Friday, April 5, 2013

ኢትኦጵ መጽሔት 1992 ዕትም..


  • “አቡነ ጳውሎስ ከፕሮቴስታንት ተቋም ነው ዲግሪያቸውን ያገኙት፡፡”  አለቃ አያሌው ታምሩ
  • “ፓትርያርክ መሾምና መሻር በሕይወት የመኖር አለመኖር ጉዳይ አይደለም ፤ ፓትርያርኩን(አቡነ ጳውሎስ) የሚያመሰግናቸው እንጂ የሚቃወማቸው ሰው አላጋጠመኝም›› አቡነ ገሪማ
  • “ለቤተክርስቲናችን የአሁኑ መንግሥት ይሻለናል”  አቡነ ገሪማ
  • ‹‹አዎ ይሻላቸዋል …. በአደባባይ ሰው ገድለው መቼ ጠየቃቸው?› አለቃ አያሌው ታምሩ
አለቃ አያሌው ከሰጡት ቃለ መጠይቅ የተወሰደ
 በፓትርያርክ ላይ ፓትርያርክ መሾም አይቻልም ፤ ማንኛውም ቢሆን ለአንድ ፓትርያክ መንበሩ ‹‹እንደ ሚስት የተቆጠረች ናት›› ነው የሚል፡፡ አንድ ሰው በሚስት ላይ ሌላ ሚስት ማግባት እንደማይችል ሁሉ በአንድ መንበር ሁለት ፓትርያርኮች ሊኖሩ አይችሉም፡፡ ይህንን ሁሉም ያውቁታል፡፡ በሕገ-ቤተክርስቲያን ሁለት ራስ በአንድ ቤት የለም ፤ ቤተክርስቲያን የክርስቶስ አካል ናት ፤ አንድ ራስ ነው ያላት ሁለት ራስ የለምና አንድ ቤተክርስቲያን አንድ ፓትርያርክ እንጂ  ሁለት ራስ የላትም፡፡
አቡነ መርቆሬዎስ ከቤተክርስቲያን ሲወጡ ስለ ሕማማቸው እውተኛ መረጃ ለቤተክርስቲያን አልቀረበም ፤ በሽታቸው ተገምግሞ ለስራ ያስችላቸው አያስችላቸው የሚል ጉባኤ አልተከናወነም ፤ ይህ እስካልሆነ ድረስ ተሽረዋል ማለት አይቻልም ፤ ሕጋዊ ዝውውር አልተደረገም ፤ የሳቸው መውረድ የተከታዩ መሾም ተቀባይነት የለውም፡፡
ስለ አብዮታዊ ቤተክርስቲያን
በወቅቱ ከፍተኛ ካድሬዎች ከተሰማሩ በኋላ የቤተክርስቲያቱ አባሎች በጠቅላላ ማለት ይቻላል በእግዚአብሔር ላይ አመጹ ፡፡ አብዮታውያን ነን አሉ ፡፡ ቤተክርስቲያንንም አብዮታዊ ቤተክርስቲያን ብለው ሰየሟት፡፡ የካቲት 10 ቀን 1968 ዓ.ም በቅድስት ማርያም የነበረው ሁኔታ በጊዜው ተገኝቶ ለተመለከተው ሰው ሁሉ ለዚህ እውነተኛ ምስክርነቱን ሊሰጥ ይችላል፡፡ በዚያ ቀን የነበሩ ተናጋሪዎች ሁሉ ‹‹አብዮታዊት ቤተክርስቲያን›› እያሉ ነበር የሚናገሩት ፡፡ አውቀውት አይደለም ጌጥ ስለመሰላቸው ‹‹አብዮታዊ መንግሥት›› የሚል ስለመጣ ‹‹አብዮታዊት ኢትዮጵያ›› የሚል ስለመጣ ይህን እንደ ጌጥ የተሸከሙት ይመስለኛል፡፡
ስለ አቡነ መርቆሬዎስ የፓትርያርክነት ምርጫ
አቡነ መርቆሬዎስ የተመረጡት በግል ጉባኤ እንጂ በቤተክርስቲያን ጠቅላላ ጉባኤ አይደለም፡፡ ለዚህ ተብሎ ዛሬ ሕንጻ ኮሌጅ በሚባለው ኮሌጅ ውስጥ አዳራሽ ተለይቶ ከየሀገሩ የተጠሩት ሰዎች ከከተማ ከሚኖር ምዕመን ጋር እንዳይገናኙ ለብቻቸው እዚያው እንዲሰበሰቡ ተደረገ፡፡ በዶ/ር ተፈራ ወንዴ (የጊዜው የጤና ጥበቃ ሚኒቴር) በእሳቸው ሃላፊነት ምርጫው ተካሄዶ አቡነ መርቆሬዎስ ተመርጠዋል ተባለ፡፡ በዚያው መምራት ጀመሩ፡፡ 
አቡነ ጳውሎስ የሮማው ፖፕ ጋር ስለመሄዳቸው
በመንገድ ሰው አትሂድ አይባልም ፤ መንገድ የማያጋጥመው የለም ፤ መንገድና ገበያ አንድ ላይ ያገናኛል፡፡ በመንገድ እገሌ ከእገሌ ጋር ተገናኝቶ ነበር ተብሎ አይከሰስም፡፡ ክስ የሚመጣው ስርዓት ባለው መልኩ የተፈጸመ እደሆነ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያንና የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ምንም አይነት ሕብረት እንዳኖራቸው በጸሎት ፤ በማዕድ ፤ በጉባኤ እንዳይገናኙ የአበው ውግዘት አለ፡፡ እስከ አሁን ድረስ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ከካቶሊካውያን ጋር አብራ በጸሎት በማዕድ የተሰለፈችበት ጉባኤ የለም፡፡ ከአቡነ ጳውሎስ በቀር፡፡ ሌሎች እንደ አቡነ ጳውሎስ በኦፊሴል ተጠርተው  ፤ በክብር እንግድነት ተገኝተው ፤ በማዕድ በጸሎት ተሳትፈው ኋላ በጉባኤ ተባባሪነታቸው ገልጠው የተገኙበት ጊዜ የለም፡፡ ይሄ ነው አባ ጳውስን ልዩ የሚያደርጋቸው ፡፡ አንደኛ ፕሮቶኮል በሚያውቀው ስርዓት የክብር እንግዳ ሆነው ፤ በካቶሊክ ቤተክርስቲያን ቫቲካን መገኝታቸው ፤ ከፓፓው ጋር በማዕድ በጸሎት መሳተፋቸው  ፤ የማሉበትን የኢትዮጵያ ቤተ መቅደስ በስጋ ወደሙ የገቡት ማህላ አፍርሰዋል፡፡  
አለቃ አያሌው በሰኞ ቀን ስለተሸሙት ጳጳሳት ያሉት
በሰኞ ቀን መሾም የካቶሊክ ስርዓት ነው፡፡ የካቶሊክ አባል መሆናቸውን ያረጋገጡበት ፤ ያሟሉበት ፤ የፈጸሙበትና የመሰከሩበት ነው፡፡ አዎ! በካቶሊክ ልብስ ፤ በካቶሊክ ስርዓት ነው ጳጳሳቱን የሾሟቸው፡፡ የካቶሊኩ ፓፓ በፈቀደ መልኩ እደፈቀደ ነው የሚያደርገው ፡፡ በፈቀደ ቀን በደብዳቤ ይሾማል ፤ አቡነ ጳውስም ቀደም ሲል አባ ተክለሚካኤል የሚባሉትን የቅድስት ስላሴ ሊቀ ስልጣናት የነበሩትን የኢየሩሳሌም ረዳት ሊቀ ጳጳስ እንዲሆኑ በደብዳቤ ሾመዋል፡፡ ይሄም ካቶሊካዊ መሆናቸው የሚያረጋግጥ ምልክት ነው፡፡ አሁን ደግሞ እሁድ ሲሉ ጌታም መሠረት ያደረገውን ፤ በጌታ መመሪያ መሰረት ሐዋርያት በዲስቂሊያ ያዘዙትን ሰለስተምዕት በፍትሀ ነገስታዊ ያጸኑትን ፤ ራሳቸው የተሾሙበት ስርዓት ተላልፈው መሾማቸው ያውም በካቶሊክ ልብስ ሙሉ በሙሉ የካቶሊክ አባል መሆናቸው ያረጋገጡበት ነው፡፡ ይህ የሚያሳፍር ነገር አይደለም?  

ሙሉ ቃለ መጠይቁን በPdf ለማንበብ ይህን ይጫኑ 
Interview By Pdf

3 comments:

  1. ሰላም ጤና ይስጥልኝ እንደምን ዋላችሁ።
    መድኃኔዓለም ይመስገን።

    ውድ ባለገጽ - ፒ ዲ ኤፉን ለመክፈት አስቸጋሪ ነው። ሆኖም ግን ከአንኳር ነጥቦቹ በመነሳት አስተያየቴን እሰጣለሁ።

    በዚህ ዘመን ብዙ መጻሕፍትን የሚጽፉ፣ መጽሐፍ ቅዱስን ሸምድደው በቃላቸው የሚያነበንቡ፣ እጅግ ብዙ ሰው ባለበት ጉባኤ በማራኪ አንደበት ስለመጽሀፍ ቅዱስ የሚናገሩ፣ ብዙ አድማጭ እና አድናቂ ያላቸውን ሰዎች በዓለም ዙሪያ እናያለን። ሁሉም የአምላክን ስም ይጠራሉ፥ ጌታ፣ ጌታ ይሉታል። እግዚአብሔር አምላክ ግን በፍሬያቸው እንድናውቃቸው አንዲት ቀላል የሆነች ምልክትን ነገረን።

    አንድ ሰው በእግዚአብሔር ስም በተናገረ ጊዜ የተናገረው ነገር ከሆነ መልእክቱ ከእግዚአብሔር ነው፤ ካልሆነ ደግሞ ከእግዚአብሔር አይደለም ተብሎ እንደተጻፈ፥ በዘመናችን ካየናቸውና ከሰማናቸው ሰዎች ሁሉ የተናገሩት የሚሆን እንደ አለቃ አያሌው በምድር ላይ ማንም የለም። እንደ አለቃ አያሌው ያሉ በኢትዮጵያ ገዳማት ውስጥ ሊኖሩ ይችላሉ፤ ካሉ ግን የነሱን ምክር ለመስማት አልታደልንም። አንዳንድ አለቃ አያሌውን የሚቃወሙ ሰዎች አሉ። በሰው እእምሮ ውስንነት ማእቀብ ከተያዘ አመክንዮ በመነሳት ሊቁን ቢነቅፉ ፋይዳ ያለው ነገር አይደለም። ቁም ነገሩ ያለው አለቃ አያሌው ተናግረውት የማይፈጸም ነገር ስለሌለ የእሳቸውን መልእክት ከእግዚአብሔር ነው ብለን መቀበል ይኖርብናል። በውድ ሳይሆን በግድ። ሺ ሰባኪ፣ ሺ ደራሲ ይመጣል ይሄዳል፣ አንድ አለቃ አያሌውን ግን አሁን ከየት እናገኛለን? በአጼ ኃይለ ስላሴ ዘመን ያስጠነቀቁትን አዳምጡ። በደርግ ዘመን የተናገሩትን አድምጡ። የራስ ቅል በሚለው ትምህርታቸው ደግሞ ስለአሜሪካ የተናገሩትን አድምጡ። ከ nine-eleven ስድስት አመት በፊት ነበር የተናገሩት። የትርኪምርኪዎቹ የኃሳውያነ መሢህ እጣ ምን እንደሚሆን የተናገሩትን ደግሞ አድምጡ። እግዚአብሔር አምላክ በቅዱስ ያሬድ በኩል የመላእክትን ዜማ እንደሰጠን የመታረሚያ መንገድንም እንዲሁ በአለቃ አያሌው በኩል ሰጥቶን ነበር። ነገር ግን ኢትዮጵያውያን በሙሉ ከባቢሎንን ጠጅ ጠጥተን በመስከራችን ምክንያት ሊቁን ልንሰማ አልፈለግንም። እነሆ አልሰማም ባይን አለንጋ መጣለት።

    ከቃላቸው እኮ የዋዛ ፈዛዛ ነገር የለም። እንዳሉትም አባ ጳውሎስ የተማሩት ፕሪንስተን ሴሚናሪ በሚባል የፕሮቴስታንት መማሪያ ቤት ነው። ፕሪንስተን ሴሚናሪ በኒው ጀርሲ የሚገኝ ፕሪስቢቴሪያን (ፕሮተስታንት) ነኝ ብሎ በግልጽ ማስታወቂያ እራሱን የሚያራምድ የፕሮቴስታንትን እምነት ወደፊት ለማራመድ የተመሠረተ በዚህም ጎዳና የሚጓዝ ትምህርት ቤት ነው። በየትኛውም የፕሮቴስታንት ትምህርት ቤት የሚማር ሰው ከዛ ተቋም የማለፊያ ወይም የመመረቂያ ነጥብ ለማምጣት በእያንዳንዱ የመመዘኛ ወረቀት ላይ የፕሮቴስታንትን እምነት አንጸባርቆ መጻፍ አለበት። ይህን ካላደረገ አያልፍም፣ አይመረቅምም። እግዚአብሔርን በፍጹም ንጽህና፣ በፍጹም እምነት፣ በጾምና በጸሎት የሚለምኑ ቅዱሳን በነበሩባት ኢትዮጵያ የፕሮቴስታንት ስልጡን የሆኑት አባ ጳውሎስ ፓትርያርክ ተብለው መሰየማቸው ምን ያህል አዘቅት ውስጥ እንደገባን የሚያሳይ መጠቆሚያ ነበር። ከፕሮቴስታንት ተቋም መመረቃቸው ብቻ ሳይሆን ሥራቸውም ሁሉ የወጡበትን ተቋም የሚመስል ነበር። በተቀደሰው ገዳም በዋልድባ ላይ ለጥፋት መነሳታቸው፣ በዚህም ምክንያት በእግዚአብሔር ተዓምር ከዚህ ዓለም መቀጨታቸው ሁሉ ሁላችንም ባንድ ላይ የደረስንበትን ጊዜ አመልካች ነው። አሁን የተመረጡት አቡነ ማቴያስን ከሌሎቹ የሚለያቸው ነገር ቢኖር በፕሮቴስታንት በሺታ ያልተለከፉ መሆናቸው ነው። ሆኖም ግን ጥያቄው ቅድስናቸውን በአሜሪካ ፓስፖርት እንደለወጡት ቀርቷልን? ደግሞስ ለዋልድባ ይቆማሉ ነው ወይስ እንደ አባ ጳውሎስ ለፕሮቴስታንት “መብት”? የድጓው ሊቅ እነ አቡነ መርቆሬዎስ ምንም እንኳን ቢገፉም አለቃ አያሌው ቦታዎትን አይልቀቁ እያሏቸው ቦታቸውን ለቀው ወደ ገዳም ተቃራኒ ሄደው፣ ድጓና ጾመ ድጓን በፒያኖና በኦርጋን ተክተው፣ በጎችን በተኩላዎች በነ አባ ውላጤ ዘእንበለ ውላጤ እያስበሉ ኑ በውጭ አገር ሆናችሁ ቤተክርስቲያንን ክፈሉ፤ እኛን ተከተሉ ይሉናል። ቅዱስ ያሬድን ማን ቅዱስ አደረገው የኛ ቅዱስ ቤቶቨን ነው ሲሉን እነ አባ ውላጤን እንዴት ዝም እንላቸዋለን? ኣረ በኃይማኖት ለመጣ ዝምታ የለም። አለቃ አያሌው አባ ጳውሎስን እንዳወገዙ ሁሉ እነዚህን በውጭ አገር ያሉ ኃይማኖት ለዋጮችንም እንዳወገዙ አትርሱ።

    ምስጋና ለእግዚአብሔር።
    ኃይለሚካኤል።

    ReplyDelete
  2. don't you guys know most of our father went to Greek and Russia theology college, which we have some doctine differences. this doesn't mean are converted. so, please don't make it personal

    ReplyDelete
  3. በጣም በሳል አስተያየት ነው። ዛሬ በአሜሪካ ያሉት ጳጳሳት በሰሩት በደል የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ ይከፍሉታል አይቀርም።

    ReplyDelete