Friday, November 21, 2014

ሃና ላይ የተፈጸመው ተግባር የምንኖርበትን ማኅበረሰብ ዝቅጠት የሚያሳይ ነጸብራቅ ነው



ሃና ማለት ይች ናት ፤ በማኅበረሳባችን መካካል በወጡ እኛን በመሰሉ ሰዎች ለ5 ቀናት የአስገድዶ መድፈር ተካሂዶባት ህይወቷን ያጣችው ሃና ፤ እግዚአብሔር ነፍሷን ያሳርፍ ፤ ይህን ከመሰለ  ከእምነታችንና ከባህላችን ያፈነገጠ የረከሰን ተግባር  ወደፊት ላለመስማትም ሆነ ላለማየት ሁላችን ሃላፊነታችንን እንወጣ፡፡ ለቤተሰቦቿና ለጓኞቿ መድኃኒዓለም መጽናናትን ያድልልን፡፡

Thursday, November 20, 2014

ርዕሰ አድባራትና ወገዳማት አክሱም ጽዮን ማርያም በከፍተኛ ጥበቃ ላይ ትገኛለች

ከሳምንት በፊት በተለያዩ ማኅበራዊ ድረ ገጾች ሲስተጋባ የነበረው ‹‹ቃል ኪዳኑ ታቦት ተሰርቋል›› የሚለውን አሉባልታ ጋር በተያያዘ በአካባቢው ማኅበረሰብ በአካባቢው ፖሊስና በፌደራል መንግሥት በተላኩ የደህንነት ሰዎች አማካኝነት በአሁኑ ሰዓት  ርዕሰ አድባራትና ወገዳማት አክሱም ጽዮን ማርያም በከፍተኛ ጥበቃ ላይ እንደምትገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡ 

Friday, November 14, 2014

‹‹ፈጣሪ አምላክ አገራችንንና ህዝቧን ከጥፋት ይታደግ ዘንድ በጸሎት እንትጋ!!›› የፖለቲካ ፓርቲዎች ለኃይማኖት ተቋማት ያቀረቡት ጥሪ

አንድ አድርገን ህዳር 6 2007 ዓ.ም
አገራችን የክርስትናና እስልምና ኃይማኖቶችን በመቀበል ቀደምት በመሆኗ ብቻ ሳይሆን የኃይማኖቶቹ ተቋማት፣አባቶችና ምዕመናን በመከባበርና መቻቻል አብረው በሠላም በመኖር ለዓለም ህዝብ ተምሳሌት መሆናችን የምንኮራበት ነው፡፡ ለዚህም የቤተ እምነቶቹ አባቶች ለምዕመናኑ ያስተማሩት የሞራልና ሥነ-ምግባር እሴቶችና በአብሮነት ላይ የቆመ የአገር ፍቅር ስሜት፣ እነዚህንም እንዲጠብቋቸውና እንዲያከብሯቸው አርዓያ በመሆን ያደረጉት አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነው፡፡
አገራችንና ህዝቧ በተፈጥሮ ሚዛን መዛባት በሚከሰትም ሆነ በአገዛዝ ሥርዓቶች ምክንያት በችግር ውስጥ በሚወድቁበት ጊዜ ሁሉ የእነዚህ ኃይማኖቶች ተቋማትና ምዕመናን መዓቱ እንዲርቅና ምህረቱ እንዲወርድ ፈጣሪያቸውን በጾምና በጸሎት በመለመን/ በመማጸን፣ በሃይማኖታዊ የሞራልና ሥነ ምግባር እሴቶቻቸው መሠረት በመተዛዘን በመረዳዳትና በመተጋገዝ የተገኘውን በመካፈል በአብሮነት ስሜት በርካታ ክፉ ጊዜያትን መሻገራቸው በታሪክ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡

ደብረ ፀሐይ ቍስቋም ማርያም

እንኳን ለቊስቋም ማርያም ዓመታዊ ክብረ በዓል አደረሰን ።

አንድ አድርገን ህዳር 6 2007 ዓ.ም
ቁስቋም ማርያም በደርቡሾች ተቃጥሎ
እንደነበር - 1930 ዓ.ም.
የእመቤታችን በትልቅ የምስጋና አገልግሎት ከሚከበሩ በዓላት መካከል የወርሐ ጽጌ በዓል አንዱና በሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ልብ ውስጥ ጥልቅ የልቦና ፍቅር ያለው የማኅሌትና የቅዳሴ በዓል ነው፡፡ወርሐ ጽጌ በመባል በቤተክርስቲያናችን የሚከበረው ይኽው የምስጋና በዓል ከመስከረም 26 ጀምሮ እስከ ኅዳር 6 ቀን ያለው ጊዜ ሆኖ የእመቤታችንን ስደት የምንዘክርበትና የምናስብበት ጊዜ ነው፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ ስለ ደብረ ፀሐይ ቍስቋም ማርያም ትንሽ ካነበብነው ማካፈል ወደድን……

ደብረ ፀሐይ ቍስቋም ማርያም ጎንደር ከተማ በስተ ስሜን ምዕራብ ወጣ ብሎ በሚገኘው ደብረ ፀሐይ ቁስቋም የተሰራ ቤተክርስቲያን ነው። ደብረ ፀሓይ ቁስቋም በእቴጌ ምንትዋብ 1725 .. እስከ 1738.. ተገንብቶ የተጠናቀቀ ሲሆን በጊዜው 360 መስታዎቶች የነበሩት፣ በቀይና ሰማያዊ ሃር አልባሳት ያሸበረቀ፣ እንደ ደብረ ብርሃን ስላሴ በጥሩ ኪነት የተዘጋጀ፣ ከወርቅና ከብር የተሰሩ የቤተ ክርስቲያን ማገልገያወች የነበሩት፣ በጊዜው የተደነቀ ቤተ ክርስቲያን ነበር። ደብረ ፀሐይ በተመሰረተበት ዘመን የራሱ ጉልት የነበረው ሲሆን ይኼውም እብናት በለሳ እና አርማጭሆ ተሰባጥሮ ይገኝ ነበር፤ ስለሆነም 260 ቀሳውስትን በስሩ ያስተዳድር ነበር፡፡ ከህንጻ ይዘቱ አንጻር በዚሁ ዘመን በምንትዋብ ከተገነባው ናርጋ ስላሴ ጋር ይመሳስል እንደንበር ግንዛቤ አለ።

ከዚህ በኋላ የተፈጠረውን የአገልግሎት መንፈስ እና አንድነት ማንም አይበጥሰውም!!

የማኀበረ ቅዱሳን አስተዋጽኦ ሁለት መልክ አለው፡፡ አንደኛው የሚታየውን ነገር መስራቱ ነው፡፡ ለእኔ ግን ሁሌም የሚገርመኝና ማኀበረ ቅዱሳን ውስጥ እንዳገለግል ጉልበት የሚሆነኝ የማይታየው ነገር ነው፡፡ ይሔ ሁሉ ሰው፣ ይሔ ሁሉ ምእመን፣ ይሔ ሁሉ የግቢ ጉባኤ ተማሪ በአንድነት ስለ ቤተክርስቲያን እንዲመክር፣ እንዲያገለግል ያደረገው ማኀበሩ የፈጠረው የአገልግሎት ፍልስፍና ነው፡፡ ዘር፣ የትምህርት ደረጃ፣ ወንዝ፣ ከሀገር ውጭ፣ ከተማ፣ ገጠር ሳይል ሁሉም አኩል ለቤተክርስቲያን እንዲጨነቅ አድርጓል፡፡ ይህን አስብ ሁሌም ጉልበት ይሰጥሃል፡፡ አሁን የቤተክርስቲያን ጉዳይ የሁሉም ጉዳይ ነው፡፡ ሁሉም ሰው እንደ ቤተክርስቲያን አባቶች እንዲያስብ ፣ እንዲጨነቅ፣ እንዲሟገት እንዲከራከር ፍልስፍናውን/አስተሳሰቡን የፈጠረው ማኀበረ ቅዱሳን ነው፡፡ ከዚህ በኋላ የተፈጠረውን የአገልግሎት መንፈስና አንድነት ማንም አይበጥሰውም፡፡

(ዶክተር ዘርዓየሁ) ከመጽሔተ ተልዕኮ ዘማኀበረ ቅዱሳን ጋር ባደረገው ቆይታ የተናገረው፡፡