Tuesday, May 1, 2012

‹‹በሀይማኖት ጉዳይ ላይ የለዘበ አቋም እንዳታሳዩ›› ከላይ የወረደ መመሪያ


(አንድ አድርገን ሚያዚያ 24 2004ዓ.ም)፡- በአሁኑ ሰዓት ነገሮች ሁሉ መልካም አይደሉም ፤ መንግስት ከኑሮ ውድነት በላይ የሀይማኖት ችግር በጣም እያሰጋው ይገኛል ፤ ሙስሊም ማህበረሰብ የጠየቁት ጥያቄ ድፍንፍን ያለ መልስ በፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር በዶ/ር ሽፈራው አማካኝነት መስጠቱ ይታወቃል ፤ የዛሬ 15 ቀን ግድም ጠቅላይ ሚኒስትራችን በፓርላማው ተገኝተው ስለ ወቅታዊ ጉዳይ ማብራሪ በሰጡበት ወቅት ረዥሙን ሰዓት የያዘው ሀይማኖታዊ ጉዳዮች ነበር ፤‹‹እኛ ስራችን ህገመንግስቱን ማስከበር ነው ፤ ሁሉም የራሱን ሀይማኖት ህገመንግስቱን እስካልተቃረነ ድረስ ማስፋፋት መስበክ ይችላል ፤ ለምን? ብለን መጠየቅ መብት የለንም ፤ የኦርቶዶክስ አማኞች ሰባኪ ከህንድ ቢያመጡ እኛን አይመለከተንም ፤ ሰለፊም የራሴን እምነት አራምዳለሁ ካለ መብቱ ነው መከልከል አንችልም ህገ መንግስቱን እስካልተጋፋ ድረስ ››ብለዋል፡፡ እስከ ዛሬ ድረስ ተንትነው በማያውቁት መንገድ ውሀቢን እና ሰለፊን የገባቸውንና ጀሌዎቻቸው የነገሯቸውን የደረሱበትን ያህል ለመግለጽ ሞክረዋል ፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተናገሩ ማለት የመንግስትን አቋም አንጸባረቁ ማለት መሆኑ እሙን ነው ፤ ባሳለፍነው ሳምንት ላይ ፍትህ ጋዜጣ ሁለት የአወሊያ ተማሪዎች ባልታወቀ ምክንያት መሞታቸውን አስነብቦናል ፤ በአሁኑ ሰዓት ደግሞ በዋልድባ እየሆነ ያለው ነገር ሁላችን የምናውቀው ነገር ነው ፤ በዚያ ላይ የአልቃይዳ ህዋስ አዲስ አበባ ውስጥ ተገኝ ተብሎ ብዙ መባሉንም እናውቃለን ፡፡

አሁን በደረሰን መረጃ መሰረት መንግስት እየተፈጠረ ያለው ነገር በጣም ያሳሰበው ይመስላል ፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፓርላማ ላይ ገለጻ ካደረጉ በኋላ መመሪያ ለበታች አካላት ተልኳል ፤ የበታች አካላት የተባሉት ፍርድ ቤቶች እና የመንግስት አቃቢ ህጎችን ያካትታል ፤ የወረደላቸው መመሪያ ‹‹ ህጉን ብቻ አስከብሩ ፤ በሀይማኖት ጉዳይ ላይ የለዘበ አቋም እንዳታሳዩ ፤ ለየትኛውም ሀይማኖት ወገንተኝነት እንዳይኖራችሁ ፤ ህገ-መንግስቱንና ህጉን ብቻ መሰረት አድርጋችሁ ስሩ ›› በማለት ትእዛዝ ተሰቷቸዋል ፤ ይህም መልዕክት የአጭር ጊዜ ስብሰባ በማድረግ ለሚመለከተው ሁሉ ተላልፏል ፤ ነፍሷን ይማረውና አያቴ ‹‹ጓደኛ ሲታማ ለኔ ብለህ ስማ ›› ትለኝ ነበር ፤ በመሰረቱ ይህ ነገር ከዳኞች እና ከአቃቢ ህግ የስነ ምግባር መርህ ውስጥ ጠፍተው አይደለም ፤ ነገር ግን በአሁኑ ሰዓት መንግስት እያስተዋለ ያለው ነገር በመገኝቱ ነው፡፡
ከሳምንት በፊት 13 ሙስሊም አቃቢ ህጎችና ዳኞች በእለተ ቅዳሜ ለስራ በማስመሰል በቢሮ ውስጥ ተሰብስበው ተገኝተዋል ፤ መቼስ ስለ ጤና ቤተሰብ ለማውራት ተሰበሰቡ ማለት አዳጋች ነው ፤ እነዚህ ሰዎች መንግስት በሰጣቸው ሃላፊነት ደረጃ ከበታች ያሉትን የክፍለ ከተማ ፖሊሶች ላይ ተጽህኖ እያሳደሩ ይገኛሉ የሚል ሹክሹክታም አለ ፤ ከሙስሊሞች እንቅስቃሴ ጋር ፖሊስ ሰዎችን እየያዘ ጣቢያ ሲያሳድር ፤ እነዚህን መሳይ ሰዎች ደግሞ ለምን ታሰሩ? ብለው ይጠይቃሉ በቀጥታም ባይሆን በተዘዋዋሪ ስራውና ህጉ ላይ ተጽህኖ እያሳደሩ እንደሚገኙ በጣም ቅርብ ከሆነ ሰው ለማወቅ ችያለሁ ፤ ይህን መሰረት በማድረግ ይመስላል ትዕዛዝ የተላለፈላቸው ፤ ይህን አይነት አካሄድ መንግስት አትኩሮት ሰጥቶት ካልተከታተለ ያስቀመጠውን ህግ አስፈጽማለው ማለት የሚያዳግተው ይመስለናል ፡፡ ህጉን የረቀቀው በሰዎች የሚፈጸመውም በሰዎች መሆኑን መዘንጋት ያለበት አይመስለንም፡፡
እኛም ቢሆን ከዚህ ትምህርት መውሰድ ያለብን የምናደርገውን ነገር ከብዙ አንግል መመልከት መቻል አለብን ፤ ስለ ቤተክርስትያን ጠበቃ መቆም መልካ ነው ፤ ነገር ግን እንዴት? የሚለው መልስ መመለስ መቻል ያለበት ይመስለናል ፤ ስሜታዊነታችንን አይሎ ከፊት ስንቆም ጥያቄያችንን በሌላ በሌላ ነገር አዙረውት ሌላ ስም እንዳይሰጠን መጠንቀቅ መቻል ያለብን ይመስለናል ፡፡
ባለፈው ጊዜ የማህበረ ቅዱሳንን ስም ለምን ፓርላማ ላይ እንደተነሳ ለማወቅ ከተለያዩ ውስጠ ሚስጥር ከሚያውቁ(ከኢህአዴግ ህዋሳት ጋር) ሰዎች ጋር ለመወያየት ሞክሬ ነበር ፤ ያላቸውንም አመለካከት በሻይ ቡና ለመቃረም ሞክሬ ነበር ፤ የማህበሩ ስም በዘመናት አንድ ጊዜም በፓርላማ ቢጠራም ያለምክንያት እንዳልተነሳ ለማወቅ ችያለሁ ፤ ያልተመከረበት ነገር ፓርላማ ላይ አይወራም ፤ ሁሉ ነገር Calculated Game ሊሆን ይችላል ፤ ስለዚ መጠንቀቁ ሳያዋጣ አይቀርም ተብያለሁ ፤ ተጽህኖውን አሁን ላይ ላናየው እንችላለን አካሄዳቸውን ግን መንግስት አይቆጣጠረውም ማለት ይከብዳልም ብለውኛል ፤ ‹‹ማህበሩ ራሱን የሚያይበት መስታወት እንዳለ ሁላ መንግስትም ማህበሩን የሚመለከትበት የራሱ የሆኑ መስታወት አለው ፤ ከመስታወቱ ውስጥ ያለውን ምስል እንደተመልካቹ ሊቀያየር ይችላል›› ብለውኛል ፤ የቴዲ አፍሮ ካሴት ሲሰራ የደህንነት ሰዎች ቀድመው ሁሉን ነገር ያውቁ ነበር ፤ ከመውጣቱም በፊት ማስተላለፍ የተፈለገው መልዕክት ታይቷል ፤ ታዲያ ለአንድ ዘፋኝ ይህን ያህል ርቀት መጓዝ ከቻሉ ለማህበረ ቅዱሳን በሺህ የሚቆጠር አባላት ላሉት ማህበር ይህን አያደርጉም ማለት ይከብዳል ብለውኛል ፡፡ መጠንቀቁ አይከፋም እንላለን ….




የዋልድባው ሪፖርት አንድ ጊዜ ጻፉት አስር ጊዜ ግን በተለያየ መንገድ ተመልከቱት ፤ ከሪፖርቱ በኋላ ስለሚከሰቱ ነገሮችም ቅድሚያ ብትወያዩበት መልካም ነው ፤ የሚመጣም ጫና ካለ ራስን ለሸክም ማዘጋጀት ተገቢ ይመስለናል ፤ ከሁሉ በላይ ደግሞ እግዚአብሔር አለ፡፡ ማስፈራሪይ አይደለም ሀሳብ ነው 

4 comments:

  1. ሪፖርቱ ምንም ይፈጠር እውነቱን ቁልጭ አድርጎ ማቅረብ አለበት፤ እውነታውን ከምናድበሰብሰው እና በግልጽ የማይቀርብ ከሆነ ባይቀርብ ይሻላል፡፡ እውነትን ብንሸራርፋት እግዚአብሄር ስለሚፈርድ የዚያን ጊዜ መተዛዘብ ይመጣል፡፡ እዚህ ላይ ቁመን ማሰብ ያለብን ስለ ቤተክርስቲያን ህልውና ነው እንጅ ስለማህበሩ ህልውና አይደለም ፣ማስተዋል ጥሩ ቢሆንም ፈርታችሁ አታስፈሩ፡፡

    ReplyDelete
  2. Wendme sel hasbah amesganlew

    Gn lmn yemiyasfera hasab takerbalh... yane muse yalakachewn hultun melktengoch hun enji, Eyasun ena Kaleb.... selelu... yemihedubt hagr asferi nebr.. negr gn yesemay amlak yirdanl alu... beka Yesemay Amalk Yirdanal...

    ReplyDelete
  3. እውነትን ከማጋለጥ መሸሸ የለባቸውም ምክኒያቱም ሰው ፈርትን ብንተውው እግዚአብሔር ምን ይለናል ብቻ አውነት የሆነውን ምናግር ኣልባችወ ከ እግዚአብሔር ይልቅ ሰው ፈርተን እውነቱን ብናድበሰብስው የዛናጊዜ ነው የማህብሩ ህልውና የሚያከትመወ አንድ ነግር ማስብ ኣለባቸሁ “አባቶቻችን ሕየወትን ብቻ ሳይሆን ሞትንም አሰትምረወናል” እንደኔ መንግስት የፈለገው ይሁን እወነትን ከምናገር አትቆጠቡ ዕላለው ከእግዚአበሔር ይልቅ መንግሰትን ከፈራን ብቃ አከተመ ….

    ReplyDelete
  4. ብዕሩ ዘ-አትላንታMay 2, 2012 at 7:48 AM

    ነገሮችን በሰከነ መንገድና በአስተዉሎት መመልከት ብልህነት ነዉ ።ማኅበረ ቅዱሳንም እየተጓዘ ያለዉ በዚህ መልኩ ይመስለኛል። ምክንያቱም መንግሥት የተነሳበት ዓላማ እና እየተጓዘበት ያለዉ መንገድ በጣም አደገኛ ስለመሆኑ ማጣቀሻ የሚያስፈልገዉ አይመስለኝም። መንግሥት በገዛ እጁ ራሱን ወደ ኪሳራ እየመራ ስለሆነ ከተደናበረ ሁሉ ጋር መደናበር ጥሩ አማራጭ አይሆንም። ለቤተ ክርስቲያንና ለሃይማኖት መቆርቆሩ ተገቢና የወቅቱ አጣዳፊ ጉዳይ ቢሆንም እርጋታ ይጠይቃል። በሥልጣን ላይ ያለዉ መንግሥት ይህን አጥቶት አይደለም መላተም የፈለገዉ፤ አጥፍቶ የመጥፋት አባዜ ተጸናዉቶት ነዉ። ይህ ባይሆንማ ጥንታዊቷንና ታሪካዊቷን የኢትዮጵያን ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ባልተደፋፈረ ነበር። ስለዚህ ከአበደ ጋር ማበድ ጥሩ አይሆንም። ጠላቶቻችን ብዙዎች ስለሆኑ ባገኙት ቀዳዳ ሾልከዉ እንዳይገቡ እያስተዋሉ ማድረግ ጥሩ መላ ነዉ። እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነታችንና እንደ የሃይማኖት ሰዉ ሰዉነታችን ማድረግ የሚገባንን ዘመኑን እየዋጀን እናድርግ። በጥበብ!! ብዕሩ ዘ-አትላንታ

    ReplyDelete