Monday, December 31, 2012

ለእርቀ ሰላም የመጡትን ተወካይ በመንግስት የደህንነት ሰዎች አማካኝነት ወደ መጡበት እንዲመለሱ ተደረገ

(አንድ አድርገን ታህሳስ 23 2005 ዓ.ም)፡- የእርቀ ሰላሙ ኮሚቴዎች እርቁ ዳር እንዲደርስ ጊዜያቸውንና ጉልበታቸውን በመሰዋት ከፍተኛ እንቅስቃሴ እያደረጉ መሆኑ ይታወቃል ፤ ቤተክርስቲያን ከነበረችበት መከፋፈል ወደ አንድ እንድትመጣ በሁለቱም ሲኖዶሶች መካከል በመሆን የንግግር መንፈሱ እንዲጀመርና በአባቶች መካከል ያለው ያለመነጋገር እና ያለመወያት መንፈስ እንዲርቅ አድርገዋል፡፡  ከቀናት በፊት ከአሜሪካ የእርቀ ሰላም ኮሚቴውን በመወከል አዲስ አበባ የመጡት ሊቀ ካህናት ኃ/ሥላሴ አለማየሁ በመንግስት የደህንነት ሰዎች አማካኝነት ወደ መጡበት እንዲመለሱ ተደርጓል ፡፡ ከቀናት በፊት የፌደራል ጉዳዮች የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ለፋና ብሮድካስት በሰጡት አስተያየት “መንግሥት በኦርቶዶክስ ተዋህዶ ፓትርያርክ ምርጫ እና እርቀ ሰላሙ ላይ እጁን አላስገባል ፤ በየ ድረ-ገፅ የሚወራው ወሬ ሀሰት ነው ፤ ሕገ መንግሥቱ መንግሥትና እምነትን ስላለያየ መንግስት በእምነቶች ላይ ጣልቃ አይገባል” በማለት ተናግረዋል ፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ ጸሀፊም “መንግስት በመካከላችን ጣልቃ አልገባም ፤ ጭራሹን አልደረሰብንም ፤ የሚወራው ወሬ ሀሰት ነው” በማለት አስረድተዋል፡፡ አቡነ ሕዝቅኤል ለእርቀ ሰላም የመጡት አባት በማን አማካኝነት ከሀገር እንዲወጡ ስለመደረጉ ተጠይቀው ለአሜሪካ ድምጽ በሰጡት መልስ “ መምጣታቸውን እናውቃለን ፤ በአካልም አግኝቼ አናግሬአቸው ነበር ፤ በምን ምክንያት እንደተመለሱ ግን የማውቀው ነገር የለም ፤ ነገ ስለምንሰበሰብ ቅዱስ ሲኖዶስ ይነጋገርበት ይሆናል” ብለዋል፡፡ አሁን ግን እየተደረገ እና እየተወራ ያለው ነገር ምዕመኑን ይባስ ግራ መጋባት ውስጥ እየከተተው ይገኛል፡፡ አባቶቻችን መንግስት ጣልቃ አልገባም ብለው በአደባባይ ሲናገሩ ፤ መንግስት ደግሞ ለእርቀ ሰላሙ የመጡትን አባት ወደ መጡበት ወደ አሜሪካ እንዲመለሱ ቲኬት ቆርጦ እንደሰጣቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡ መንግሥት የቀጣይ ፓትርያርኩን ምርጫ በቅርበት ሆኖ የሚከታተል ኮሚቴ በፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር አማካኝነት እንዳቋቋመ ከወር በፊት መጻፋችን ይታወቃል፡፡ ( ይህን ይጫኑ )አሁን በግልጽ እየታየ ያለው ነገር ቢኖር መንግሥት ከአሜሪካ በሚመጡት አባቶች ወይም በእርቀ ሰላሙ ላይ ፍላጎት እንደሌለው ነው ፤ ይህ የእርቀ ሰላም ጉዳይ ያለ መንግሥት መልካም ፍቃድ ጫፍ የማይደርስበት ሁኔታ እየተስተዋለ ነው ፤  የውጭ ጫናዎች እንዳሉ ሆነው አባቶች ያላቸውን አቅም አሰባስበው የውስጥ ስምምነታቸውን አጠንክረው በአንድ አቋም እና በአንድ ሀሳብ ለቤተክርስቲያኒቱ የተሻለው ሁሉ ቢያደርጉ መልካም ነው እንላለን፡፡ እድሜም ይገፋል ፤ ስልጣንም  ያልፋል ፤ ሞትም ይፈጥናል  ትውልድ ግን ይቀጥላል ፤ በትውልዱ የምትወቀሱበት ስራ እንዳትሰሩ እግዚአብሔር ይርዳችሁ፡፡

Thursday, December 27, 2012

የአቶ ስብሀት ነጋ ቅዥት





  • “ስብሓት ነጋ ቤተ ክርስቲያን ልትበታተን እንደምትችል አስጠንቀቁ!!”  ሀራዘተዋህዶ


(አንድ አድርገን ታህሳስ 18 2005 ዓ.ም)፡- “ስብሀት ነጋ ቤተክርስቲያን እንደምትበታተን አስጠነቀቁ” በማለት አንድ ጽሁፍ ሀራ ዘተዋህዶ ላይ አነበብን ፤ አቦይ ስብሀት  ቤተክርስቲያኒቱ ሃገራዊ ግዴታዋን ስትወጣ የነበረች፣ ለወደፊቱ ታላቅ ሚና ሊኖራት የሚችል ስለኾነች አሁን የት አለች ብለን እናስብ በማለት የአቡነ ጳውሎስ ሞት በኋላ በቤተክህነት አዳራሽ በተቀመጠው ደብተር ላይ ጽፈዋል ፤ ሰውየው አንዳንድ ጊዜ እንደ ነብይ ያደርጋቸዋል ፤ አንዳንዴ ደግሞ በትህምክት ባህር ውስጥ የሰመጡ ትህምክተኛ ሆነው ሳለ “ትምክተኞች” ብለው መናገር ይዳዳቸዋል ፤ አንዳንዴም አይምሮውን ያጣ ሰው ይመስል የሚናገሩትን ነገር አያውቁትም ፤ ሌላም ጊዜ ደግሞ አንደበታቸው ከጭንቅላታቸው የቀደመ አዛውንት ሆነው ያገኙቸዋል ፤ አልፎ አልፎም ፕሮፈሰር መስፍን እንዳሉት “ቂል የያዘው ሰይፍ” አይነት ሃሳብ በማንሳት የማህበረሰብ መነጋገሪያ ሆነው ያገኟቸዋል፡፡ ትልቅ አዛውንት ብለው እንዳያከብሯቸው የወረደ እና የዘቀጠ በ21ኛው ክፍለ ዘመን መነሳት የሌለበት ሃሳብ ሲያነሱ ያገኟቸዋል ፤ ቀላል ብለው እንዳይንቋቸው ደግሞ አምላክ እድሜ ሰጥቶ ሁለት ጸጉር እንዲያወጡ አድርጓቸዋል ፤ ታዲያ እኝን ሰው ምን እንበላቸው ?

Tuesday, December 25, 2012

የዋልድባ አካባቢ እየታረሰ ነው


(አንድ አድርገን ታህሳስ 16 2004 ዓ.ም)፡- የእርቀ ሰላሙ ጉዳይ የዋልድባን ጉዳይ ወደ ኋላ እንዲል አድርጎታል ፤ ምዕመኑ “እርቀ ሰላሙ ካልቀደመ ፓትርያርክ ምርጫው መደረግ የለበትም” ሲል አባቶች ደግሞ የአራት ቁጥርና የስድስት ቁጥር ነገር አስጨንቋቸዋል ፡፡  ከቀናት በፊት ከስኳር ኮርፖሬሽን ያገኝንው የፎቶ መረጃ ቦታው ላይ ምን እየተሰራ እንደሆነ ጥሩ አመላካች ሆኖ አግኝተነዋል ፤ ይህ የምታዩት ፎቶ ከስሩ ይህ ጽሁፍ ሰፍሮበት ይገኛል  “The Gorge of Zarema River where the MayDay Dam will be in place at Wolkayite” ይላል ፡፡

Monday, December 24, 2012

የብጹዕ አቡነ ሕዝቅኤል ወቅታዊ ቃለ መጠይቅ



ዕንቁ ፡- ብፁዕ አባታችን ስለ እድገትና ትምህርትዎ በአጠቃላይ ስለ ራስዎ ይንገሩን ?
ብጹእ አቡነ ሕዝቅኤል፡- የቀድሞ ስሜ መልአከ ምህረት አባ መኮንን ሀብተማርያም ይባላል፡፡ከአባቴ መሪጌታ መኮን ኃይሉና ከእናቴ ወ/ሮ አታላይ ደርሰህ ግንቦት 7 ቀን 1948 ዓ.ም በደበቡብ ወሎ አማራ ሳይንት ልዩ ስሙ ደብረ ብርሃን ለንጓጥ ሥላሴ በተባለው ቦታ ተወለድኩ፡፡ ከሙሉጌታ አበበ እሸቴ ከፊደል እስከ ዳዊት በተወለድኩበት ደብር ከተማርኩ በኋላ በዚያው በአማራ ሳይንት ደራው መድኃኒዓለም ከመሪ ጌታ አፈወርቅ ሳህሉ ቁም ዜማ አቋቋም ፤ ቦረና ቅዱስ ቂርቆስ ደብር ከመጋቤ ምስጥር ደስታ ብዙነህ ቅኔ ከነ አገባቡ ተምሬአለሁ፡፡
ከብጹዕ አቡነ ገብርኤል በ1956 ዓ.ም የዲቁና ማዕረግ ተቀብያለሁ፡፡ ከዚያ ጎጃም መርጡ ለማርያም ከየኔታ ኢሳያስ ቅኔ ከነ አገባቡ ፤ ከመምህር ሀብተ ኢየሱስ መጽሐፈ ነገስት ትርጓሜና የቅኔ መንዶችን ፤ ደብረ መድሃኒት መድኃኒዓለም ከየኔታ አስካል የቅኔ መንገዶችን ከነ አገባቡ ፤ ብቸና ቅዱስ ጊዮርጊስ ከየኔታ ፍሰሐ ወልደሚካኤል ምስጢርና የቅኔ ሙያን አዳብሬያለሁ፡፡ ከየኔታ ፍስሀ ወልደ ሚካኤል በ1969 ዓ.ም በቅኔ መምህርነት ተመርቄአለሁ፡፡

Saturday, December 22, 2012

ማኅበረቅዱሳን ቅዱስ ሲኖዶስ ፮ኛውን ፓትርያርያክ ለመምረጥ የወሰነውን ውሳኔ በድጋሜ እንዲያጤነው ጠየቀ





  •   ቤተክርስቲያን ስድስት ቦታ ብትከፈል አያገባኝም።” አቡነ ቀሌምንጦስ
  •  “ወነአምን በአሐቲ ቤተክርስቲያን” ማኅበረቅዱሳን
  •  ቅዱስ ሲኖዶስ ለእርቀ ሰላሙ ቅድሚያ የማይሰጥ ከሆነ ራሳችንን እናገላለን” በአሜሪካ የኢትዮጵያ አብያተክርስቲያናት ምእመናን
  •  ሀራ ተዋህዶ የተሰኘው የጡመራ መድረክ “ማኅበረቅዱሳን አቋሙን ለወጠ።” የሚለው መሰረተ ቢስ ወሬ ግብ ምን እንደሆነ እያነጋገረ ነው።
  •  “መንግሥት በካርድ ነው የሚመርጠው ፣ ስለዚህ መንግሥት ኃጥያተኛ ነው? እኛ ማን ሆነን ነው በዕጣ ካልሆነ የምንለው? ከመንግሥት እኛ እንበልጣለን?” አቡነ ጎርጎርዮስ

(አንድ አድርገን ታህሳስ 13 2005 ዓ.ም)፡- ባለፉት ሃያ ዓመታት ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት በማበርከት በቅዱስ ሲኖዶስ እና በምእመናን ዘንድ ታማኚነት ያተረፈው ማኅበረ ቅዱሳን ከአቡነ ጳውሎስ እረፍት በኋላ የቤተክርስቲያን አንድነት ቅድሚያ በመስጠት ቅዱስ ሲኖዶስ ለእርቀ ሰላም ቅድሚያ ሰጥቶ እንዲወያይ ለጥቅምቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ በደብዳቤ ማሳወቁ፣ በህትመትና ኤሌክትሮኒክስ ልሳኖቹ ማሳወቁ እንዲሁም የማኅበሩ አመራሮች አባቶችንና ምእመናን መደበኛ በሆኑና ባልሆኑ መንገዶች በማወያየት የበኩሉን ድርሻ ለመወጣት መጣራቸው ይታወቃል።

ቅ/ሲኖዶስ የሠየመው የፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴ ዓለም አቀፍ ተቃውሞ ቀስቅሷል

from :- Addis Admass

  • ‹‹ዕርቀ ሰላሙ ይቅደም›› የሚሉ ጳጳሳት የሲኖዶሱን ውሳኔ አንቀበለውም ብለዋል
  • የላሊበላው ውዝግብ ወደ አላስፈላጊ ግጭት እንዳያመራ ተሰግቷል
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የስድስተኛውን ፓትርያሪክ ምርጫ ዝግጅት የሚመራና እስከ ጥር መጨረሻ ዕጩዎችን የሚያቀርብ አስመራጭ ኮሚቴ መሠየሙ በቤተ ክርስቲያኒቱ ካህናትና ምእመናን ዘንድ ዓለም አቀፍ ተቃውሞ መቀስቀሱ ተገለጸ። ‹‹የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ያገባኛል›› በሚል መርሕ በዋናነት በማኅበራዊ ሚዲያዎችና ብሎጎች እየተገለጸ ያለው ይኸው ተቃውሞ፤ የቤተ ክርስቲያን ሰላምና አንድነት የሚረጋገጥበት የዕርቁ ጉባኤ ‹‹የአባቶች ጉዳይ ብቻ አይደለም፤ ምእመናኑን ያገለለ ሊኾን አይገባም›› በሚል የካህናቱና ምእመናኑ ድምፅ እንዲደመጥ የሚወተውት ነው፡፡

Thursday, December 20, 2012

በተግባር ተቃውሟችንን እንግለጽ



  • እረኞች ሆይ የበጎቻችሁን ምክር ስሙ

(አንድ አድርገን ታህሳስ 12 2004 ዓ.ም)፡-በአሁኑ ሰዓት ፓትርያርክ ለመሾም የሚደረገውን ጥድፊያ “አንድ አድርገን” አጥብቃ ትቃወማለች ፤ለ20 ዓመት የቆየውን መከፋፈል ወደ ሌላ ደረጃ የሚያሻግር ስራ መስራት ከታሪክ ተወቃሽነት አያድንም ፤ ህዝቡ መጀመሪያ እርቀ ሰላሙን ይቅደም የቤተክርስቲያኒቱን አንድነት ይመለስ ከዚያ የፓትርያርክ ምርጫው ይደረስበታል የሚል አቋም በያዘበት በአሁኑ ወቅት አባቶች የምርጫ ህጉን እንደዚህ አጣድፈው የምርጫ አስፈጻሚ ኮሚቴ ለመሰየም የሚያደርጉት ጉዞ አንድም ለራሳቸው ሁለተኛም ለቤተክርስቲያን ሶስተኛም ለምዕመኑ ጥሩ አካሄድ አለመሆኑን አውቀው የያዙትን አቋም ቢያንስ እስከ እርቀ ሰላሙ ፍጻሜ ድረስ ቢያቆዩት መልካም ነው የሚል አስተያየት አለን ፡፡ ይህን አካሄድ ለመቃወም ፌስቡክ እና ዘመናዊ የኤሌክትሮኒክ ሚዲያዎች በቂዎች ናቸው ብለን አናስብም ፤ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የኢንተርኔት ተጠቃሚ ከ500ሺህ ባልዘለለበት ሁኔታ ነገሩን በድህረ-ገጾች እና በፌስቡክ ላይ ተደራሽ ከማድረግ በተጨማሪ ምዕመኑ ሁኔታው አውቆ እና ተረድቶ በግልጽ በአካል የሚቃወምበት ሃሳቡን የሚገልጽበት መንገድ ራሱን በማደራጀት ማመቻቸት መቻል አለበት ፡፡ ኢንተርኔት ኢትዮጵያ ውስጥ 2 በመቶ ተደራሽ አለመሆኑን ልናውቅ ይገባል ፤ ይህ ጉዳይ ከምናወራውና ከምናስበው በላይ ከባድ የሆነ ችግር ይዞብን እንደሚመጣ መገመት መቻል አለብን ፡፡ ባለፈው 20 ዓመት እሮሮ ሳይበቃ ወደ አዲስ እሮሮ መሸጋገር መቻል የለብንም ፤ ሌላ የገማ እንቁላል ሲወረወር መመልከት መቻል የለብንም ፤ ቤተክርስቲያን አሁን የሚያስፈልጋት ከፓትርያርክ ምርጫ በፊት አንድነቷ ነው ፡፡ ባለፉት 16 መቶ ክፍለ ዘመናት ከግብጽ በመቶ አስራ አንድ አባቶች አንድነቷ አደጋ ላይ ሳይወድቅ መመራት ችላለች ባለፉት 40 እና 50 ዓመታት በንጉሰ ነገስቱ እና በወቅቱ በነበሩ አባቶቻችን  የጳጳስነት እና የፓትርያርክነት ስልጣን ወደ ኢትዮጵያውያን ከተመለሰ በኋላ በአንድነት የማያስቀጥላት ደረጃ ላይ ደርሳለች፡፡ 

Tuesday, December 18, 2012

ሽጉጥ ያስመዘዘ የሰበካ ጉባኤ ምርጫ




ከዳዊት
(አንድ አድርገን ታህሳስ 9 2005 ዓ.ም)፡- በመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል  ገዳም (በተለምዶ ግቢ ገብርኤል) እየተባለ የሚጠራው የቤተክርስትያን ቅጥር ውስጥ  በምዕመናን እና በገዳሙ አመራሮች መካከል በተፈጠረው አለመግባባት ድንጋይ መወርወሩንና የገዳሙ ገንዘብ ቤት ኃላፊ የሆኑት መምሬ ንጉሴ የታጠቁት ሽጉጥ መምዘዛቸውን በስፍራው የነበሩ የአይን እማኞች ተናግረዋል፡፡
ምዕመናኑንና የገዳሙን አመራር ለልዩነት የዳረገው ምክንያት የሰበካ ጉባኤ አባላት አመራረጥ ሂደት መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ እንደ መረጃ ምንጮቻችን በ2003 ዓ.ም ወርሃ መጋቢት በተደረገ ምርጫ ዘጠኝ አባላት ያሉት ሰበካ ጉባኤ የገዳሙንና የሃይማኖቱን ቃለ አዋዲ በጠበቀ መልኩ ወደ ስራ ገብተው ነበር፡፡ ከአዲሱ ሰበካ ጉባኤ በፊት የነበሩት የሰበካ ጉባኤ አባላት የገዳሙን ገንዘብ በመመሳጠር ሲዘርፉ በመቆየታቸው የተነሳ የስራ ዘመናቸውን ሳያጠናቅቁ እንዲሰናበቱ ተደርገው ነበር፡፡

‹‹የጳጳሱ ቅሌት›› መጽሐፍ ጸሐፊ በ‹‹የጳጳሱ ስኬት›› መጽሐፍ ይቅርታ ጠየቀ


(አንድ አድርገን ታህሳስ 8 2005 ዓ.ም)፡- የቀድሞ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በነበሩት ብጹዕ አቡነ ሳሙኤል ላይ “የጳጳሱ ቅሌት” በሚል ርእስ መጽሐፍ የጻፈውና ‹‹ተከስ ዘሪሁን›› በተባለ ኅቡእ ስም የሚታወቀው ጸሐፊ  “የጳጳሱ ስኬት” በተሰኝ ሌላ መጽሐፍ  ሊቀ ጳጳሱንና  በቀደመ መጽሐፉ ‹‹አለስማቸውና አለግብራው ተጠቅሰዋል›› ያላቸውን ግለሰቦች በመዘርዘር ይቅርታ ጠይቋል፡፡ በ‹‹ጳጳሱ ቅሌት›› መጽሐፍ ውስጥ የተገለጹት ‹‹ሳሙኤል›› ከሊቀ ጳጳሱ ብጹዕ  አቡነ ሳሙኤል ጋር በምንም መልኩ ግንኙነትየሌላቸው ናቸውያለው ጸሐፊው ‹‹ የሊቀ ጳጳሱን ስም ለማጥፋት ዘመኑን በአስተሳሰብና በተግባር በመዋጀት በሰጡት ከፍተኛ አመራር  ለቤተክርስቲያን ያበረከቱት አስተዋጽኦ ለማጠልሸት  ብሎም ቤተክርስቲያኒቱን ለመናፍቃን አሳልፎ ለመስጠት ያሴሩ ናቸው›› ባላቸው ግለሰቦች ፍላጎት በመገዛቱ መጸጸቱንና ሊቀ ጳጳሱን አቡነ ሳሙኤልን ይቅርታ እንደሚጠይቅ ገልጧል፡፡

ቀድሞ ቤተክርስቲያኒቱን ቀኖና ለማፈራረስ እና ምዕመኑን ከመናፍቃን ጋር ለመቀላቀል የረዥም ጊዜ እቅድ ነድፈው  ሲንቀሳቀሱ የነበሩ የውስጥ አርበኞች መኖራቸው ይታወቃል ፤ አሁንም እንዳሉ እሙን ነው ፡፡ የያዙትን አላማ ለማስፈጸምም በርካታ ገንዘብ በመመደብ ብዙ ቅጥረኞችን በስራቸው በማሰራት የምዕመኑ እይታ ላይ ብዥታ ሲፈጥሩ ተስተውሏል ፤ በውጭ እምቢ ያላቸውን አካሄድ ወደ ውስጥ በማስረግ መድረሻቸው እስኪደርሱ ድረስ ማወካቸው ውስጥ ውስጡን መስራታቸው የማይቀር ነገር ነው ፤ ይህም ግለሰብ ራሱ እንደተናገረው “ቤተክርስቲያኒቱን ለመናፍቃን አሳልፎ ለመስጠት ያሴሩ ናቸው” ባለቸው ሰዎች ሆዳው አምላካቸው በሆኑ ሰዎች አማካኝነት ይህን የስም ማጥፋት ስራ መስራት ችሎ ነበር ፤ ወደ አእምሮው ሲመለስ የሰራው ስራ መልካም ያለመሆኑን በመገንዘብ ይቅርታ ሊጠይቅ ችሏል ፤ እኛም ቤተክርስቲያንን ለተሃድሶያውያን እና ለመናፍቃን አሳልፈን ላለመስጠት ሁላችን እንደ  ምዕመን ልንነቃ ያስፈልጋል፡፡
 ቸር ሰንብቱ

Sunday, December 16, 2012

ቅዱስ ሲኖዶስ ተመራጩ ፓትርያርክ ኢትዮጵያዊ ዜጋ ብቻ እንዲሆን ወሰነ




አዲስ አድማስ ጋዜጣ እንዳገኝነው

  • ዜግነትን መቀየር ለትውልድ ካለው አርአያነት አንጻር ከአንድ በላይ ዜግነት ያላቸው ጳጳሳት በምርጫው አይካተቱም፡፡
  • መንፈሳዊ እና ማኅበራዊ አገልግሎትን በመፈጸም በቂ ችሎታና ልምድ ከማካበት አንጻር የገዳም መነኩሴ የሚለው እንዲወጣ ተደርጓል

(አንድ አድርገን ታህሳስ 8 2005 ዓ.ም)፡- በፓትርያርክ ምርጫ ሕግ ረቂቅ ላይ ውይይት እያካሄደ የሚገኝው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የተመራጩ ፓትርያርክ ዜግነት ኢትዮጵያዊ ብቻ መኾን እንደሚገባው ወሰነ፡፡

Wednesday, December 12, 2012

ዛሬ በአታ ለማርያም ሄጄ ይህን ሰምቼ መጣሁ

(አንድ አድርገን ታህሳስ 3 2005 ዓ.ም)፡- የዛሬዋን ቀን ለማክበር እና ከእመቤታችን በረከት ለመቀበል በታእካ ነገሥት በአታ ለማርያም ቤተክርስቲያን  አቃቢ መንበር ብጹእ አቡነ ናትናኤል ፤ ብጹእ አቡነ አረጋዊ የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የበላይ ጠባቂ ፤ ብጹእ አቡነ ስምኦን የምስራቅ ወለጋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፤ ብጹእ አቡነ ዮሴፍ የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና ከአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራ የመጡ  በርካታ ዲያቆናት ቀሳውስት መነኮሳት እና ምዕመናን በአሉን ለማክበር ቦታው ተገኝተዋል፡፡

Tuesday, December 11, 2012

የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ምእመናን አቡነ ማርቆስ ያደረሱትን አስተዳደራዊና ሃይማኖታዊ በደል ለጠቅላይ ቤተክህነት አቀረቡ

  • መጋቤ ብሉይ አእመረ አሸብር አዲስ አበባ የሚኖሩ የደብረወርቅ ተወላጆችን “አቡነ ማርቆስ ደብረወርቅ ላይ ልማት በመጀመራቸው ተቃውመው ነው የመጡት” በማለት በርካታ ምእመናን በተሳሳተ አጀንዳ ቢያሰባስብም፣ ጉዳዩ ሃይማኖታዊ መሆኑን ስለተረዱ ይቅርታ ጠይቀው ተመልሰዋል።
  • አቡነ ማርቆስ የቀረበባቸው ሃይማኖታዊና አስተዳደራዊ በደል ባሻገር በልማድ “ቅባት”ና ተዋህዶ በመባል ተከፋፍሎ የሚኖሩት የሀገረ ስብከቱ ምእመናን ርስበርሳቸው የሚያጋጩ ሥራዎች በመስራት ላይ መሆናቸው ጠቅላይ ቤተክህነትንና መንግስትን አሳስቧል።
  • አቡነ ማርቆስ የገዟቸው ቤቶች (በአዲስ አበባ ሁለት፣ በግንደ ወይንና ሻሸመኔ) የሃብት ምንጫቸው የቤክህነቱን ትኩረት ስቧል።
  •  ምዕመኑ ከ116 ገጽ የድጋፍ ፊርማ ጋር አቤቱታውን አብሮ አቅርቧል
  • ጠቅላይ ቤተክህነቱ አጣሪ ኮሜቴ ወደ አገረስብከቱ ይልካል።
ክፍል  ሁለት  
(አንድ አድርገን ታህሳስ 2 2005ዓ.ም) አቡነ ማርቆስ በሃገረስብቱ ላይ ያደረሱትን በደል ባለፈው በክፍል አንድ (ክፍል አንድ ለማንበብ ይህን የጫኑ ) ጽሑፍ ማስነበባችን ይታወቃል። ይህን ተከትሎ ርቱዓነ ሃይማኖት የሆኑ የሃገረስብከቱ ምዕመናን በቤተክረስቲያኗ መዋቅር የስልጣን ተዋረድ መሰረት ለጠቅላይ ቤተክህነቱን የአስተዳደር ዘርፍ ምክትል ሥራአስኪያጁን አቶ ተስፋዬ ውብሸት ቅሬታቸውን አቅርበዋል። ከም/ሥራ አስኪያጁ ጋር የምእመናን ተወካዮች ሰፊ ውይይት ማድረጋቸውን ምንጮቻችን ዘግበዋል። በውይይቱ ወቅት ም/ሥራ አስኪያጁ “ የቤተክርስቲያንን ማንነትና ክብር የሚያስጠብቅ እስከሆነ ድረስ ችግሩን የማንፈታበት ምክንያት የለም” ማለታቸው ተሰምቷል። በቀጣይ አጣሪ ኮሚቴ ወደ ሀገረስብከቱ እንደሚላክና ያሉትን ማስረጃዎች ለአጣሪ ኮሚቴ እንዲያቀርቡ አሳስበዋል።

Monday, December 10, 2012

ምርጫ ይቅደም ወይስ እርቀ ሰላም ?




ከዲ/ን አባይነህ ካሴ
(አንድ አድርገን ታህሳስ 1 2005 ዓ.ም) ፡- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የዘወትር ተግባሯ ከሆነው መንግሥተ እግዚአብሔርን ከማስፋፋት ባሻገር በአሁኑ ወቅት ሁለት አበይት የቤት ሥራዎች ከፊቷ ተደቅነዋል፡፡ “እርቀ ሰላም” እና ቀጣይ “የፓትርያርክ ምርጫ” ፡፡ እነዚህ ሁለቱ አጀንዳዎች የሕዝበ ክርስቲያኑን አይንና ጆሮ  ሰቅዘው ይዘዋል፡፡ መረጃው ለደረሳቸው ከበረሀ እስከ ከተማ ፤ ከሀገር ቤት እስከ ውጭ ሀገር ያሉ የቤተክርስቲያን ልጆች ሁሉ የልብ ትርታ ሆኗል ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡
ቅድስት ቤተክርስቲያን ከእነዚህ ከሁለቱ ለየትኛው ቅድሚያ ልትሰጥ ይገባታል ? የሚለው ጥያቄ እየተብላላ ፤ በየአእምሯችን እየተጉላላ ፤ ወደ ህሊናችን እየተመላለሰ ፤ ቀንን ቀን እየወለደ ከዛሬ ደርሰናል፡፡ የጥቅምቱ ቅዱስ ሲኖዶስ የፓትርያርክ የምርጫ ሕግ እንዲዘጋጅ ያሳለፈው ውሳኔ እና በተለያዩ መገናኛ ብዙሃን “አምስት ብሎ ስድስት እንጂ አራት የለም” የሚለው መግለጫ እያነጋገረ ቀጥሏል፡፡ ከዚሁ ጎን ለጎን በአሜሪካ የሚገኙት አባቶች ደግሞ “4ተኛው ፓትርያርክ ወደ መንበራቸው ይመለሱ” ማለታቸው የውይይት አጀንዳ ሆኖ ሰነባብቷል፡፡

Saturday, December 8, 2012

የምሥራቅ ጎጃም ምእመናን በብፁዕ አቡነ ማርቆስ ሃይማኖታዊና አስተዳደራዊ በደል ማዘናቸውንና መማረራቸውን ገለጹ



  •  ሊቀ ጳጳሱ ስድሰት ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በ38 ሰዎች ላይ ሹም ሽርና እገዳ አካሄደዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ግማሽ የሚሆኑት ከወንድም ልጅ ጀምሮ እስከ ወዳጅና የሀገር ሰው የሚዘልቅ የዝምድናና የጎጠኝነት ትስስር ያላቸው መሆናቸው እየተነገረ ነው፡፡
  •   ብፁዕነታቸው በትዕቢትና በንቀት በብዙ ሃይማኖታዊ ጉዳዮች ላይ የተናገሯቸው ንግግሮች ምእመናንን እጅግ አሳዝኖአል።
  • መልክዓ መልክኡ ፤ማኅሌቱ፣ተዓምረ ማርያምም ቢሆንኮ ደብተራ የደረሰው ነው”  አቡነ ማርቆስ
  •  የሀገረ ስበከቱ ካህናትን ውኃ ግድግዳ ላይ መርጨት ብቻ የለመዱ ወንጌል ያልገባቸው ሲሉ ሰንበት ትምህርት ቤቶችንና ማኅበረ ቅዱሳንን ደግሞ “ወንበዴዎች፣ሌባዎች፣አሸባሪዎች” ብለው መሳደባቸውን የደረሰን መረጃ ያመላክታል፡፡
  •  “እኛ የምንሰብከው ዛሬ ጠፍቶ የተገኘውን መስቀል ሳይሆን መስቀሉ ላይ የተሰቀለውን ክርስቶስን ነው” ,...... አቡነ ማርቆስ በዘንድሮ የመስቀል በዓል ላይ የተናገሩት።


ክፍል አንድ

(አንድ አድገን ኅዳር 29/2005 ዓ.ም ) ብፁዕ አቡነ ማርቆስ በ1997 ዓ.ም ከ4 ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በቅዱስ ሲኖዶስ የጵጵስና ማዕረግ የተሰጣቸው አባት ናቸው፡፡ ብፁዕነታቸው ለ 17 ዓመታት ያህል በውጭ ሀገር የቆዩ ሲሆን ወደ ሀገር ቤት-ኢትዮጵያ ከመጡ በኋላ በመጀመሪያ ከ1997 ዓ.ም2001 ዓ.ም የምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ፤ ከ2001 ዓ.ም- 2003 ዓ.ም የአዊና መተክል ዞኖች ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ሆነው ከቆዩ በኋላ የጥቅምት 2004 ዓ.ም ቅዱስ ሲኖዶስን ስብሰባ ተከትሎ በተወሰነው ውሳኔ መሰረት ተወልደው ባደጉበት፣ በተማሩበትና በቅኔ መምህርነት ባስተማሩበት የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው በማገልገል ይገኛሉ፡፡

Friday, December 7, 2012

እርቀ ሰላም ፍቅር



(አንድ አድገን ህዳር 28 ፤ 2005 ዓ.ም)፡- መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል ለሰው ሁሉ ከሚሆነው በቀር ምንም ፈተና አልደረሰባችሁም፤ ነገር ግን ከሚቻላችሁ መጠን ይልቅ ትፈተኑ ዘንድ የማይፈቅድ እግዚአብሔር የታመነ ነው። ትታገሡም ዘንድ እንድትችሉ ከፈተናው ጋር መውጫውን ደግሞ ያደርግላችኋል። የፍቅር እጦት እንጂ ሰውም በወንድሙ ላይ በክፋትና በአመፅ አይነሳምና ቃየል አቤልን በምቀኝነትና በጥላቻ ተነሳስቶ እንደገደለው ሁሉ ዛሬም ብዙ ቃየላውያን በወንድሞቻቸው ላይ በትዕቢት እና በእብሪት ተነሳስተው የሚሞት ስጋቸውን ለመግደል ያሴራሉ። መግደል ለእነርሱ እጅግ የቀለለ ተግባር ነው፤ ቀድመው ህሊናቸውን ገድለዋልና። ነገር ግን ዛሬም አሁንም በዚች ቅጽበትም በንስሃ ለተመለሰ ሁሉ ምህረት አለ። ከጥፋት መንገድ ዘወር ላለ መዳን ይሆንለታል። ነገር ግን እንደቀደመው ጊዜ በክፋትና በተንኮል ለመመላለስ ልቡን ያደነደነ፣ ፍቅርን የገፋ፣ ምህረትን የናቀ፣ ለወገኖቹ መጥፊያ ያሴረ፣ ጥላቻን ያነገበ እርቅን የጠላ ሰው ወይም ቡድን የኋላ ኋላ በታላቅ አወዳደቅ መንኮታኮቱ አይቀርም።

Wednesday, December 5, 2012

ፕሬዝዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ ለብጹዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ወደ መንበራቸው እንዲመለሱ ደብዳቤ ጻፉ


  •  “የጠቅላይ ሚኒስቴር ቢሮ ፤ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፤ የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴርና ለሀገር ውስጥ ጉዳዮች ሚኒስቴር ” ደብዳቤውን እንዲያውቁት የተባሉት መስሪያ ቤቶች
  •  ከስልጣኔ ውጪ ነው ያደረኩት ፤ በችኮላ የተጻፈ ደብዳቤ ሆኖ አግኝቼዋለሁ ፤ በስሜትና በችኮላ የሆነ ነገር ነው ፤ ስለ ሰራሁት ስህተት አቡነ ናትናኤል ይቅርታ አድርጌልሃለሁ ብለውኛል” ፕሬዝዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ
  •  “ይህ የእናንተ ጉዳይ አይደለም አያገባችሁም” አቃቢ መንበር አቡነ ናትናኤል

(አንድ አድርገን ህዳር 27 2005 ዓ.ም)፡-የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን አራተኛ ፓትርያርክ ብጹእ አቡነ መርቆርዮስ ከነሙሉ ክብራቸውና ማዕረጋቸው ወደቀደመ ቦታቸው እንዲመለሱ የሚጋብዝ ከኢትዮጵያው ፕሬዝዳንት ግርማ ወልደ ጊዮርጊስ ደብዳቤ መጻፉ ተሰማ፡፡ 


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ አባቶች መካከል ቀኖና ተጣሰ በሚል ምክንያት በሁለቱ መካከል የተፈጠረውን ልዩነት ለመፍታት በሰሜን አሜሪካው የሰላም ኮሚቴው አስተባባሪነት ሶስተኛውን የእርቀ ሰላም ድርድር ረቡዕ ህዳር 26 ቀን 2005 ዓ.ም በአሜሪካ ዳላስ ውስጥ መጀመራቸው ታውቋል፡፡ ለዚህው እርቀ ሰላም ጉባኤ ከአዲስ አበባው  ፩ኛ/ ብፁዕ አቡነ ገሪማ የልዑካኑ መሪ፣ ፪ኛ/ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ አባል፣ ፫ኛ/ ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ አባል ፬ኛ/ ንቡረዕድ ኤልያስ አብርሃ በጸሐፊነት  የተወከሉ ሲሆን ከአሜሪካው ሲኖዶስ ፩ኛ/ ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ የልዑካኑ መሪ፣ ፪ኛ/ ብፁዕ አቡነ ኤልያስ አባል፣ ፫ኛ/ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ አባል ፬ኛ/ ሊቀ ካህናት ምሳሌ እንግዳ በጸሐፊነት ተወክለዋል፡፡ የዳላሱ ጉባኤ ከመጀመሪያው የዋሽንግተን ጉባኤ ለየት የሚያደርገው አባቶች አብረው ጸልየውና አብረው ማዕድ ቀርበው የጀመሩት ጉባኤ በመሆኑ  ተስፋ ሰጪ ነው ተብሏል፡፡ “ውግዘት” የሚለው አልፈው አብረው በአንድ ማዕድ መቀመጣቸው እና አንድ ላይ ጸሎት ማድረጋቸው በዋነኛነት ሁለቱም ወገኖች ለሰላሙ መሳካት ፍላጎት እንዳላቸው ፤ ቀጥሎም የሰላምና የአንድነት ጉባኤውን ጥረት የሚያሳይ መሆኑ ተገልጿል፡፡ ትላንት ህዳር 26  የተጀመረው የሰላም ጉባኤ አባቶች የሚነጋገሩበት ጉዳይ እና የሚደርሱበት የስምምነት ሃሳብ ምዕመኑ በከፍተኛ ተስፋ የሚጠብቀው ጉዳይ ሆኗል ፡፡ ይህ ደግሞ በዛሬ እና በነገ የሚታይ ውጤት ይሆናል፡፡

Wednesday, November 28, 2012

ሚስጥረኛው መንግስታችን


  • ኢጣልያኖች የምኒሊክን ሐውልት ሲያወርዱ የተመለከተ አንድ ትንሽ ልጅ ጮሆ አለቀሰ፡፡ ኢጣልያኖችም ለምን እንደጮህና እንዳለቀሰ  ልጁን ጠየቁት፡፡ልጁም የንጉሴን ምስል ስላወረዳችሁ ነው አላቸው፡፡ ኢጣልያኖችም ከሙሶሎኒ ሌላ ንጉስ እንደሌለ ነግረውና ገርፈው አባረሩት…” ኒውዮርክ ታይምስ የካቲት 13 ቀን 1937 ዓ.ም እትም
(አንድ አድርገን ህዳር 20 ቀን 2004 ዓ.ም)፡-  ለዚች ሀገር እጅጉን ብዙ ውለታ ከዋሉት የሀገር መሪዎች ግንባር ቀደም መሪ ዳግማዊ አጼ ምኒሊክ ናቸው ቢባሉ ማጋነን አይሆንም፡፡ እንደ አለመታደል ሆኖ ሚኒሊክ ከጂቡቱ አዲስ አበባ ድረስ ተዘርግቶ ማየት የፈለጉት ከ10 ዓመት በላይ በርካታ ዋጋ የከፈሉበትና የደከሙበት  የባቡር ዝርጋታው በርካታ መቶ ኪሎ ሜትሮችን አቋርጦ የአዲስ አበባ ምስራቅ መውጫ  አቃቂ ከተማ እንደደረሰ ህይወታቸው እንዳለፈ ታሪክ ይናገራል ፡፡ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትርም የዛሬ 100 ዓመት ሚኒሊክ ሊያዩት ያሰቡትን ባቡር እሳቸውም ማየት ቢመኙትም ስራው በእሳቸው ዘመን ተጀምሮ ስራው ሳይጠናቀቅ  ለህዝቡ ሚስጥር በሆነ ህመም ህይወታቸው ሊያልፍ ችሏል፡፡ የሚኒሊክ ሞት ህዝቡን ክፉኛ ይረብሸዋል ሀገሪቱ ላይም አለመረጋጋት ያመጣል ተብሎ ስለታሰበ  ከሞቱ በኋላ ከ1902 -1906 ዓ.ም ድረስ   ሞታቸው ለህዝብ ሚስጥር ነበር በማለት ታሪክ ይነግረናል ፤ የጠቅላይ ሚኒስትር የአቶ መለስ ዜናዊም  ህዝቡ ነሐሴ 15 2004 ዓ.ም  አረፉ ተብሎ ቢነገረውም ፤ ሌሎች ጉዳዩን በቅርብ እናውቃለን የሚሉ ሰዎች ከሞቱ 40 ቀን አልፏቸው ሞታቸው ይፋ እንደወጣ ይናገራሉ፡፡

Tuesday, November 27, 2012

በእንተ ሐውልት

From :- Abel Wabella

ለአንዳንድ ኦርቶዶክሳውያን
(አንድ አድርገን ህዳር 19 ፤ 2005 ዓ.ም)፡- የሰማዕቱ አቡነ ጴጥሮስን ሐውልት መነሳት አስመልክቶ ጥቂት ያሳዘኑኝ ጉዳዮች አሉ፡፡ የመጀመሪያውሐውልቱ መነሳቱ ካልቀረ ቢነሳ ችግር የለውም” የሚለው ነው፡፡ ለኔ እንደሚገባኝ እንዲህ ማለት አቡኑ የከፈሉትን መስዋዕትነት ማቃለል እና ዋጋ ማሳጣት ነው ፡፡ ይህን የምልበት ምክንያት መጀመሪያ ስርዓቱ (ሕወሓት መር) ቤተ ክርስቲያኒቷን ሆን ብሎ ከስሯ ለመንቀል እንደሚንቀሳቀስ የታወቀ ነው፡፡ ከትጥቅ ትግል እስካሁን ድረስ ይህ አቋሙ አልተለወጠም ፤ ትላንት ደብረ ዳሞ ገብተው ቤተ ክርስቲያኒቷን እንዲሰልሉና እንዲሰነጥቁ የሐሰት መነኮሳት እያሰለጠነ ሲያሰርግ የነበረው ስብሐት ነጋ ዛሬ ደግሞ ትልቁ ስኬታቸው የኦርቶዶክስ እና የአማራ(አማራ የሚባል ነገር?) “የበላይነት”(quote unquote ) ማስቀረት እንደሆነ በድፍረት ተናግሯል፡፡ ይህ የሚያሳየው ስርዓቱ በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ የጠነከረውን በትር ቤተ ክርስቲያኒቷ ላይ እንደሚያሳርፍ ነው፡፡ ስኳር ፋብሪካ ሲባል ተነስቶ ዋልድባ ላይ መንገድ ሲባል ደግሞ ተነስቶ የሰማዕቱ ሐውልት የሚታይ ከሆነ ለምን ? ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ በሰለጠነው አለም የአንድ ግለሰብ መኖሪያ አከባቢ አዲስ ነገር ሲሰራ  የሚሰራው ነገር በሰውዬው የወትሮ እንቅስቃሴ፣ አስተሰሳሰብ ልማድ ላይ ያለው ተጽእኖ ታይቶ በንድፍና በሞዴል ቀርቦለት የግል አስተያየቱን እንዲሰጥ ይጠየቃል፡፡ የአንድ ግለሰብ፣ የአንድ ነፍስ፣ የአንድ ንፋስ መብት! እኛ ግን ብዙ ሚሊዮኖች ሳለን እንደማንኛውም ተራ ዜና፣ እንደ ማንኛውም የሐማስ ሮኬት ከሬዲዮ መስማታችን እጅግ ያሳዝናል፡፡ እውነታው ይህ ሆኖ ሐውልቱ እንደማንኛውም ድንጋይ እናነሳዋልን ሲሉን ተሸቀዳድመንየሚመለስ ከሆነ” ብለን እሺ ማለታችን  እጅግ የሚያሳፍር ነው፡፡