱም አሉና ከ20 ዓመታት በፊት በሕመም ምክንያት ሥራውን መሥራት አልችልም በሚል ደብዳቤ አስገብተው ትተውት ስለሄዱ በቦታቸው ሌላ ፓትርያርክ ተክተን ቆይተናል አሁን ለ20 ዓመታት ምንም እንዳልተሠራ ቆጥረን ወደኋላ መመለስ አንችልም ፡፡ በማለት የሚያውቁትን እውነት ሳይሆን የሚኖሩትን እብለት በይፋ ተናገሩ ፡፡ ለዚህ ለዚህማ ድርድሩና እርቁስ ለምን አስፈለገ? ፡፡ሰዎቹ በመግለጫቸው ብፁዕነታቸው ልሂድ ሲሉ አሉ «ቅዱስ አባታችን ለማን ትተውን ይሄዳሉ? ማንስ ይሰበስበናል?» ብለን ለምነናቸው ነበር፡፡ ከሄዱም በኋላ ለ10 ወራት ያህል ጠብቀን ሕመማቸውም ተሽሏቸው ከሆነ እንዲመለሱልን ጠይቀናቸው ነበር ብለዋል፡፡ ታዲያ መሄዳቸው ይህንን ያህል ያስጨነቃቸው ያስከፋቸውም ከሆነና እንዳሉትም መመለሳቸውን  የሚፈልጉና የሚናፍቁ ከሆነ ምነዋ ታዲያ አሁን ልመለስ ሲሉ ምን ሲደረግ ዘራፍ ማለታቸው? በቀል መሆኑ ነው ወይስ ውሸት?፡፡ እውነቱን ግን ማለትም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ማን እንዴት አድርጎ እንዲሰደዱ እንዳደረጋቸው አይደለም እነሱ ሕዝበ ክርስቲያኑም በተለይ በአሁኑ ጊዜ በሚገባ የሚያውቀው ጉዳይ ነው፡፡ ይህንንም እያወቁ ለአፍታ እንኳን እግዚአብሔርን ባለማሰብ ፤ ባለመፍራትና ባለማፈር ማበላቸው ለገዛ ራሳቸው ያላቸውንና የሚሰጡትን ዝቅተኛና እርካሽ ዋጋ ሊያሳይ ቢችል እንጂ ሌላ የሚፈጥርላቸው እርባና እንደሌለ ኅሊናቸው ያውቀዋል፡፡

Wednesday, April 17, 2013

‹‹እኔ ማርያም ነኝ›› ያለችው ወይዘሮ ትዕግስት በእስራትና በገንዘብ ተቀጣች

(ሰንደቅ ሚያዚያ 9 2005 ዓ.ም)፡- የፌደራሉ አቃቢ ሕግ የማይገባትን ጥቅም ለማግኝት በማሰብ በተለያዩ ጊዜያትና ቦታዎች በመንቀሳቀስ ሰዎችን በማታለል ‹‹እኔ ማርያም ነኝ ፤ እንደ ኢየሱስም በጅራፍ ተገርፌአለሁ ፤ ከሞትም ተነስቻለሁ ፤ የወለድኳቸውን ልጆች ያገኝሁት በመንፈስ ነው›› ስትልና የዓለም ፍጻሜ ደርሷል በሚል የሰዎችን የግል ሀብት ለራሷ ስታደርግ ደርሼባታለሁ ሲል ክስ የመሰረተባት የ34 ዓመቷ ትዕግስት ብርሃኑ ወ/ጊዮርጊስ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 6ተኛ ወንጀል ችሎት ፊት ቀርባ ጥፋተኛ ሆና በመገኝቷ በ2 ዓመት ከ4 ወር ጽኑ እስራትና በ1000 ብር የገንዘብ መቀጮ እንድትቀጣ ሲል ባሳለፍነው ሳምንት ወሰነ፡፡

እንደ አቃቢ ሕግ የክስ ዝርዝር ከሆነ ግለሰቧ በአራት የተለያዩ ክሶች የተወነጀለች ሲሆን ፤ የፊደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ‹‹ለሰው ሕይወት ማለፍ ሳቢያ ነች›› ሲል አቃቢ ሕግ ያቀረበውን ክስ ያልተሟ ነው ሲል ውድቅ ሲያደርገው በተቀሩት 3 ክሶች ግን ጥፋተኛ ነች ብሎ እንድትከላከል ብይን ሰጥቷል፡፡

Monday, April 15, 2013

ተዓምሯን አንቀብርም


 (አንድ አድርገን ሚያዚያ 7 2005 ዓ.ም)፡- በአዲስ አበባ ባለፉት አስርት አመታት ውስጥ ከተቆረቆሩት አብያተ ክርስቲያናት አንዷ አጉስታ ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን አንዷ ነች፡፡ ይች ቤተ ክርስቲያን በምዕራብ አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ውስጥ በጦር ኃይሎች ወይራ ቤተል መንገድ አውጉስታ ልብስ ስፌት ፋብሪካ አካባቢ ትገኛለች፡፡ ቀደም ሲል ከንጉሠ ነገሥቱ ዘመን ጀምሮ ቤተ ክርስቲያኒቱ ያረፈችበት ቦታ ‹‹የቢስ ግቢ›› እየተባለ ይጠራ ነበር፡፡ ከዚያም ጊዜ በኋላ ለቀድሞ መንግሥት ደርግ ለከፍተኛ ሹማምንቱ እና ባለሥልጣናቱ ለመኖሪያ ቤት መስሪያነት ቦታውን ቢሰጥም ‹‹ግቢው ከብዶናል እዚህ ግቢ ውስጥ ቤት አንሰራም››በማለት ቦታው የተመሩት ሰዎች በአንድም ይሁን በሌላ ምክንያት ቤት ሳይሰሩበት ቦታውን ትተው ሊሄዱ ችለዋል፡፡ ከዚህ በኋላ መንግሥት ለአካባቢው ልጆች እንዲማሩበት ለትምህርት ቤት ቦታውን ቢፈቅድም የአካባቢው ማኅበረሰብ ልጆቻቸውን እዚህ ቦታ ማስተማር ባለመፍቀዳቸውና ለመንግስትም አቤቱታ በማሰማታቸው ትምህርት ቤትም ሊሰራበት አልቻለም ፡፡ ይህም አቤቱታ የተመለከተው መንግሥት በአካባቢው ላይ ሌላ ቦታ ላይ ‹‹ትንቢተ ኤርሚያስ›› በመባል የሚታወቀው ትምህርት ቤት ሊመሰርትላቸው ችሏል፡፡ ቦታው ወጣቶችና ህጻናት የኳስ መጫወቻ አድርገውት እንደነበር ለተወሰነ ጊዜም ባዕድ አምልኮ ይፈጽሙበት እንደነበር ቦታውን የሚያውቁት አረጋውያን አባቶች ይናገራሉ፡፡ ይሁን እንጂ የመማጸኛ ከተማ ተብሎ በመጽሐፍ ቅዱስ እንደተጻፈ ሁሉ ከብዙ ቦታዎች ይልቅ ይህ ቦታ ለህሙማን መፈወሻ ፤ ሀዘን ለገባቸው ማረጋጊያና የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ  አድርጎ በእግዚአብሔር ስለተመረጠ ለዘመናት በመጠበቅ አሁን ላይ በመድረስ የተዓምራት መገለጫና መታያ ቦታ ሊያደርጋት ችሏል፡፡ 

 ይህ እንዲህ እንዳለ የአካባቢው ምዕመናን ሥርዓተ አምልኮ የሚፈጽሙበትና እግዚአብሔርን የሚያመልኩበት ሥፍራ በመራቁ  ምክንያት ፤ ህጻናት የሥላሴን ልጅነት የሚያገኙበት ፤ ወጣቶች ስርዓተ ቤተክርስቲያንን የሚማሩበት ፤ ስብከተ ወንጌልን የሚያገኙበት ፤ አረጋውያን አባቶች በቦታ ርቀት ምክንያት ስጋወ ወደሙ የሚቀበሉበት ቤተክርስቲያን በመራቁ ምክንያት ለበርካታ ጊዜያት ሲጨነቁ ይኖሩ ነበር፡፡ ‹‹ጊዜ ሲደርስ አምባ ይፍረስ›› እንዲሉ ከዚህ ሁሉ ነገር በኋላ በእመቤታችን ፍቃድ እዚህ ቦታ ላይ ከአስራ አንድ ዓመት በፊት ጥቅምት 24 1994 ዓ.ም ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ልትመሰረተ ችላለች፡፡

ታቦተ ጽዮን በአጉስታ አካባቢ ከገባችበት ጊዜ ጀምሮ አካባቢው ከእመቤታችን ፈውስና በረከት እየተጎበኝ ይገኛል፡፡ ቀደም ሲል አቃቂ ተብሎ የሚጠራው ወንዝ ውስጥ ብዙ ሰዎች እየገቡ ይሞቱ የነበሩበት ሁኔታ በእመቤታችን ጠባቂነት በአሁኑ ሰዓት ሙሉ ለሙሉ ሊወገድ ችሏል፡፡  ለአስርት አመታት መድሃኒት ካልተገኝለት ከኤች.አይ.ቪ በሽታና በተጨማሪ ተላላፊ ካልሆኑ በሽታዎች መካከል ከስኳር ፤ ከአስም ፤ ከልብ ህመምና ከካንሰር በሽታ የእመቤታችንን ጸበል በመጠመቅና በመጠጣት ብዙ ህመምተኞች እንደዳኑም አስተዳዳሪው መልአከ መዊዕ ስብሀት ባይህ ይገልጻሉ፡፡ የደብሩ ስታስቲክስ ክፍል መረጃ እንደሚያመለክተውም በጸበሏም ተጠምቀው ከዳኑት ሰዎች መካከል እስከ አሁን 15 የሚሆኑ ሙስሊሞች አምነው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን እምነት አባል ለመሆን በቅተዋል፡፡

የዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ  654-56  ላይ ‹‹ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘላለም ሕይወት አለው ፤ ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ በእኔ ይኖራል እኔም በእርሱ እኖራለሁ።›› የሚለውን በወንጌል ቃል መሠረት በማድረግ በአሁኑ ወቅት ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን የበርካታ ምዕመናን ስጋወ ደሙ መቀበያ ቤተክርስቲያን ልትሆን ችላለች ፡፡ በወትሮ ቀን የተቀባዩን ምዕመን ሰልፍ ከቤተ ክርስቲያኒቱ በራፍ  መውጫ ላይ ሲሰለፉ ማየት ያልተለመደ ቢሆንም ፤ ባለንበት የአብይ ጾም ግማሽ በደብረ ዘይት ዕለት ግን ምዕመኑ እጅጉን ስለበዛ ከቤተክርስቲያኗ  የውስጥ መውጫ በር እስከ ዋናው የቤተክርስቲያን መግቢያ የውጭ በር ድረስ ስጋው ደሙ ለመቀበል ተሰልፈው መመልከት ችለናል ፡፡ በሁኔታውም እጅጉን ተገርመናል ፤ ይህን ያህል ሰልፍ ስጋወ ደሙ ለመቀበል የምንመለከተው በነሃሴ 24 በደብረ ሊባኖስ አቡነ ተክለሃይማኖት ገዳም ነበር፡፡

ከሦስት ወር በፊት በወርሀ ጥር በአስራ አራተኛው ቀን 2005 ዓ.ም መነሻው እስከ አሁን ባልታወቀ ምክንያት ቤተክርስቲያኒቱ የእሳት አደጋ ደርሶባት ነበር ፡፡ አደጋው የደረሰበት ቀን እና ሰዓት ሰዎች በስራ ምክንያት በአካባቢው የማይገኙበት በመሆኑ እሳቱ ቤተክርስቲያኒቱ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ማድረስ ችሏል፡፡  መዝሙረ ዳዊት 69፤35 ‹‹እግዚአብሔር ጽዮንን ያድናታልና›› እንዲል ታቦተ ልደታ ለማርያም ፤ ታቦተ ዮሐንስ መጥምቅና የቅዱስ ኡራኤል ጽላቶች አንዳች እሳት ሳይነካቸው በተዓምር ከአደጋው ሊተርፉ ችለዋል፡፡ በተጨማሪም አባቶች ለአገልግሎት የሚጠቀሙባቸውታአምረ ማርያም ፤ መጽሐፈ ስንክሳር ፤ መጽሐፈ አርጋኖ ፤ ገድለ ዮሐንስ መጥምቅ ፤ መጽሀፈ ቅዳሴና የተለያዩ መጠን ያላቸው የእንጨት መስቀሎች በእሳቱ ብዙም ጉዳት ሳያደርስባቸው ለምልክት ያህል በመለብለብ ብቻ ሊተርፉ ችለዋል፡፡ የቤተክርስቲያቱ ምሰሶ እንጨት ሆኖ ሳለ እሱ ወደ አመድነት ሲቀየር አባቶቻችን ምዕመኑን የሚባርኩበት መስቀል የእሳት ነበልባል ብቻ አርፎበት መትረፉ ሁሉን አስገርሟል ፡፡ ከእሳት የተረፉት መስቀሎች በነሀስ በብር እና በብረት የተሰሩ ቢሆኑ ኖሮ ለመትረፋቸው በርካታ ምክንያቶች በተሰነዘሩ ነበር  ግን አልሆነም ፡፡ ቤተክርስቲያኒቱ የተሰራችበትን የግድግዳ ማገር ፤ ቆርቆሮ እና እንጨቶች ላይ ወደ አመድነት የመቀየር አቅም የነበረው እሳት የእግዚአብሔር ስም የሰፈረበት የእመቤታችን ውዳሴ እና ምስጋናን ፤ የጻድቃን የሰማዕታትና የመላእክትን ምስጋና የተሸከሙ መጻህፍት ላይ ይህ ነው የሚባል ጉዳት አለማድረሳቸው ተአምር ሆኖ አልፏል፡፡ በወቅቱ አንድ አባት የደረሰውን ጉዳት በመመልከት አንገታቸውን እየነቀነቁ ‹‹እግዚአብሔር በጽዮን ታላቅ ነው›› መዝሙረ ዳዊት 76፤2 ፤ ‹‹ማደሪያውም በጽዮን ነው›› መዝሙረ ዳዊት 76፤2  የተባለው ‹‹እሳቱን እንዴት እሳት ይበላዋል?›› በማለት የሆነው ነገር  አይተው ሁኔታውን አድንቀዋል፡፡
ከቃጠሎ በኋላ የተሰራችው ቤተክርስቲያን


ከእሳት የተረፉ መጻህፍት በጥቂቶቹ

 
ይህን የእመቤታችን ተዓምር ይገለጽ እና ምዕመኑም ያውቀው ዘንድ የደብሩ ሰበካ ጉባኤ አስተዳደር ጽ/ቤት እና የአካባቢው ምዕመን አንድ ላይ በመሆን ‹‹ተአምሯን አንቀብርም ›› በሚል አርዕስት ከነደደው እሳት ሳትቃጠል በተዓምር የወጣችው የእመቤታችንን ታቦትና ልዩ ልዩ ንዋየ ቅድሳት ምክንያት በማድረግ ታላቅ ጉባኤና የቅኔ ምሽት በቀጣይ እሁድ ሚያዚያ 13 ቀን 2004 ዓ.ም ከቀኑ 10 ሰዓት ጀምሮ አዘጋጅተዋል፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይ ከነደደው እሳት የተረፉ ንዋየ ቅድሳትን ለምዕመኑ የማሳየት ዝግጅት እንደሚኖረው ለማወቅ ተችሏል፡፡  በመርሐ ግብሩ ላይ ብጹአን ሊቃነ ጳጳሳት ፤ የመንፈሳዊ ኮሌጅ መምህራን ፤ ታላላቅ የቅኔ ምሁራን ፤ የድጓ እና የአቋቋም መምህራንና ዘማሪዎች ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡  እርስዎም በዚህ ጉባኤ ላይ በዕለቱ ተገኝተው በተዓምር ከእሳት የወጡ ታቦታትን እንዲሳለሙ ፤ ልዩ ልዩ ንዋየ ቅዱሳትን በአካል እንዲጎበኙና በረከት አግኝተው እንዲመለሱ በታቦተ ጽዮን ስም ተጋብዘዋል፡፡

ከእሳት የተረፈ መስቀል አንዱ(መሀል ላይ ያለውን ይመልከቱ)
ከእሳት የተረፉ ጥቂት መስቀሎች



በጉባኤው ላይ መገኝት ለማትችሉ በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጪ የምትገኙ እህቶችና ወንድሞች የደብሩ ሰበካ ጉባኤ መርሐ ግብሩን በቪዲዮ በመቅረጽ የሆነውንና የተደረገውን ተዓምራት አይተው ያደንቁ እምነትዎንም ያጸኑ ዘንድ ፤ ተዓምራቱን በመጽሄትና በጋዜጦች በወቅቱ የነበሩትን የአይን እማኞችን ተዓማኒ በማድረግ ለማሰራጨት እንዳሰበም ለማወቅ ተችሏል፡፡

አዲሱን ህንጻ ቤተክርስቲያኑን የሚመለከት
በአሁኑ ሰዓት ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን የተጀመረ አንድ ትልቅ ቤተክርስቲያን በግቢው ውስጥ ይገኛል ለዚህ ቤተክርስቲያን የመሠረት ድንጋይ የተጣለው በአቡነ ጳውሎስ ፕትርክና ዘመን ከአራት አመት በፊት መሆኑን ቦታው ላይ የሰፈረው ጽሁፍ ያመለክታል፡፡ ይህ ቤተክርስቲያን በአሁኑ ሰዓት አዲስ አበባ ውስጥ ካሉት አስርት አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ በዲዛይንም ሆነ በውስጡ  ስፋት በደረጃ ውስጥ የሚቀመጥ ነው፡፡ ከአራት አመት በፊት ሲጀመር የግንባታ ወጪው ከአስራ አንድ ሚሊየን ብር በላይ ይፈጃል ተብሎ ተገምቶ ነበር፡፡ አሁን ላይ በየሳምንቱ ምዕመኑ እጁን ባለማሳጠር የአቅሙን በየሳምንቱ ቢዘረጋም የግንባታው በኮንስትራክሽን እቃዎች ንረት ምክንያት የመዘግየት ሁኔታ ይታይበታል ፤ በአሁኑ ወቅት ትልልቅ ስራዎች ተጠናቅቀው የመጨረሻ ምህራፍ የያዘ ቢመስልም ከፍተኛ ወጪ እንደሚጠብቀው ግን ከባለሙያዎች ለማወቅ ተችሏል፡፡ ደብሩ በዜና ማሕደረ ስብሐት ጋዜጣ ላይ ጥር 21 2006 ዓ.ም እግዚአብሔር ቢፈቅድ ሥራ ተተናቅቆ ታቦተ ሕጉ ለማስገባት አስቧል ፡፡ ምዕመናን ስማችሁን በሰማያዊ መዝገብ ታጽፉ ዘንድ የህንጻ ቤተክርስቲያኗን ግንባታ ከፍጻሜ ለማድረስ ይቻል ዘንድ አቅም በፈቀደ ሁሉ ትብብራችሁ እንዳይለየን ሲል በቤተክርስቲያኒቱ ስም ጥሪውን አስተላልፏል፡፡

በመሰራት ላይ ያለው ቤተክርስቲያን


ለበለጠ መረጃ የደብሩን የስብከተ ወንጌል ኃላፊ በዚህ ስልክ ማነጋገር ይችላሉ ..0912-629177



መርዳት የሚቻልበት መንገድ ከደብሩ አስተዳደር ጋር በመነጋገር ወደፊት እንጠቁማለን

ቸር ሰንብቱ
‹‹ተዓምሯን አንቀብርም››