Wednesday, April 22, 2015

አብረን ልናስባቸው የሚገቡ ሌሎች በስቃይ ውስጥ ያሉ ዜጎች

Diakon Abayneh Kasse
ትናንት በአሜሪካ ድምጽ አሁንም እዚያው ሊብያ ትሪፖሊ ውስጥ በተዘጋ ቤት ውስጥ በጭንቅ እነዚያን የሞት መልእክተኞች ፈርተው የተደበቁ መኖራቸውን ስሰማ የበለጠ ሰውነቴን ነዘረኝ፡፡ ድምጻቸው የተማኅጽኖ ነው፡፡ ተናጋሪው ወንድማችን ክርስቲያን መኾናቸውን ለጋዜጠኛው ነግረውታል፡፡ በዚህም ላይ ከአሁን አሁን ይመጡብናል የሚል ፍርሃት እና ሽብር ላይ መኾናቸው በድምጻቸው ይታወቃል፡፡ እኔም እዚያ ውስጥ ያለሁ መሰለኝ፡፡ ውስጤ ተረበሸ፡፡

እርሳቸው እንደተናገሩት ከኾነ ከወለደች ጥቂት ቀን የኾናት አንዲት እኅታችንን እና እርጉዞች የኾኑ እኅቶቻችንን ማንነታቸው የማይታወቁ ገጻቸውን የተሸፋፈኑ ሰዎች አፍሰው ወስደዋቸዋል፡፡ አብረውም ሌሎች ወንዶች ታፍሰዋል፡፡ ደግሞ ምን ሊያደርጉ ይኾን? ይኽንን ሳስብ ሰውነቴ ይንቀጠቀጣል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ሆይ አንተው ድረስላቸው፡፡ የጭንቅ አማላጃችን ድንግል ማርያም ሆይ መንገዱን አብጅላቸው፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ ዘግናኝ ግድያ ለተፈጸመባቸው ኢትዮጵያውያን ጸሎተ ፍትሐትና ምህላ እንዲደረግላቸው ወሰነ




በሰሜን አፍሪካ ሊቢያ ውስጥ ሚያዝያ 11 ቀን 2007 .. አሰቃቂና አረመኔያዊ ግድያ ለተፈጸመባቸው ኢትዮጵያውያን፣ ከሚያዝያ 14 ቀን 2007 .. ጀምሮ ለሰባት ቀናት የሚቆይ ጸሎተ ፍትኃትና ጸሎተ ምህላ እንዲደረግላቸው፣ የኢትየጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ሚያዝያ 13 ቀን 2007 .. ውሳኔ አስተላለፈ፡፡

በሜድትራኒያን ባህር ዳርቻ አካባቢ ሁሉም የክርስትና እምነት ተከታዮች መሆናቸው በተገለጸው ኢትዮጵያውያን ላይ የተፈጸመው ግድያ፣ ከምንጊዜውም በተለየ ሁኔታ እጅግ በጣም እንዳሳዘነውና እንዳሳሰበው የገለጸው ቅዱስ ሲኖዶስ፣ ድርጊቱ በአንድ የሃይማኖት ተከታዮች ላይ ብቻ የተፈጸመ ሳይሆን፣ በሁሉም የዓለም ሃይማኖት ተከታዮች ላይ የተቃጣ የወንጀል ተግባር መሆኑን ገልጿል፡፡ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብና የሃይማኖት ተቋማት፣ እንዲሁም የዓለም መንግሥታትና ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ፣ ድርጊቱን ከማወገዝና ከመቃወም ባለፈ ትርጉም ያለው ለውጥ የሚያመጣ ፈጣንና ዘላቂ መፍትሔ ማፈላለግ እንዳባቸው አክሏል፡፡

Tuesday, April 21, 2015

ክርስትና የመናቅና የመጠላት ሃይማኖት



ከሁለት ወራት በፊት የግብፅ ክርስቲያን ወንድሞቻችንን አንገት ቀልተው ወጣቶቹንና ቤተ ክርስቲያኒቱን ለሰማዕትነት ክብር ያበቁ አረመኔዎች ሰሞኑን ደግሞ ተራው የኢትዮጵያውያን ወጣቶች እና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን መሆኑን በተግባር የወንድሞቻንን አንገት ከመቅላት እና በጥይት ከመደብደብ አልፈው በቃልም ሰማዕታቱንየጠላታችን የኢትዮጵያ የመስቀል ተከታዮችብለው በመደንፋት ገልጸውልናል። ለሃይማኖታቸው የቆረጡ ዕድለኞቹ ወንድሞቻችንም አንገታቸውን ለስለት፣ ጀርባቸውንም ለጥይት እሩምታ በመስጠት ፈጣሪያቸውንና ቤተ ክርስቲያናቸውን በሰማዕትነት ሞት አክብረዋል።ፈጣሪ ለምን ዝም አለ? እንዴትስ በእነዚህ ጨካኞች እጅ ሕይወታቸው እስኪያልፍ ተዋቸው?” በማለት የእምነታቸውን መላላት ያሳዩንም አሉ።