Wednesday, November 28, 2012

ሚስጥረኛው መንግስታችን


  • ኢጣልያኖች የምኒሊክን ሐውልት ሲያወርዱ የተመለከተ አንድ ትንሽ ልጅ ጮሆ አለቀሰ፡፡ ኢጣልያኖችም ለምን እንደጮህና እንዳለቀሰ  ልጁን ጠየቁት፡፡ልጁም የንጉሴን ምስል ስላወረዳችሁ ነው አላቸው፡፡ ኢጣልያኖችም ከሙሶሎኒ ሌላ ንጉስ እንደሌለ ነግረውና ገርፈው አባረሩት…” ኒውዮርክ ታይምስ የካቲት 13 ቀን 1937 ዓ.ም እትም
(አንድ አድርገን ህዳር 20 ቀን 2004 ዓ.ም)፡-  ለዚች ሀገር እጅጉን ብዙ ውለታ ከዋሉት የሀገር መሪዎች ግንባር ቀደም መሪ ዳግማዊ አጼ ምኒሊክ ናቸው ቢባሉ ማጋነን አይሆንም፡፡ እንደ አለመታደል ሆኖ ሚኒሊክ ከጂቡቱ አዲስ አበባ ድረስ ተዘርግቶ ማየት የፈለጉት ከ10 ዓመት በላይ በርካታ ዋጋ የከፈሉበትና የደከሙበት  የባቡር ዝርጋታው በርካታ መቶ ኪሎ ሜትሮችን አቋርጦ የአዲስ አበባ ምስራቅ መውጫ  አቃቂ ከተማ እንደደረሰ ህይወታቸው እንዳለፈ ታሪክ ይናገራል ፡፡ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትርም የዛሬ 100 ዓመት ሚኒሊክ ሊያዩት ያሰቡትን ባቡር እሳቸውም ማየት ቢመኙትም ስራው በእሳቸው ዘመን ተጀምሮ ስራው ሳይጠናቀቅ  ለህዝቡ ሚስጥር በሆነ ህመም ህይወታቸው ሊያልፍ ችሏል፡፡ የሚኒሊክ ሞት ህዝቡን ክፉኛ ይረብሸዋል ሀገሪቱ ላይም አለመረጋጋት ያመጣል ተብሎ ስለታሰበ  ከሞቱ በኋላ ከ1902 -1906 ዓ.ም ድረስ   ሞታቸው ለህዝብ ሚስጥር ነበር በማለት ታሪክ ይነግረናል ፤ የጠቅላይ ሚኒስትር የአቶ መለስ ዜናዊም  ህዝቡ ነሐሴ 15 2004 ዓ.ም  አረፉ ተብሎ ቢነገረውም ፤ ሌሎች ጉዳዩን በቅርብ እናውቃለን የሚሉ ሰዎች ከሞቱ 40 ቀን አልፏቸው ሞታቸው ይፋ እንደወጣ ይናገራሉ፡፡

 “በአሁኑ ሰአት መንግስት ሀገሪቱን በ11.2 በመቶ ላለፉት 9 አመታት በኢኮኖሚ እንድታድግ አድርጌአለሁ ፤ ይህ እድገት ቀጣይነት እንዲኖረው ለማስቻል የ5 አመት የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ አውጥቼ እየተንቀሳቀስኩኝ እገኛለሁ” እያለ በመንግስት እና በግል መገናኛ ብዙሀን መናገር ከጀመረ ሰንበትበት ብሏል ፡፡ ከአመታት በኋላ እደርስበታለሁ ያለው እቅድ አንዱ የመንገድ መሰረተ ልማት መሆኑ ይታወቃል ፤ በአሁኑ ጊዜ የገጠር ቀበሌዎችን ከዋና መንገዶች ለማገናኝት ከፍተኛ ስራ እየሰራ ይገኛል ፡፡ በባቡር መሰረተ ልማትን በተመለከተም ሀገሪቱን ከባቡር ቴክኖሎጂ ጋር የዛሬ 100 ዓመት ያስተዋወቁት ዳግማዊ ምኒሊክ  በኋላ ሀገሪቱን በባቡር መስመር ለማገናኝት ስራውን ጀምሮታል ፡፡ የባቡር መስመሩ መጀመሪያ ትግራይን ከሱዳን ፤ ትግራይን ከኮምምቦልቻ እና ከአዋሽ እንዲሁም ከጂቡቲ እንዲያገናኝ ተደርጎ በ1998 ዓ.ም የተነደፈ ቢሆንም ፡፡ ከጂቡቲ የሚነሳው የባቡር መስመር በአዋሽ አድርጎ ኮምቦልቻን አቋርጦ ትግራይ ከደረሰ በኋላ ወደ ሱዳን ይሻገራል ተብሎ ይታሰባል ፡፡ ለምን መጀመሪያ ይህ መስመር ተመረጠ ? ትግራይስ ለምን መዳረሻ ሆነች? ቀጣዩስ መስመር የደቡቡ ወይስ የምዕራቡ የሀገሪቱ ክፍል ? ብለው ቢጠይቁ “ሚስጥር” ነው ይባላሉ፡፡ በወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ከጂቡቲ በአዋሽ በኮምቦልቻ አድርጎ ሱዳን የሚገባውን ባቡር በዚያ የሆነበትን ምክንያት  ሲናገሩ የኮምቦልቻን ከተማ የኢንደስትሪ መንደርነትን እንደ ምክንያት አስቀምጠው ነበር ፡፡ ይህን ሲናገሩ “ሳታማህኝ ብላ” የሚለው ሀገር በቀል ብሂልን ትዝ አስብለውናል፡፡  ይህም ፕሮጀክት ቢሆን ህዝብ ያልመከረበት ባለስልጣኖቻችን መክረው በሚስጥር የጨረሱት ጉዳይ ነው ፡፡ ሚስጥረኛው መንግስታችን ሀገሪቱ ላይ የሚደረጉትን መሰረተ ልማቶች ሁሉንም በሚስጥር ማከናወኑን ከጀመረ ሰነባብቷል፡፡ ለዘመናት ትውልድ ሲዘፍንለት የነበረው የአባይ ግድብን ለመስራት ሲታሰብ በከፍተኛ ሚስጥር የያዘው ጉዳይ ነበር ፡፡ የተለያዩ የሀገሪቱን ከተሞች የባህር ወደብ ካላቸው ሀገሮች ጋር ለማገናኝትም ሲታሰብ ጉዳዩ ሚስጥር ነበር ፡፡ በ1992 ዓ.ም ፕሮጀክቱ ተሰርቶ እንደተጠናቀቀ የሚታወቀው በዋልድባ ላይ የሚሰራውን የስኳር ልማት ጉዳይም የሚመለከታቸው አካላት ማለትም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፤ የዋልድባ ገዳም መነኮሳት እና ለአካባቢው ነዋሪዎች ፕሮጀክቱ እስኪጀመር ድረስ ፕሮጀክቱ ሚስጥር ነበር ፡፡ ይህ ጉዳይ በጊዜው የትግራይ ክልል መስተዳደር ከነበሩት ባለስልጣን  ጀምሮ በተዋረድ ያሉ ሰዎች በአካባቢው ላይ ለመስራት የታሰበውን የስኳር ፕሮጀክት በሚስጥር  እስከ ፕሮጀክቱ ውልደት 2004 ዓ.ም ድረስ ይዘውት ቆይተዋል፡፡
ባለፈው ሀምሌ 2004 ዓ.ም ህይወታቸው ከዚህ ዓለም ያለፈው የአቶ መለስ ዜናዊ የጭንቅላት ህመምም ለህዝቡ  ሚስጥር ነበር ፡፡ አቶ መለስ በህመም ሳሉ የሄዱበት ሀገር ፤ የሚታከሙበት ሆስፒታል ፤ የህመሙ አይነት እና መሰል ጉዳዮች ሁሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ብሎ ለመረጣቸው ህዝብና ለተወካዮች ምክር ቤት አባላት ሚስጥር ነበር ፡፡ በዚያን ጊዜ አቶ በረከት ስምኦን ስለ ሁኔታው ለመገናኛ ብዙሀን ሲናገሩ ከትግል ጊዜ አንስቶ በሚስጥር የመያዝ ባህል በድርጅቱ ውስጥ እንዳለ እና ይህም ሚስጥር እንደሆነ ጠቆም አድርገው አልፈዋል ፡፡ በአሁኑ ሰዓት ደግሞ አዲስ አበባን ከ34 ኪሎ ሜትር በላይ ይሸፍናታል የተባለው የባቡር መንገድ ስራው በባቡር ኮርፖሬሽንና በቻይናው ካምፓኒ አማካኝነት ከተጀመረ ወራት ተቆጥሯል ፡፡ ይህ የባቡር ስራን በሚመለከት የአቡነ ጴጥሮስ ሐውልት እንደሚነሳ እና ከግንባታው በኋላ ሐውልቱ ተመልሶ እንደሚተከል ጊዜው እስኪደርስ ድረስ መንግሥት በውስጡ የያዘው ለህዝቡ ሚስጥር ነበር ፤ በአሁኑ ሰዓት የሚሰራውን የባቡርን ስራ በተመለከተ ማንም እንዲህ ነው ብሎ መናገር አይችልም ፤ ለምን ሌላ ሐውልቶቹን የማይነካ አማራጭ የባቡር መንገድ እንዳልታሰበ? የአቡነ ጴጥሮስ ሐውልት መቼ እንደሚነሳ ? ማን እንደሚያነሳው ? መንገዱ ተሰርቶ እስኪያልቅ የት እንደሚያርፍ ? ማንስ በኃላፊነት ቦታው ላይ እንደሚመልሰው?  በሐውልቱ ላይ አንዳች ችግር ቢፈጠር ማን ኃላፊነት እንደሚወስድ ? ሐውልቱን ያነሳሉ የተባሉት በሙያው የብዙ አመት የስራ ልምድ አላቸው ተባሉት አውሮፓውያንና የቴክኒክ ኮሚቴው ስብጥር ምን እንደሚመስል? ፤ ከምድር ባቡር ፤ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፤ ከባህልና ቱሪዝምና ከአዲስ አበባ መስተዳደር ምን አይነት ኮሚቴ ለማቋቋም እንደታሰብ  ወይም እንደተቋቋመ ?  ፤  ከመንግስት ውጪ ይህን ሚስጥር ማወቅ የሚችል የለም ፡፡ እኛም ከተኛን ቆይተናል ቀስቃሽ ከሌለ በስተቀር ከተኛንበት መንቃታችንን እንጃ….
የምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ሥራ አስኪያጅ ለቪኦኤ እንደተናገሩት ከሆነ ቁፋሮ ከሚኒሊክ ሐውልት በጣም በአጭር ርቀት ላይ ወደ ታች ከ20 ሜትር ያላነሰ እንደሚቆፈር ተናግረዋል ፤ ቁፋሮውም ከቀናት በኋላ ለማስጀመር በአሁኑ ወቅት ሙሉ የሚኒሊክን አደባባይ በቆርቆሮ የማጠር ሥራ ተሰርቷል ፤ በቁፋሮ ወቅት ሐውልቱ ላይ ምንም አይነት ጉዳት እንደማያሰጋው ተናግረዋል ፤ በቁፋሮ ወቅት የሚኒሊክ ሐውልት ምንም ጉዳት እንደማይደርስበት ማን ኃላፊነት ይውሰድ ? ሐውልቱን እንጂ አጥሩን እንደሚነካው ምልክት ሰጥተዋል ፤ የባቡር መስመሩ ጫፍ እና የምኒሊክ ሐውልት ከ5 ያነሰ ሜትር እንደማይራራቁ ምልክቶች እየታዩ ናቸው፡፡ በቁፋሮ ወቅት የሐውልቱን መሰረት አያናጋውም ማለት አይቻልም ፤ ከ5 ሜትር ባነሰ ርቀት የሚዳምጥ ሮሎ ሐውልቱ ላይ የሚፈጥረው ጉዳት አይኖርም ማለትም ይከብዳል፡፡  መንግሥት ሐውልቱ “ምኒሊክ” ሆኖበት እንጂ አያነሳውም የሚል እምነት የለንም ፡፡ አሁንም በሁለቱ ሐውልቶች ላይ ሚስጥራዊነቶች እየበዙ እየሄዱ ይገኛሉ፡፡ ሥራው አይሰራ የሚል ጭፍን አመለካከት የለንም ፤ እነዚህ ሐውልቶች የሀገርና የህዝብ እስከሆኑ ድረስ መንግሥት እነዚህ አካባቢ ለሚሰራቸው ስራዎች ሁሉ ህዝቡና የሚመለከታቸው ተቋማት በግልጽ ውይይት ሊያደርጉበት ይገባል፡፡ ህዝብ ለሚጠይቀው ጥያቄ ትክክለኛ መልስ የመስጠት ኃላፊነት የመንግሥት ነው፡፡ ለ30 ደቂቃ ለዜና ግብአት የሚሆን የኃላፊዎች ቃለ መጠይቅ ስለ ሐውልቶቹ ሙሉ መታመኛ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ ከተጠያቂነት ለመዳን ሲባል ለጊዜው የሚደረግ ሽፍንፍን ስራ የትም አያደርስም ፡፡ አሁን ለእኛ “የአቡነ ጴጥሮስ  ሐውልት ተነስቶ ወደ ቦታው ይመለሳል ፤ የእምዬ ምኒሊክ ሐውልት ደግሞ አይነሳም” ማለት አጥጋቢ መልስ አይደለም ፡፡ ይህ እንኳን እንዴት ሚስጥር ይሆንብናል?
የንጉሴን ምስል ለምን አወረዳችሁት
አዲስ አበባ ከተማ ያለውን የዳግማዊ ምኒሊክ ሐውልት ያሰሩት ልጃቸው ንግሥት ዘውዲቱ ናቸው፡፡ ሐውልቱ የተሰራው ጀርመን ነው፡፡ የተሰራውም ሐርቲን በተባለ ጀርመናዊ ነው፡፡ ሐውልቱ  ተመርቆ ለሕዝብ ለመጀመሪያ ጊዜ የተገለጠው ጥቅምት 22 ቀን 1923 ዓ.ም ነው፡፡ ኢጣልያን የአዲስ አበባ ከተማን እንደያዘ ሐምሌ 4 ቀን 1928 ዓ.ም የምኒሊክ ሐውልትካለበት ቦታ ወርዶ ተቀብሮ ነበረ፡፡ ነጻነት ከተመለሰ በኋላ ሐውልቱ ከተቀበረበት ወጥቶ እንደገና በድሮ ሁኔታ ቆመ ፤ እንደገና ለሁለተኛ ጊዜ ሚያዚያ 27 ቀን 1934 ዓ.ም ተመረቀ፡፡ ኒውዮርክ ታይምስ ኤንድ ኢትዮጵያን ኒውስ የተባለው ጋዜጣ  የካቲት 13 ቀን 1937 ዓ.ም ባወጣው እትሙ “… ኢጣልያኖች የምኒሊክን ሐውልት ሲያወርዱ የተመለከተ አንድ ትንሽ ልጅ ጮሆ አለቀሰ፡፡ ኢጣልያኖችም ለምን እንደጮህና እንዳለቀሰ  ልጁን ጠየቁት፡፡ልጁም የንጉሴን ምስል ስላወረዳችሁ ነው አላቸው፡፡ ኢጣልያኖችም ከሙሶሎኒ ሌላ ንጉስ እንደሌለ ነግረውና ገርፈው አባረሩት…” ልጁም በዚህ ድንጋጤ ከጥቅምት ወር ጀምሮ ታሞ ተኝቷል…” በማለት ጽፏል፡፡(አጤ ምኒሊክ መጽሀፍ ከጳውሎስ ኞኞ ፤ ገጽ 499)  እኛስ መቼ ይሆን ለምን? ብለን ለመንግሥትን በአደባባይ ጥያቄ የምናቀርበው?  
በስተመጨረሻም ታሪክን ፍቆ ታሪክ ለመስራት በሚያስብል መልኩ በትግራይ ክልል  ተምቤን – አብዪአዲ የሚገኘውና በጀግናው ራስ አሉላ አባነጋ ስም ተሰይሞ የቆየው የሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ስያሜው ተቀይሮ በመለስ ዜናዊ ስም እንዲሰየም ተወስኗል ፤የራስ አሉላ ስም ተሰርዞ « መለስ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት » ተብሎ ተሰይሟል ፤ በሌላም በኩል በመቀሌ ከተማ ፒያሳ አካባቢ የአፄ ዮሃንስን መታሰቢያ ሃውልት ለማቆም ተጀምሮ የነበረው እንቀስቃሴ እንዲቆም መደረጉን ታውቋል ፤ ባለፈው አመት ከህዝብ በተዋጣ ገንዘብ ሓውልቱን ለማቆም የመሰረት ድንጋይ ተጥሎ እንደነበር ይታወቃል፡፡

4 comments:

  1. Very quickly this web site will be famous amid all
    blogging and site-building users, due to it's good articles
    Feel free to visit my site :: mac baren cube

    ReplyDelete
  2. Heya i am for the primary time here. I found this board and I to find It truly helpful
    & it helped me out a lot. I hope to present something back and help others like you aided me.
    My web page :: amber leaf

    ReplyDelete
  3. ታሪክ አፍራሾች ለመሆናቸው ዛሬ ስላልጀመርሩት ሁሉም ኢትዮጵያዊ የሀገሩን ክብር ይየሃማኖቱን ታሪካዊ ጽናት ተሞርክዞ ያላ ልዩነት ቅርሱን ማስጠበቅና በትላቻና በታሪክ አፍራሽነት የመጡበትን የወገን ጠላቶች በጽናት በግምባር መግጠም እንጂ በወረቀትና በየቤታችን ሆነን ማማረርና መቆጨት ኃላፊነት መወጣት ስላልሆነ ይህን ጉዳይ መላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ አማኞች በቤተክርስቲያኑ ያሉትን አባቶች እዚህን የታሪክ ውድመት ተጠያቂነት ስላላእባቸው እንድ አቡነ ጴጥሮስ መስቀላቸውን ይዘው ታቦት አስቀድመው የዚህ የሀገር ታሪክ አጥፊ ስብስብ በመገዘት ተግባሩን ማቆም ኃላፊነት አለባቸው፡ እንዲሁም በስራቱ በሆድ አደርነት ያሉ ወገኖች ካለፈ በኋላ ከመቆጨትና ከተጠያቂነት ለመዳን ከህዝቡ ጋር በማበር ተግባሩን ማቆም ይጠበቅባቸዋል፡ ሕዝቡም ከደረሰበት ሶቆቃና መከራ ከረሃብና እርዛት ካለበት የቁም እስር ራሱን ለመፍታት በጎሳ ባማንነት ሳይለያይ ከፍርሃት ወጥቶ በትባት በጀግንነት ታሪኩን ማስጠባቅ ክብሩንና ማንነቱን ማሳየት ይኖርበታል፡

    ReplyDelete
  4. የተሰጠውን አስተያየት የማይለተፍ ከሆን እውነትን እስካላወታችሁ እሚነገር መነገር እንዳለበት እያወቃችሁ እናንተም ከምታደርጉት ማንናውም ዘገባ በእርግጠኝነት ትክክል እንዳልሆነ ካመናችሁበት የሰተሁትን አስተያየት ከጻፋችሁት የመንግስት ሚስትራዊ አስተዳደር የተልየ ስላልሆነ አሁንም ቢሆን የኢትዮፕያ ሕዝብ በፍርሃት ቆፈን በመሸሽብሸቡ አንድነትና ማንነቱን በማሳየት ይህንን ታሪክ ደላዥ አፍራሽ ሰአት በጽናት መታገል እንጂ በድህረገጽ በማጻፍና በማማረር ኢሓዴግን ማሸነፍ አይቻልም፡ ደግሞ ደጋግሞ የሚደረገው በልማት ስም በታሪክና በቅርስ ላይ የሚያደርገው እንቅስቃሴ ምንም አይነት የአቋም እንቅስቃሴ ለማሳየት ሆነ በአንድነት እንደማንቆም የታዘበው ስላለ መሆኑን ተረድተን በሀገር የመጣውን ጥፋት በልምምጥ ሳይሆን በግምባር ስንገትመው ብቻ ነው፡ እሰተሁት አስተያየት አባቶችም የዚህ የታሪክ ተተያቂዎች ናቸው ምክንያቱም የገቡበትን አምላካዊ ቃልኪዳን ለስጋዊ ሲሉ መንፈሳዊነታቸውን አጥተዋል ይህ ደግሞ ሃሜት ሳይሆን በቤተክርስቲያናችን ላለፉት ሀያ አንድ ዓመታት እየተየ ያለ በመሆኑ የሚደበቅ አይደለም አስተያየት ውይም ትችት ገምቢነት ስላለው በግልጽ ስህተትም ካለ መታረም የሚችለው ሁሉም አምብቦ ትረድቶ የሚሰተው ምላሽ በመሆኑ፡ እስሜት የፍርሃት ካለበት ገምቢ ሊሆን አይችልም፡ አስተያየት የተለያየ ድብቅ ነገሮችን ለማግኘት የሚያስችል ፋለግ ነው፡ በዚህ መሰረት ሁሉንም ማስተናገድ ይገባችኋል----------------- አመሰግናለሁ

    ReplyDelete