Friday, September 7, 2012

ያለፈው ዘመን ይበቃል ... 1ጴጥ.4፡3

  • የአሕዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት በመዳራትና በሥጋ ምኞትም በስካርም በዘፈንም ያለ ልክም በመጠጣት ነውርም ባለበት በጣዖት ማምለክ የተመላለሳችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃልና። 1ጴጥ.43፡፡ 
  • «ሰውስ ዘመኑ እንደ ሣር ነው እንደ ዱር አበባ እንዲሁ ያብባል፡፡ ነፋስ በነፈሰበት ጊዜ ያልፋል» መዝ.102/103 1516

አባታችን አዳም ጀምሮ ብዙ ትውልድ በዚህች ምድር ላይ ተመላልሷል፡፡ ወጥቷል ወርዷል አልፏል፡፡ ዘመን ሲያልፍ ዘመን ሲተካ ሰው ሲያልፍ ሰው ሲተካ፡ ዛሬ ላይ ደርሰናል፡፡ ነቢየ እግዚአሔር ዳዊት በመዝሙሩ«ሰውስ ዘመኑ እንደ ሣር ነው እንደ ዱር አበባ እንዲሁ ያብባል፡፡ ነፋስ በነፈሰበት ጊዜ ያልፋል» መዝ.102/103 1516 ብሏል፡፡ ይህም ቃል በአዳም ልጆች ሁሉ ላይ ሲሠራ ኖሮ ከአሁኑ ትውልድ ደርሷል፡፡ ቋሚ የቆየ የሚመስለው የአሁኑ ዘመን ሰው ግን ሊያስተውለው የሚገባ አንድ ዐቢይ ቁም ነገር አለ፡፡ ይኸውም ከእርሱ በፊት የነበረው ትውልድ ቦታውን ለአሁኑ እንደለቀቀ ሁሉ ይኸኛውም ትውልድ በበኩሉ ኃላፊ መሆኑ ነው፡፡ ታዲያ አሮጊው ዘመን አልፎ አዲሱ ዘመን ሲተካ ክርስቲያኖች አዲሱን ዘመን በምን ዓይነት መንፈስ ነው የምንቀበለው?

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ መልስ የሚሆነን ነገር በመጀመሪያ ክታቡ ላይ ዘግቦት እናገኘዋልን፡፡  የአሕዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት በመዳራትና በሥጋ ምኞትም በስካርም በዘፈንም ያለ ልክም በመጠጣት ነውርም ባለበት በጣዖት ማምለክ የተመላለሳችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃልና 1ጴጥ.43፡፡ ባለፈው ዓመት ሕግ እንደ ሌላቸው አሕዛብ ያለ ሕግ የተመላለስንበት የኃጢአት ሕይወት ዛሬ በንስሐ ተወግዶ በፍጹም ተለውጠን አዲስ ሰው የምንሆንበት ጊዜ ነው፡፡ ሮሜ.6 በክርስቶስ ክርስቲያን የተሰኘን ሁላችን በስካርና በዝሙት፣በስርቆት እና በቅሚያ፣ በመግደልና በምቀኝነት በቅንዓትና በቂመኛነት ያሳለፍነውን ሕይወት ትተን አዲስ ሰው የምንሆንበት ዘመን ሊሆን ይገባል፡ የቀን መቁጠሪያው 2004ኛውን የምሕረት ዓመት አስቆጥሮናል እኛም በግላችን በዚህ ምድር ላይ ብዙ የምሕረት ዓመታትን አሳልፈናል፡፡ በእውነት ግን ካሳለፍናቸው የምሕረት ዓመታት በስንቶቹ ተምረንባቸው ይሆን? በምሕረት ዓመታት የብርሃንን /የጽድቅን/ ሥራ ትተን የጨለማን /የኃጢያትን/ ሥራ ብቻ ስንሠራ አሳልፈን ከሆነ ግን አዲሱ ዓመት ይህንን ትተን ወደ እግዚአብሔር የምንቀርብበት የምሕረት ዓመት ሊሆን ይገባዋል፡፡
በሰው ፊት ጻድቅ በእግዚአብሔር ፊት ግን ኃጥእ የሆንበት፣ ሃይማኖታችንን በገንዘብ የለወጥንበት፣ በማንኛውም መንገድ እግዚአብሔርን ያስከፋንበት ያለፈው ዘመን አክትሞ መጪው ጊዜ አዲስ ሰው የምንሆንበት ሊሆን ይገባል፡፡ አዲስ ሰው መሆን ያለፈ ዘመንን ክፉ ሥራ መተው ነው፡፡ በምትኩም ለመልካም ሥራ መነሳሳት የመንፈስ ፍሬያትን ማፍራት ነው፡፡ «የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር፣ ደስታ፣ ሰላም፣ ትዕግሥት፣ ቸርነት፣ በጎነት፣ የውኃት፣ ራስን መግዛት ነው፡፡» ገላ.5-22፡፡
እነሆ የመዳን ቀን አሁን ነው እና ኃጢአታችን በንስሐ ውኃ የምንታጠብበት፣ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቀራንዮ በቆረሰልን ሥጋው ባፈሰሰልን ደሙ የምንታተምበት፣ኃጢአተኛ የነበረውን ሰውነታችንን ለእግዚአብሔር ሕግ የምናስገዛበት የምሕረት ዓመት እንዲሆን እራሳችንን እንቀድስ በአዲስ ዓመት አዲስ ሰው እንሁን፡፡
በአዲስ ዓመት አዲስ ሰው መሆንን ከፈለግንና ለማረጋገጥም ከሻን ትላንት በአንደበታችን ሰዎችን ክፉ በመናገር ያስቀየምን፣ የሰረቅን፣የዋሸን፣ የገደልን፣ የሰው ንብረት ያለ አግባብ የወሰድን፣ በሀሜትና በዝሙት ኀጢአት የወደቅን፣ የምዋርት፣ የጥልና የክርክር መንፈስ ያለብን፣ወዘተ ሰዎች ሁሉ ይህ ሁሉ ራሳችንን ከሚጎዳ በስተቀር ምንም የማይጠቅመን መሆኑን ተገንዝበን ንስሐ ልንገባ ከእግዚአብሔር ጋር ልንታረቅ ይገባናል፡፡ለዚህም የሰላም የፍቅር የምሕረት አምላክ እግዚአብሔር ይርዳን፡፡አሜን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

1 comment: