Friday, November 16, 2012

ቅዱስ ሲኖዶስ ለአክሱም ሙዚየም ግንባታ 13 ሚሊየን ብር መደበ




(አንድ አድርገን ፤ ህዳር 7 2005 ዓ.ም)፡- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የአክሱም ሙዚየም ግንባታ እዳይቋረጥ ባለፈው ጥቅምት ጉባኤ 13 ሚሊየን ብር መመደቡ ተሰማ ፡፡ ከቤተክርስትያኒቱ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው ከአቶ ስታሊን ገ/ሥላሴ ለሸገር ሬዲዮ እንዳሉት “አቡነ ጳውሎስ በህይወት ሳሉ ያስጀመሩትና 2 ዓመት እየተጠጋው ያለውን የአክሱም ሙዚየም ግንባታ  የአቡነ ጳውሎስ እረፍት  የግንባታውን ሂደት እንዳያቀዘቅዘው በማለት ነው ሲኖዶሱ ይህን ያህል ብር የመደበው” ብለዋል፡፡ 

እጅግ ዘመናዊ የተባለውን ሙዚየም ሰርቶ ለመጨረስ በጠቅላላ 25 ሚሊየን ዩሮ ወይም ከ500 ሚሊየን ብር በላይ የኢትጵያ ብር ያስፈልጋል ተብሏል ፤ የመጀመሪያው ዙር ግንባታም በተክለ ብርሀን ኮንስትራክሽን ድርጅት አማካኝነት እየተከናወነ ሲሆን  በሙዚየሙ ውስጥ የቅርስ ማስቀመጫ ፤ የአባቶች ማረፊያ እና የተለያዩ ክፍሎችን ይኖረዋል ብለዋል፡፡ 

የኢትዮጵያ ቅርስ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ዮናስ ደስታ በበኩላቸው የሙዚየሙ ስራ “በአለም ቅርስነት የተመዘገቡትን ቦታዎች እይታ ይለውጥብናል” የሚል ስጋት ዩኔስኮ  አድሮበት የነበረ ቢሆንም የአፍሪካ ተወካዩን ባሳለፍነው መስከረም ወር በመላክ የፈራው እንደማይን አረጋግጧል፡፡ ዩኔስኮ የጥንታዊ ህንጻ ገጽታ እንዲኖረውም እፈልጋለሁ ባለው መሰረት ግንባታው እተከናወነ ይገኛል በማለት ለሸገር ሬዲዮ ገልጸዋል፡፡
ምንጭ:- ህዳር 7 2005 ዓ.ም (ከጠዋት የሸገር ሬዲዮ ዜና የተወሰደ)

No comments:

Post a Comment