Monday, November 28, 2011

ከደሴ ደብረ ቤቴል ቅ/ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ምረቃ የቀሩት አቡነ ጳውሎስ የጌታቸው ዶኒን መኖሪያ ቤት መረቁ


  • መኖሪያ ቤቱ ብር 1.5 ሚልዮን ያህል እንደወጣበት ተነግሯል 
  •  አቡነ ጳውሎስ ያለጥንቃቄ ባደረጉት ጉዞ ጥያቄ ቀርቦባቸዋል 
  •  “አይ ቅዱስነትዎ፣ ተዋረዱ!! አሁን ይህ ለእርስዎ ክብር ነውን? የመቂ ሕዝብ እርሱን [ጌታቸው ዶኒን] ከእኛ የተሻለ ጠንቅቆ ነው የሚያውቀው፤ እንግዲህ የጌታቸው ዶኒ ጓደኛ ነው የሚልዎ!” /አቡነ ጎርጎርዮስ በድርጊቱ ማዘናቸውን ለአቡነ ጳውሎስ የገለጹበት መንገድ/
(ደጀ ሰላም፤ ኅዳር 15/2004 ዓ.ም፤ ኖቬምበር 25/2011/ )ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ፣ ባለፈው ሳምንት እሑድ፣ ኅዳር 10 ቀን 2004 ዓ.ም ከቀትር በኋላ በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት መቂ ከተማ ተገኝተው የሊቀ ካህናትጌታቸው ዶኒን መኖሪያ ቤት መርቀዋል፡፡ ከአዲስ አበባ 98 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በምትገኘው መቂ ከተማ ከድልድይ በላይ ተብሎ በሚታወቀው አካባቢ በ400 ሜትር ካሬ ስፋት ያረፈውና በ‹ሀ› ቅርጽ የተገነባው የሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ ቪላ 1.5 ሚዮን ብር ማውጣቱን ግለሰቡ በምረቃው ዕለት ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ባቀረበው አጭር ሪፖርት ገልጧል፡፡ በምረቃው ላይ በግለሰቡ ጥሪ የተደረገላቸው 200 ያህል እንግዶች የታደሙ ሲሆን ድግሱም ሞቅ ያለ እንደነበር ተዘግቧል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ወደ መቂ ያመሩት ከአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ገዳማት እና አድባራት በተዋጣው አራት ሚዮን ብር በተገዛው Vx8 ላንድክሩዘር መኪና ሲሆን ጉዟቸውም በምስጢር የተደረገ ነበር ተብሏል፡፡ ከፓትርያኩ ጋራ ብፁዕ አቡነ ገሪማ አብረዋቸው የነበሩ ሲሆን በመንገድም ለምሥራቅ ሸዋ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ስልክ በመደወል ሞጆ ላይ እንዲቀላቀሏቸው አድርገዋል፡፡ በዕለቱ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ በወንጂ የሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ምረቃ ሥነ ሥርዐት ላይ እንደነበሩ ከፓትርያኩ ጋባደረጉት የስልክ ልውውጥ ቢነግሯቸውም የተፈለጉበት ሳይነገራቸው በቀጭን ትእዛዝ እንዲያገኟቸው መደረጉ ተነግሯል፡፡
በአቡነ ጳውሎስ ድንገተኛ አመጣጥ የተገረሙት ብፁዕነታቸው ጉዞው የጌታቸው ዶኒን ቤት ለመመረቅ እንደሆነ ከፓትርያኩ ሲነገራቸው፣ “ይህ ለእርስዎ ጥሩ አይደለም፤ ውርደት ነው፤ ዝቅ ማለት ነው፤ ሰዉም ግምት ይወስድብዎታል፤” በማለት ሐሳባቸውን ለማስቀየር ጥረት ማድረጋቸው ተመልክቷል፡፡ ይሁንና ቀደም ብለው በጉዟቸው የቆረጡበት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ መንገዳቸውን በመቀጠል ወደ አንድ የቁጥጥር ኬላ ሲደርሱ [ዓለም ጤና አካባቢ] ያለ ጥበቃ/ አጀብ/ መጓዛቸው ጥሩ እንዳልሆነ ሲጠየቁ “ለሽምግልና ስለሆነ ነው” በሚል መልስ ሰጥተው አልፈዋል፡፡ መቂ ከተማ መግቢያ ላይ ሲደርሱ ጌታቸው ዶኒ ያሰለፋቸው ሞተርኬዶች አጅበው ለማስገባት ተዘጋጅተው የነበረ ቢሆንም አጀቡን የተመለከቱት ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ፣ “አይ ቅዱስነትዎ፣ ተዋረዱ!! አሁን ይህ ለእርስዎ ክብር ነውን? የመቂ ሕዝብ እርሱን [ጌታቸው ዶኒን] ከእኛ የተሻለ ጠንቅቆ ነው የሚያውቀው፤ እንግዲህ የጌታቸው ዶኒ ጓደኛ ነው የሚልዎ!” በማለታቸው ሹፌራቸው ፍጥነቱን ጨምሮ ወደፊት (ወደ ዝዋይ) እንዲፈተለክ ፓትርያኩ ቀጭን ትእዛዝ ይሰጣሉ፡፡
ከመቂ በስተደቡብ 27 ኪ.ሜ ርቃ ወደምትገኘው ዝዋይ ከተማ አቅጣጫ የተፈተለከው ሹፌርም ትንፋሹን የያዘው መኪናዋ ዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ስትገባ ነበር፡፡ ቅዱስነታቸውን ከብፁዕ አቡነ ገሪማ እና ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ጋ በያዘችው Vx8 ላንድክሩዘር መኪና ሽምጠጣ ግራ የተጋቡት ሞተሪስቶች ወደ ኋላ ቢቀሩም በቅዱስነታቸው ግብታዊ ‹የጉብኝት ዜና› የተረበሹት ዝዋያውያንም ለአቀባበሉ ሽር ጉድ ለማለት መጀመራቸው አልቀረም ነበር - ብዙም ሳይቆዩ ቅዱስነታቸው ፊታቸው መልሰው በመጡበት አቅጣጫ በረሩ እንጂ፡፡ ብልሃቱ ለጊዜው ከሞተርኬዶቹ አጀብ ለማምለጥ ቢሆንም ፍጻሜው ግን በብፁዕነታቸው የማስጠንቀቂያ ቃል መሠረት የጌታቸው ዶኒን ቪላ ቤት ምረቃ “ከዝዋይ ገዳም መልስ በአልፎ ሂያጅ /እግረ መንገድ/” የተደረገ ለማስመሰል መሆኑን ታዛቢዎች ተናግረዋል፡፡
ሽጉጥ ታጣቂው 
ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ
ይሁንና ብልሃቱ የቪላ አስመራቂውን ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒን የድግስ መርሐ ግብር በማዛባቱ የዕለቱ ‹የክብር እንግዳ› በሰዓቱ ባይገኙም እድምተኛው መስተናገዱ አልቀረም፡፡ ከቀኑ 8፡00 እንዲገኙ ፕሮግራም የተያዘላቸው አቡነ ጳውሎስም በጉዞው ላይ በተደረጉት ታክቲካዊ መስተካክሎች ምክንያት ከአንድ ሰዓት በላይ ዘግይተው ይደርሳሉ፤ ብዙው እድምተኛ ከድግሱ ተቃምሶ፣ መርቆ እየተሰናበተ በመውጣቱ በተወሰነ መልኩ ጭር ማለቱ ደጋሹን አሳጥቷቸዋል፤ “የረባ ዝግጅትም የለህ፤ ለእኔ እንኳ ኩኪስ አላዘጋጀህልኝም” - የአቡነ ጳውሎስ ትችት ሲሆን “ቅዱስ አባታችን፣ በምን አቅሜ/ገንዘብ?” የጌታቸው ዶኒ መልስ ነበር፤ ታዲያ ቦታውን ተመርተው ቢያገኙትም ቪላውን ያሳነፁበትን 1.5 ሚልዮን ብር ከየት አገኙት? - የታዛቢዎች ጥያቄ ነው፡፡     
የሆነው ሆኖ በኢትዮጵያ ባንዲራ በደመቀው ቅጽር አልፈው ወደ ሳሎኑ የዘለቁት አቡነ ጳውሎስ በትልቅ አልበም ተሠርቶ የተሰቀለውን የራሳቸውን ምስል ለመመልከት ታድለዋል፡፡ ወዲያውም ጌታቸው ዶኒ ለፓትርያኩና ለቀሩት እንግዶች ሪፖርት ያቀረበ ሲሆን በሪፖርቱም ለቪላው 1.5 ሚዮን ብር ወጪ ማድረጉን ተናግሯል፤ በሥራውም ያገዙትን አምስት ያህል ሰዎች አመስግኗል፡፡
ከአንድ ሰዓት ላልበለጠ ጊዜ በጌታቸው ዶኒ ቪላ የቆዩት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ፣ ወደ ሐዋሳም ለማምራት ዕቅድ ነበራቸው ቢባልም የምጽአታቸው ወሬ ቀደም ብሎ ተሰምቶ ኖሮ በከተማው ቀናዒ ምእመናንና በሌሎቹ መካከል ፍጥጫ የመፍጠር አዝማሚያ በመስተዋሉ ምክንያት፣ ከክልሉ የፍትሕ እና ጸጥታ ቢሮ ለፓትርያኩ በደረሳቸው ማሳሰቢያ መሠረት ዕቅዳቸው ሰርዘው ወደ አዲስ አበባ መመለሳቸው ታውቋል፡፡
ባለፈው ዓመት ግንቦት ርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ሃይማኖቱ እና ሃይማኖተኝነቱጥያቄ ተነሥቶበት የምልአተ ጉባኤውን አባላት ያከራከረው ጌታቸው ዶኒ፣ ከፕሮቴስታንት የእምነት ተቋማት ጋራ ያለው ያልተገባ ግንኙነት በማስረጃ መረጋገጡ ከተነገረና፣ ፓትርያኩ ያለ ሲዳሞ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ዕውቅና የሀ/ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ አድርገው ከሾሙበት ሥልጣኑ በሐዋሳ ምእመናን ጠንካራ ተቃውሞና በምልአተ ጉባኤው ውሳኔ ከተነሣ በኋላ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የገዳማት አስተዳደር መምሪያ ምክትል ሓላፊ ሆኖ መሾሙ ይታወሳል፡፡ ይሁንና ከፓትርያኩም ይሁን በዙሪያቸው ከተሰለፉ ሕገ ወጥ ግለሰቦች ራሱን ማግለሉን ሲነገርለት የቆየው ጌታቸው ዶኒ አሁን ቪላውን ለማስመረቅ ፓትርያኩን መጋበዙ፣ ፓትርያርኩም የቁርጥ ቀን ወዳጃቸውን ጥሪ ሳይንቁ መገኘታቸው አነጋጋሪ ሆኗል - ጌታቸው ዶኒ ለ18 ዓመት በዓለ ሢመታቸው ላሠራላቸው ሐውልተ ስምዕ ውለታውን ለመመለስ፣ በዚህ ዓመት በልዩ ሁኔታ እንዲከበር ‹ተወስኖ› ከወዲሁ እንቅስቃሴ ለተጀመረበት 20 ዓመት በዓለ ሢመታቸው ‹የላቀ ትብብሩን› የሚጠይቅ ፈለማ/ቅድሚያለመያዝ ይሆን?
ርግጡን ወቅቱ ሲደርስ የምናየው ሲሆን የሚዲያ ተቺዎች ግን ፓትርያርኩ የጌታቸው ዶኒን ቪላ መመረቃቸው ከመንፈሳዊ አባትነታቸው፣ ከቀረቤታቸውም አኳያ የሚጠበቅ ቢሆንም መስከረም 18 ቀን 2004 ዓ.ም ቅዳሴ ቤቱ በተከበረው በታላቁ የደሴ ደብረ ቤቴል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በዓል ላይ ካለመገኘታቸው ጋራ በማያያዝ ክፉኛ ትችታቸውን ይሰነዝሩባቸዋል፡፡ ለጉዳዩ ቅርበት የነበራቸው ምንጮች እንደሚናገሩት ቅዳሴ ቤቱ ከተከበረበት አንድ ቀን ቀደም ብሎ ቅዱስነታቸው መስከረም 15 ቀን በመኪና አደጋ ሕይወታቸው ያለፈው ዘጠኝ የክልል ትግራይ ፖሊስ ኪነት ቡድን አባላት ቀብር ሥነ ሥርዐት በተከናወነበት መቐለ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ነበሩ፡፡
ደሴ ደብረ ቤቴል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን
የቋሚ ሲኖዶስ አባላትን አስከትለው በመሄድ በቀብር ሥነ ሥርዐቱ ላይ የማፅናኛ መልእክት ያስተላለፉት ቅዱስነታቸው በተከታዩ ቀን ለሚካሄደው የደሴ ደብረ ቤቴል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ቅዳሴ ቤት ቀደም ብለው በራሳቸው ጥያቄ ፕሮግራም አስይዘው የነበረ ቢሆንም ሳይገኙ ወደ አዲስ አበባ ተመልሰዋል፡፡ 18 ዓመት እና ዘጠኝ ሚልዮን ብር በፈጀው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ቅዳሴ ቤት ላይ የደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስን ጨምሮ የደቡብ ጎንደር ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እንድርያስ ከደብረ ታቦር፣ የሰሜን ወሎ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ከወልዲያ ማልደው ተጉዘው ተገኝተው ነበር፡፡ በደቡብ ትግራይ የማይጨው ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ በቅዳሴ ቤቱ ቡራኬ ላይ ለመገኘት አስበው የነበረ ቢሆንም በፓትርያርኩ ጥሪ ወደ መቐለ ተመልሰዋል፡፡
(ፎቶ) የደሴ ደብረ ቤቴል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ምረቃ፤ የእስልምና እና ፕሮቴስታንት እምነቶች ተወካዮች ባሉበት
በ2002 ዓ.ም በዚያው በደሴ ቅድስት አርሴማ ወአቡነ አረጋዊ ገዳም ይዞታ ጋ በተያያዘ ተፈጥሮ በነበረው ግጭት 12 ምእመናን ቆስለው አራት ምእመናን ሲሞቱ ፓትርያርኩ ኀዘናቸውን አለመግለጻቸውን የሚስታውሱት የከተማው ነዋሪዎች፣ “አሁን ደግሞ ቤተ ክርስቲያንም አሠርተን መርቁ ብለን ብንጠራቸው አልመጡም፤ አባትነታቸው ከወዴት አለ?” ሲሉ ቅሬታቸውን ገልጸዋል፡፡ የምእመኑና የአገልጋዩ ጠንከር ያለ ቅሬታ በተለያየ መንገድ የደረሳቸው የሚመስሉት ፓትርያርኩም በ30ው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ላይ ልካኑ በይፋ ይቅርታ መጠየቃቸው ተዘግቧል፡፡
 ቃላዊ ይቅርታው የሚገፋ ባይሆንም በአስደናቂ ኪነ ሕንፃው ‹ዳግማዊ ላሊበላ› በተሰኘው፣ የክርስቲያን ሙስሊሙ ማኅበራዊ መግባባትና መረዳዳት ጎልቶ በታየበት በደሴ ደብረ ቤቴል ቅዱስ ገብርኤል ቅዳሴ ቤት ላይ “የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዝዳንት” የሆኑት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከመቐለ - ደሴ 262 ኪ.ሜ ብቻ ገሥግሠው በክብረ በዓሉ ላይ አለመገኘት የግለሰቡን ጌታቸው ዶኒን ቪላ ለመመረቅ 98 ኪ.ሜ ለመጓዝ ካሳዩት ብልሃት አንጻር ዳግመኛ ጥያቄውን ማጫሩ አልቀረም፡፡

ቸር ወሬ ያሰማን፣ አሜን

1 comment:

  1. oh God please remove Tehadiso and Jihadists from our Church

    ReplyDelete