Tuesday, August 16, 2011

«ወዮልኝ፣»


«ወዮልኝ፣»

           
         ድካማቸውን አይተው፥ ጉድለታቸውን አስተውለው፥ ራሳቸውን የሚገሥጹ፥ በራሳቸው የሚፈርዱ ሰዎች ብፁዓን (ንዑዳን፥ ክቡራን) ናቸው። ያለፈውን ዞር ብሎ በማየት፥ የቆሙበትን በማስተዋል፥ ወደፊት ሊመጣ የሚችለውንም አሻግሮ በ መመልከት፦ «ወዮልኝ፤» ብሎ ራስን ማስጠንቀቅ መንፈሳዊነት ነው። በተሰጣቸው ጸጋ ሳይኰፈሱ ፥ በአገልገሎት ብዛት ሳይጋረዱ፥ ወደ ውስጥ ማየት የአእምሮ መከ ፈት ነው። «አይገባኝም ፥ ሳይገባኝ ነው፤» ማለት የእግዚአብሔርን ቸርነት መግለጥ፥ ለጋስነቱን መመስከር ነው። በምድርም በሰማይም (በሰውና በእግዚአብሔር ዘንድ) ትሑት ሰብእና፥ ቅን ልቡና ይዞ መገኘት ነው። «ወዮልኝ፤» ያለ ታላቁ ነቢይ ኢሳይያስ ነው። እርሱም ከዓበይት ነቢያት አንዱ ነው።
ነቢዩ ኢሳይያስ ማነው?
          ኢሳይያስ ማለት ቅቡዕ እምቅብዓ ትንቢት ማለት ነው። እንዲህ መባሉም ትንቢት የሚገልጥ መንፈስ ቅዱስ ስላደረበት ፥ ሀብተ ትንቢት ስለተሰጠው ነው። ኢያሱ ፥ ሆሴዕ ፥ ኢየሱስ መድኃኒት ማለት እንደሆነ መድኃኒት ማለትም ነው። ኢያሱ ወልደ ነዌ መድኃኒት የተባለው፡- ባጭር ታጥቆ ፥ ጋሻ ነጥቆ ፥ ዘገር ነቅንቆ ፥ አማሌቃውያንን አጥፍቶ ፥ እስራኤልን አድኖ ነው። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደግሞ፡- «ሕማማተ (መከራ) መስቀልን ታግሦ፥ ሥጋውን ቆርሶ፥ ደሙን አፍስሶ ፥ አጋንንትን ድል አድርጐ፥ ነፍሳትን አድኖ ነው። «ኢሳይያስስ ምን ሠርቶ ነው?» እንል ይሆናል። ኢሳይያስም ወደፊት በትንቢቱ፥ በትምህርቱ እንደሚያድን ፥ እግዚአብሔር ገልጦላቸው፥ ከቤተ ግዝረት ገብተው መድኃኒት ብለውታል።
          ኢሳይያስ የነበረው፡- በይሁዳ ነገሥታት፡- በዖዝያን፥ በአካዝና በሕዝቅያስ ዘመነ መንግሥት ነበር። ዘመኑም ከ740 - 688፡ ቅድመ ልደተ ክርስቶስ ነው። በአካዝና በሕዝቅያስ ዘመነ መንግሥት የቤተ መንግሥቱ አማካሪ ነበር። ፪ኛ ነገ ፲፱፥፫ ኢሳ ፯፥፩። ምክንያቱም የመንፈሳውያን ምክርና ተግሣጽ ለቤተ መንግሥቱ ያስፈልጋልና ነው። (ዛሬ ዛሬ ግን የተገላቢጦሽ ነው)። የአባቱ ስም አሞጽ ይባላል። ኢሳ ፩፥፩፣ ፪ኛ ነገ ፲፱፥፩። ነቢዩ ኢሳይያስ በስድሳ ስድስት ምዕራፍ የተከፈለ የትንቢት መጽሐፍ አለው። ይልቁንም ስለ ነገረ ማርያም፡- «ናሁ ድንግል ትጸንስ፥ ወትወልድ ወልደ፥ ወትሰምዮ ስሞ አማኑኤል፤ እነሆ፥ ድንግል ትፀንሳለች፥ ወልድንም ትወልዳለች፤ ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች።» በማለት ደረቅ ትንቢት (ትርጓሜ የማያሻው ትንቢት) ተናግሯል። ኢሳ ፯፥፲፬ ሰለ መከራ መስቀሉም፡- «እርሱ ግን በእውነት ደዌያችንን ተቀበለ፥ ሕመማችንንም ተሸከመ፥ ስለ እኛም ታመመ፤ . . . እርሱ ግን ስለ ኃጢአታችን ቈሰለ፤ ስለ በደላችንም ታመመ፥ የሰላማችንም ተግሣጽ በእርሱ ላይ ነበረ፥ በእርሱም ቁስል እኛ ተፈወስን። . . . እርሱ ግን በመከራ ጊዜ አፉን አልከፈተም፤ እንደ በግ ወደ መታረድ ተነዳ፤ የበግ ጠቦትም በሸላቾቹ ፊት ዝም እንደሚል፥ እንዲሁ አፉን አልከፈተም። ብሏል። ኢሳ ፶፫፥፬።
«ወዮልኝ፤» ያለው መቼ ነው?
          ነቢዩ ኢሳይያስ «ወዮልኝ፤» ያለው፦ እግዚአብሔርን በንጉሠ ነገሥት አምሳል በዙፋን ተቀምጦ ባየው ጊዜ ነው። ጊዜውም ንጉሡ ዖዝያን በሞተበት ዓመት ነው። «ርኢክዎ ለእግዚአብሔር ፥ እንዘ ይነብር ዲበ መንበሩ ነዋኀ ወልዑል። እግዚአብሔርን በረዥምና ከፍ ባለ ዙፋን ላይ (በልዑል መንበሩ) ተቀምጦ አየሁት፤ ምስጋናውም ቤቱን ሞልቶት ነበር። (ቤቱን ብርሃን ሞልቶት አየሁት)። ሱራፌልም (ሃያ አራት ካህናተ ሰማይ) በዙርያው ቆመው ነበር። (አክሊላቸውን አውርደው፥ ከጉልበታቸው ሸብረክ ብለው፥ አንገታቸውን ቀለስ አድርገው፥ የወርቅ ጽንሐ ይዘው ፥ የእሳቱን ዙፋን ዙሪያ ውን ያጥኑ ነበር)። ለእያንዳንዳቸውም ስድስት ስድስት አክናፍ ነበራቸው። ሁለት ክንፎቻቸውን ወደ ላይ ዘርግተው ፊቶቻቸውን ይጋርዱ ነበር ፥ ሁለቱን ክንፎቻቸውን ወደታች ዘርግተው እግሮቻቸውን ይሸፍኑ ነበር። የተቀሩትን ሁለቱን ክንፎቻቸውን ደግሞ እንደ መስቀል ግራና ቀኝ ዘርግተው ከጽንፍ እስከ ጽንፍ ይበርሩ ነበር።» ብሏል።
          ሱራፌል ሁለት ክንፎቻቸውን ወደ ላይ መዘርጋታቸው፡- «ወደላይ ቢወጡ፥ ቢወጡ አይደረስብህም ፥ (ባህርይህ አይመረመርም)፤ ማለታቸው ነው። ፊታቸውን መሸፈናቸው ደግሞ መለኮታዊ እሳት እንዳያቃጥላቸው ነው። አንድም ትእም ርተ ፍርሃት (የፍርሃት ምልክት) ነው። አንድም አንተን ማየት አይቻለንም ሲሉ ነው።  ሁለት ክንፎቻቸውን ወደታች መዘርጋታቸው፡- «ወደታች ቢወርዱ፥ ቢወርዱ አይደረስብሀም፥ ባህርይህ አይመረመርም፤» ማለታቸው ነው። እግሮቻቸውን መሸፈናቸው ደግሞ በፊትህ መገለጥ (መቆም) አይቻለንም፥ አይገባንም ማለታቸው ነው። ሁለት ክንፎቻቸውን ደግሞ በመስቀል አምሳል ግራና ቀኝ ዘርግተው ከጽንፍ እስከ ጽንፍ መብረራቸው  ትእምርተ ተልዕኮ ነው። አንድም ከጽንፍ እስከ ጽንፍ ብንበርር የሌለህበት ሥፍራ የለም፤ አይደረስብህም፥ ባህርይህ አይመረመርም፤ ማለታቸው ነው። በሌላ በኲል ደግሞ ከዕለተ ዓርብ በፊት በትእምርተ መስቀል አምሳል በፊቱ መታየታቸው፡- እንዲህ ባለ አርአያ ተሰቅለህ ዓለምን ታድናለህ ሲሉ ነው። በቅዳሴ ዮሐንስ ወልደ ነጐድጓድ፡- «የሚያቃጥል እሳት እንዳይበላቸው በመብረቅ ፊታቸውን ይሸፍናሉ፥ የኃይል ነበልባል እንዳያቃጥላቸው እግራቸውን በፍም ይሸፍናሉ፥ በአራቱ ማዕዘንና በዳርቻም ሁሉ ይወጣሉ። (ይበራሉ)።» የሚል አለ። ቁ 18
          ሱራፌል፡- «ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ፥ ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለች።» እያሉ፦ በታላቅ ድምፅ ፥ በአንድነት በሦስትነት ሲያመሰግኑ ነቢዩ ኢሳይያስ አይቷል ፥ ሰምቷል። ይህ ምስጋና በሰማይም በምድርም ፍጹም ነው። ሦስት ጊዜ ቅዱስ ማለታቸው ለሦስትነታቸው ፥ የቃሉ አለመለወጥ ደግሞ ለአንድነታቸው ምሳሌ ነው። ሥላሴ አንድም ሦስትም ናቸውና። ከዚህ በኋላ ጩኸው ከሚያመሰግኑት ምስጋና የተነሣ የመድረኩ መሠረት ተናወጠ፤ ቤቱንም ጢስ ሞላበት። ይህም፡- የፀውርተ መንበሩ (የእሳቱን ዙፋን የሚሸከሙ) የኪሩቤልን (የገጸ ሰብእ፥ የገጸ ላህም፥ የገጸ ንስር፥ የገጸ አንበሳ) ዕርገተ ጸሎታቸውን (የጸሎታቸውን ማረግ) ለኢሳይያስ ሲያሳየው ነው። አንድም ጢስ፦ እግዚአብሔር፦ እስራኤል ዘሥጋን ፈጽሞ እንደተጣላቸው የሚያመለክት ነው። ይኸውም በሀገራቸው ልማድ ሲገልጥለት ነው። በሀገራቸው አማላጅ የሄደ እንደሆነ፦ ጢስ አጢሰው፥ ቤት ጠርገው ይቆዩታል፤ እንዳይቀመጥ ትቢያ ይሆንበታል፥ እንዳይቆም ዓይኑን ጢስ ይወጋዋል፤ (ያቃጥለዋል)፤ በዚህን ጊዜ እንደምንም አንድ ነገር ወይም ሁለት ነገር ተናግሮ ይሄዳል። ይህም ምልጃህን ለመቀበል አልፈቀድንም ለማለት ነው። እግዚአብሔርም እስራኤል ዘሥጋን አልማለዳቸውም ሲል ጢሱን አሳይቶታል። በዚህን ጊዜ ነው ፥ ነቢዩ ኢሳይያስ፡- «እኔም ከንፈሮቼ የረከሱብኝ (በለምጽ የነደዱብኝ) ሰው በመሆኔ ፥ ከንፈሮቻቸው በረከሱባቸው ሕዝብ (ቢመክሯቸው ቢያስተምሯቸው በማይሰሙ፥ ሕገ እግዚአብሔርን በማያውቁ ወገኖች) በእስራኤል መካከል በመቀመጤ ዐይኖቼ የሠራዊትን ጌታ እግዚአብሔርን ስለአዩ ጠፍቻለሁና ወዮልኝ፤» ያለው።
ነቢዩ ኢሳይያስ ለምን በለምጽ ተመታ?
          በኦሪቱ ለምጽ የርኲሰት ምልክት ነበር። ነቢዩ ኢሳይያስ በነበረበት በንጉሡ በዖዝያን ዘመን ሊቀ ካህናቱ አዛርያስ ይባል ነበር። ስለ ክብረ ክህነት የከበረ ልብስ ይለብስ ስለነበር ንጉሡ፡- «ምነው? ከእኔ በላይ» ቢለው፦ «ካህናቲከ ይለብሱ ጽድቀ፤ ካህናትህ ጽድቅን ይለብሳሉ፤» ተብሎ ተጽፎብሃል ሲል መለሰለት። በአደባባይ የሚቀመጠውም በቀኙ ስለነበር ፥ አሁንም «ምነው?» ቢለው፡- «ካህን ይነብር በየማነ ንጉሥ፤ ካህን በንጉሥ ቀኝ ይቀመጣል፤» ይልብሃል አለው። ሦስተኛም ንጉሡ አዛብቶ ፥ አጓድሎ ፥ የፈረደውን ፍርድ ፥ አሟልቶ አቃንቶ ፈረደ። አሁንም «ምነው?» ቢለው፡- «እምነ መንግሥት የዓቢ ክህነት፤ ከሥልጣነ መንግሥት ሥልጣነ ክህነት ይበልጣል፤» አለው።
          በዚህን ጊዜ ንጉሡ ዖዝያን፡- «እኔስ በአባቴ ወገን መንግሥት ከተሰጠው ከነገደ ይሁዳ ብወለድም በእናቴ በኲል ክህነት ከተሰጠው ከነገደ ሌዊ እወለዳለሁ፤» ብሎ ለጥፋት ልቡ ታበየ፥ አምላኩንም እግዚአብሔርን በደለ፤ ልብሰ ተክህኖውን ለብሶ፥ ማዕጠንተ ወርቁን ይዞ፥ በዕጣን መሠዊያው ላይ ያጥን ዘንድ በድፍረት ወደ መቅደስ ገባ። ካህኑም አዛርያስ፥ ከእርሱም ጋር ጽኑአን የነበሩ ሰማንያ የእግዚአብሔር ካህናት ተከትለው ገቡ። ንጉሡንም ዖዝያንን እየተቃወሙ፥ «ዖዝያን ሆይ፥ ዕጣን ማጠን ለተቀደሱት ለአሮን ልጆች ለካህናቱ ነው እንጂ ለእግዚአብሔር ታጥን ዘንድ ለአንተ አይገባህም፤ ከእግዚአብሔር ርቀሃልና ከመቅደሱ ውጣ፤ ይህም በአምላክ በእግዚአብሔር ዘንድ ለአንተ ክብር አይሆንልህም፤» አሉት። ዖዝያንም ተቆጣ፤ በመቅደስም የሚያጥንበት ጥና በእጁ ነበረ፤ ካህናቱንም በተቆጣ ጊዜ በካህናቱ ፊት በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ በዕጣኑ መሠዊያ አጠገብ ሳለ በግምባሩ ላይ ለምጽ ታየ። (በሻሽ ቢሸፍነው በሻሹ ላይ ወጣበት)። ታላቁ ካህን አዛርያስ ካህናቱም ፈጥነው አባረሩት። እርሱም እግዚአብሔር ቀሥፎት ነበርና ይወጣ ዘንድ ቸኰለ። እስኪሞትም ድረስ ከለምጹ አልነጻም። ፪ኛ ዜና ፳፮፥፳። ልጁ ኢዮኣታም በሱ ተተክቶ እንደ ምስለኔ ሁኖ ሲገዛ ኑሯል። ያን ጊዜ ኢሳይያስ ለዖዝያን ወዳጁ ነበር፤ ቢመክረው፥ቢያስተምረው ይመለስ ነበር፤ ነገር ግን አፍሮት ፈርቶት፥ ሳይመክረው ፥ ሳያስተምረው፥ በመቅረቱ ከከንፈሩ ለምጽ ወጥቶበት ሀብተ ትንቢት ተነሥቶታል። እግዚአብሔር፦ ንጉሡ ዖዝያን ሲሞት ጠብቆ ለኢሳይያስ የተገለጠለት፡- «የፈራኸው ንጉሥ አለፈ፤ እኔ ግን በባህርዬ ሞት፥ በመንግሥቴ ኀልፈት የለብኝም፤ በዘባነ ኪሩብ ስሠለስ፥ ስቀደስ እኖራለሁ፤» ሲለው ነበር።

ለምጽና ሥርዓቱ፤
          በኦሪት ዘሌዋውያን ምዕራፍ ፲፫ እና ምዕራፍ ፲፬ ላይ ፥ እግዚአብሔር በልሙጻን ላይ የሠራውን ሥርዓት፥ ለሙሴና ለአሮን ሲነግራቸው እናገኛለን። ከዚህም ውስጥ፡- «የለምጽ ደዌ ያለበት ሰው፦ ልብሱ የተቀደደ ይሁን፥ ራሱም የተገለጠ ይሁን፥ ከንፈሩንም ይሸፍን፥ ርኲስ ይባላል፤ ደዌው ባለበት ዘመን ሁሉ ርኲስ ይሆናል፤ እርሱ ርኲስ ነው፤ ብቻውን ይቀመጣል፤ መኖሪያውም ከሰፈር በውጭ ይሆናል።» የሚል ይገኛል። ዘሌ ፲፫፥፵፭።
          «ልብሱ የተቀደደ ይሁን፤» ማለት፦ ስለ ኃጢአቱ ፈጽሞ ይዘን ማለት ነው። በልማድም ዕብራውያን ፈጽመው ሲያዝኑ ልብሳቸውን ለሁለት ይቀድዱታል። የዳዊት ልጅ ትዕማር የገዛ ወንድሟ ደፍሯት  ከቤት አስወጥቶ በዘጋባት ጊዜ፡- በራስዋ ላይ አመድ ነስንሳ፥ ብዙ ሕብርም ያለውን ልብሷን ተርትራ እየጮኸች አልቅሳለች። ፪ኛ ሳሙ ፲፫፥፲፱። «ራሱም የተገለጠ ይሁን፤ (አይሸፋፈን)፤» ማለት ለጊዜው ለምጹ እንዲታይ ነው። ለፍጻሜው ግን ኃጢአቱን አይሸፍን ፥ ገልጦ ለካህኑ ይናገር፥ (ይናዘዝ)፥ ማለት ነው። ጌታ በወንጌል ለምጻሙን ሰው፡- «ለማንም እንዳትናገር ተጠንቀቅ፥ ነገር ግን ሄደህ ራስህን ለካህን አሳይ፤» ያለው ለዚህ ነው። ማቴ ፰፥፬።  
          «ከንፈሩንም (አፉን) ይሸፍን፤» ማለት፦ ለጊዜው ደዌው በትንፋሽ እንዳይተላለፍ ሲሆን ፥ ለፍጻሜው ግን «ቅዱሱን የእግዚአብሔርን ስም መጥራት አይገባኝም፤» ይበል፥ማለት ነው። ለወገቡ መታጠቂያ፥ ለእግሩም ጫማ አይኑረው፥ የሚልም አለ። ለወገቡም መታጠቂያ አይኑረው የተባለው፦ ለጊዜው የለምጻም አካሉ ልህሉህ ስለሆነ እንዳይቆስል ሲሆን ፥ ለፍጻ ሜው ግን «ንጽሕና የለኝም፤» ይበል፥ ማለት ነው። ወገብን መታጠቅ የንጽህና ምልክት ነውና። ጌታችን አምላካችን መድኃ ኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወንጌል፡- «ወገባችሁ የታጠቀ፥መብራታችሁም የበራ ይሁን፤» ያለው ለዚህ ነው። ሉቃ ፲፪፥፴፭። ትርጉሙም፡- ልቡናችሁን በንጽህና ዝናር ታጠቁ፥ የልብ ንጽሕና ይኑራችሁ፥ ማለት ነው። ይኸንን በተመለከተ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ፡- «ስለዚህ የልቡናችሁን ወገብ ታጥቃችሁና ነቅታችሁ ኑሩ፤» ብሏል። ፩ኛ ጴጥ ፩፥፲፫ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም፡- «እንግዲህ ወገባችሁን በእውነት (በጽድቅ) ታጥቃችሁ ቁሙ፤» ብሏል። ኤፌ ፮፥፲፬። «ለእግሩ ጫማ አይኑረው፤» ማለትም ጫማ የምግባር ምሳሌ በመሆኑ «የምግባር ደሀ ነኝ፤» ይበል ማለት ነው። ቅዱስ ጳውሎስ ፦ «ወንጌልን ተጫሙ ፤ (በምግባረ ወንጌል ጸንታችሁ ቁሙ ፥ በወንጌል የታዘዘውን ፈጽሙ) ፤» ማለቱ ለዚህ ነውና። ኤፌ ፮፥፲፭።
«በደልህም ከአንተ ተወገደ፥ ኃጢአትህም ተሰረየልህ፤»
          ነቢዩ ኢሳይያስ፡- «ወዮልኝ፤» በማለቱ፡- ከሱራፌል አንዱ እየበረረ ወደ እርሱ መጣ። በእጁም ከሰማይ መቅደስ ከመሠዊያው በጉጠት የወሰደው ፍም ነበረ። አፉንም ዳሰሰበትና፡- «እነሆ፥  ይህ ከንፈሮችህን ነክቷል፥ በደልህም ከአንተ ተወገደ፥ኃጢአትህም ተሰረየልህ፤» ብሎታል። መሠዊያ የዓለመ ሥላሴ፥ ጉጠት የሥልጣነ እግዚአብሔር፥ ፍም የሀብተ ትንቢት ምሳሌ ነው። ከንፈሩን ማስነካቱም ሀብተ ትንቢትን መለስኩልህ ሲለው ነው። አንድም መሠዊያ የመንበር፥ ጉጠት የእርፈ መስቀል፥ መልአክ የቀሳውስት፥ ፍም የሥጋ ወደሙ፡ ምሳሌ ነው።
          ከዚህ በኋላ፡- «ማንን እልካለሁ? ማንስ ወደዚያ ሕዝብ ይሄድልናል?» የሚለውን የእግዚአብሔርን ድምፅ ሰምቷል። እርሱም፡- እነሆኝ፥ ጌታዬ፥እኔን ላከኝ፤» ሲል መልሷል። እንደ ጥንቱም፡- «ስማዕ ሰማይ፥ ወአጽምዒ ምድር፤ ሰማይ ስማ፥ ምድርም አድምጪ፤» የሚል ሆኗል። ትርጉሙም፡- «ሰማይ ሆይ፥ የእስራኤልን ነገር (ክፋታቸውን) ሰምተህ፥ ዝናም ለዘር፥ ጠል ለመከር አትስጥ፤ ምድርም ሰምተሽ የዘሩብሽን አታብቅዪ፥ የተከሉበሽን አታጽድቂ፤» ማለት ነው። አንድም በዚህ ምድር እንደ ሰማይ ከፍ ከፍ ያላችሁ ልዑላን (ባለሥልጣኖች፥ ባለጠጐች) ስሙ። እንደ መሬትም ዝቅ ዝቅ ያላችሁ ታናናሾች አድምጡ ማለት ነው። አንድም ሰማይ የተባሉ መላእክት ሲሆኑ ምድር የተባሉ የአዳም ልጆች ናቸው።
እንደ ኢሳይያስ፦ «ወዮልኝ፤» ማለት ያስፈልጋል፤
          የእግዚአብሔር ሰዎች «ወዮልኝ፤» እያሉ ራሳቸውን ገሥጸው ይኖራሉ። ጌዴዎን የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጦ ፊት ለፊት ስላየው ፥ ቃል በቃል ስላነጋገረው፡- «አቤቱ አምላኬ ሆይ፥ ወዮልኝ፤ የእግዚአብሔርን መልአክ ፊት ለፊት አይቻለሁና፤» ብሎ ነበር። እግዚአብሔርም፡- «ሰላም ለአንተ ይሁን፥ አትፍራ፥ አትሞትም፤» ብሎታል። መሳ ፮፥፳፪። ነቢዩ ኤርምያስም፡- «በሆድ ሳልሠራ አውቄሃለሁ፥ ከማኀፀንም ሳትወጣ ቀድሼሃለሁ፥ ለአሐዛብም ነቢይ አድርጌሃለሁ፤» በተባለ ጊዜ፡- «ወዮ ጌታ እግዚአብሔር፥ እነሆ፥ብላቴና ነኝና እናገር ዘንድ አላውቅም፤» ብሏል። ኤር ፩፥፬። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ፦ «ወንጌልን ባልሰብክ ወዮልኝ፤ » ብሏል። ፩ኛ ቆሮ ፱፥፲፮።
          እነዚህ «ወዮልኝ፤» ማለታቸው ለእኛ አብነት ነው። ታላላቆቹ እንዲህ ካሉ ከእኛ ከታናናሾቹ የብዙ ብዙ ይጠበቃል። ዕለት ዕለት «ወዮልኝ፤» እያልን ደረታችንን ልንደቃ፥ እንባችንን ልናፈስስ ይገባል። ሥጋችንን ደስ ከማሰኘት በስተቀር እግዚአብሔርን ደስ አሰኝተን አናውቅምና። ሰውን ደስ ለማሰኘት በሰውም ዘንድ ለመወደድ (ለውዳሴ ከንቱ) እግዚአብሔርን እናሳዝናለንና። እንኳን መንፈሳዊ መሆን መምሰሉ እንኳ አቅቶናልና። ሃያ፥ሠላሳ ዓመት ቃለ እግዚአብሔር ዘር ተዘርቶብን፡- ሠላሳ፥ስድሳ፥መቶ ማፍራት የተሳነን ዘረ ቆርጥሞች ነንና። መቁረባችን ማቁረባችን ፥ መቀደሳችን ፥ ማስቀ ደሳችን፥ ማሳለማችን፥መሳለማችን፥ መናዘዛችን፥ማናዘዛችን፥ መዘመራችን፥ማዘመራችን፥ መስበካችን፥መሰበካችን ሁሉ ከንቱ ሆኖብናልና። ስለሆነም «እገሌ ሳይገባው ነው፤» የሚለውን ትተን፡- «እኔ ሳይገባኝ ነውና ወዮልኝ፤» እንበል። የእግዚአብሔር ሰዎች፡- «ወዮላችሁ፤» እስኪባሉ አይጠብቁምና።
«ወዮላችሁ፤»
          የዓለም ሰዎች፡- «ወዮላችሁ፤» እስኪባሉ ይጠብቃሉ፤ ተብለውም አይመለሱም፤ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የቃሉን ትምህርት ሰምተው፥ የእጁን ተአምራት አይተው ያልተመለሱትን ጸሐፍት ፈሪሳውያንን በአንድ ምዕራፍ ላይ ብቻ ስምንት ጊዜ «ወዮላችሁ፤» ብሏቸዋል።
-      «እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን፦ መንግሥተ ሰማያትን በሰው ፊት ስለምትዘጉ ወዮላችሁ።»
-      «እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን፦ በጸሎት ርዝመት እያመካኛችሁ የመበለቶችን ቤት ስለምትበሉ ወዮላችሁ።»
-      «እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን፦ አንድ ሰው ልታሳምኑ በባሕርና በደረቅ ስለምትዞሩ፥ በሆነም ጊዜ ከእናንተ   
        ይልቅ ሁለት እጥፍ የባሰ የገሃነም ልጅ ስለምታደርጉት፥ ወዮላችሁ።»
-      «ማንም በቤተመቅደስ የሚምል ምንም የለበትም፤ ማንም በቤተመቅደስ ወርቅ የሚምል ግን በመሓላው ይያዛል  
        የምትሉ ፥ ዕውሮች መሪዎች ወዮላችሁ።»
-      «እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን፦ ከአዘሙድና ከእንስላል ከከሙንም አሥራት ሰለምታወጡ፥ ፍርድንና  ምሕረ  
        ትን ፥ ታማኝነትንም፥ በሕግ ያለውን ዋና ነገር ስለምትተዉ ወዮላችሁ።»
-      «እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን፦ በውስጡ ቅሚያና ስስት፦ ሞልቶ ሳለ የጽዋውንና የወጭቱን ውጭ 
        ስለምታጠሩ ወዮላችሁ።»
-      «እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን፦ በውጭ አምረው የሚታዩ በውስጥ ግን የሙታን አጥንት ርኲሰትም ሁሉ 
        የተሞሉ በኖራ የተለሰኑ መቃብሮችን ስለምትመስሉ፥ ወዮላችሁ።»
-      «እናንተ ግብዞች ጻፍችና ፈሪሳውያን፦ የነቢያትን መቃብር ስለምትሠሩ ፥ የጻድቃንንም መቃብር ስለምታስጌጡና 
        በአባቶቻችን ዘመን ኖረን በሆነስ በነቢያት ደም በአልተባበረናቸውም ነበር ስለምትሉ፥ ወዮላችሁ።»
     አይሁድ «ወዮላችሁ፤» ተብለውም አልተመለሱም፥ ጌታም እንደማይመለሱ ያውቃል። ስለሚያውቅም «እንግዲያስ የነቢያት ገዳዮች ልጆች እንደሆናችሁ በራሳችሁ ትመሰክራላችሁ። እናንተ ደግሞ የአባቶቻችሁን መስፈሪያ ሙሉ። እናንተ እባቦች፥ የእፉኝት ልጆች፥ ከገሃነም ፍርድ እንዴት ታመልጣላችሁ?» ብሏቸዋል። ማቴ ፳፫፥፲፫-፴፪። ከእነርሱም በፊት የኮራዚንና የቤተ ሳይዳ ሰዎች «ወዮላችሁ»፤ ብሏቸው ነበር። ማቴ ፲፩፥፳፩።ይኸውም ንስሐ ባለመግባታቸው ነው። የሰዶምና የጐመራ ሰዎች እነርሱ ያገኙትን ዕድል አግኝተው ቢሆን ኖሮ፦ ማቅ ለብሰው ፥ ዓመድ ላይ ተኝተው ንስሐ ይገቡ እንደነበር ነግሯቸዋል። እኛም ያገኘነውን ዕድል ያላገኙ ብዙ ሕዝቦች እንዳሉ ማስተዋል አለብን። ጌታችን፦ «ወዮ ለዓለም ማሰናከያ፤ ማሰናከያ ሳይመጣ አይቀርምና ፥ ነገር ግን በእርሱ ጠንቅ ማሰናከያ ለሚመጣበት ለዚያ ሰው ወዮለት።» ያለበትም ጊዜ አለ። ማቴ፲፰፥፯። ያ ሰው የተባለ ለጊዜው ይሁዳ ሲሆን ለፍፃሜው የሁላችንንም ሕይወት ይመለከታል። በአንድም ይሁን በሌላ የእኛም ሕይወት ለሌላው መሰናክል እንቅፋት እየሆነ ነውና። ንጹሐ ባህርይ ኢየሱስ ክርስቶስ ፦ «ወዮላችሁ፤» ቢል የባህርይ አምላክ በመሆኑ ነው። ቅዱሳንም፦ «ወዮላችሁ፤» ቢሉ ፦ ከኃጢአት ርቀው፥ ከበደል ተለይተው፥ ሃይማኖት ይዘው ፥ ምግባር ሠርተው ነው። እኛ ግን እምነታችን ደካማ ፥ጸሎታችን የማይሰማ ፥ ምግባራችን ጐዶሎ መሆኑን እያወቅን ሌሎችን «ወዮላቸው፤» እንላለን። ከምዕመናን ፥ ከዲያቆናት፥ ከቀሳውስት፥ ከመዘምራን ፥ ከሰባክያን ፥ ከጳጳሳት ፥ የማንፈርድበት የለም። አንድም ቀን በራሳችን ፈርደን፥ «ወዮልን፤» ብለን አናውቅም። ስለዚህ ኃጢአታችን እንዲሠረይልን ፥ በደላችንም እንዲወገድልን የዘወትር ጸሎታችን «ወዮልኝ፤» የሚል ይሁን። በሌላ በኲል ግን ሃይማኖት ፥ሥርዓት ፥ ትውፊት ፥ ሲጠፋ ተመክረው ፥ ተገሥፀው የማይመለሱትን «ወዮላችሁ፤» ብሎ ማስጠንቀቅ መፍረድም ይገባል። እንግዲህ እንደ ፈሪሳዊያን ከመሆን የእግዚአብሔር ቸርነት፥ የድንግል ማርያም አማላጅነት ይጠብቀን። አሜን።

No comments:

Post a Comment