Saturday, December 3, 2011

የግብረሰዶማውያኑ ስብሰባ የፈጠረው ትኩሳት



(From Reporter) ዛሬ በአዲስ አበባ ከተማ የሚጀመረው 16ኛው ዓለም አቀፍ የኤችአይቪ/ኤድስና የአባላዘር በሽታዎች(አይካሳ) ጉባዔን አስታክኮ፣ መሰንበቻውን የግብረሰዶማውያን ቡድን እያካሄደ ያለውን እንቅስቃሴ ከተለያዩ ወገኖች ተቃውሞ ሲቀርብበት ነበር፡፡
 በተለይ የሃይማኖት መሪዎች ለትናንት በጁፒተር ኢንተርናሽናል ሆቴል ለማካሄድ ቀጠሮ ተይዞለት ስለነበረው ስብሰባ ምንነትና ይዘት የሚያሳይና የሚኮንን መግለጫ ሊሰጡ ካሉ በኋላ መሰረዙን በሪፖርተር ባለፈው ረቡዕ ማውጣታችን ይታወሳል፡፡ ግብረሰዶማውያኑ ስብሰባቸውን በተባበሩት መንግሥታት ስብሰባ ማዕከል ማካሄዳቸውም እየተነገረ ነው፡፡
ትናንት ማለዳ ላይ በስብሰባ ማዕከሉ የግብረሰዶማውያኑ ስብሰባ እንደሚካሄድ ሰምተው ለተቃውሞ የወጡ ጥቂት ሰዎች በፖሊስ ተበትነዋል፡፡ ፖሊስ ለተቃውሞ የወጡትን የበተነው በሕጋዊ መንገድ የወጡ አይደሉም በማለት ነው፡፡ ድርጊቱን በምስል ለማስቀረት በስፍራው የተገኘው የሪፖርተር ፎቶ ጋዜጠኛም በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ውሎ ያነሣቸው ምስሎች ቅጂዎችም ተወስደዋል፡፡
በእንዲህ ዓይነቱ አወዛጋቢ ሁኔታ ውስጥ ለአምስት ቀናት የሚካሄደው የአይካሳ ጉባዔ ዛሬ ይጀመራል፡፡ ከጉባዔው ባሻገር፣‹‹የግብረሰዶማውያኑ ስብሰባ የፈጠረው ትኩሳት›› በሚል ርእስ በተለያዩ ወገኖች የተሰጡትን አስተያየቶችና ምልከታዎችን የሚያሳየውን ሐተታ ከዚህ በታች ይመልከቱ፡፡

ሰዶማውያን ማለት ግብረሰዶምን የሚፈጽሙ ይህም ወንድ ከወንድ ሴት ከሴት ጋር ዝሙት የሚያደርጉ ማለት እንደሆነ መዝገበ ቃላቱ ይፈታዋል፡፡ ግብረሰዶማዊነት የሚለውን ስያሜም የተገኘው በአደባባይ ለመጀመርያ ጊዜ ድርጊቱን በፈጸሙ ሰዎች አገር ስም ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን በድረ ገጹ ባወጣው ጽሑፍ እንደተገለጸው፣በዘመናት ታሪክ ውስጥ በእግዚአብሔር ዘንድ መጸጸትን፣ የቁጣ ጅራፍን፣ መዓትንና እጅግ መራራ ቅጣትን ካስከተሉ እኩያን ተግባራት መካከል ተፈጥሮ ከሚያዘው ውጪ ወንዶች ከወንዶችና ሴቶች ከሴቶች ጋር የሚያደርጉት ግንኙነት አንዱ ነው፡፡ 

ይህ በቅዱስ መጽሐፍ የተግባሩ እኩይነት የቅጣቱ አስከፊነት በተጨባጭ የተነገረለት ግብረሰዶማዊነት ሳይቋረጥ የዘመናትን ድንበር ተሻግሮ ነውርነቱ እንደ መልካም ተግባር ተቆጥሮ በአራቱ መአዝነ ዓለም እየተፈጸመ ይገኛል፡፡ በተለይም በሥልጣኔ ወደፊት ተራምደዋል የሚባሉት ምዕራባውያን ድርጊቱን ከ1980ዎቹ አጋማሽ ጀምረው በምስጢርና በድብቅ መፈጸማቸውን ትተው ወደ አደባባይ ካወጡት ሰነባብቷል፡፡

የድርጊቱም ፈጻሚዎች ቁጥር ከዕለት ወደ ዕለት እጅግ እያሻቀበ መጥቷል፡፡ አንዳንድ ምዕራባውያን አገሮች በሕጋቸው ያጸደቁት ግብረሰዶማዊነትን እኩያን የሆኑ አንዳንድ የኪነጥበብ ሰዎች ሙያውን ለወሲብ ንግድ ማስፋፊያ በማዋል በፊልም፣ በሲኒማ እየተወኑ በእርስ በእርስ ጦርነት፣ በረሐብ፣ በኤች አይ ቪ/ኤድስ ቁምስቅላቸውን ለሚያዩ አፍሪካውያን ጭምር እንካችሁ እያሉ ነው፡፡ 

ግብረሰዶማዊነት ወደ ኢትዮጵያ የገባው ለተለያየ ጉዳይ ወደ አገሪቱ በሚመጡ የወጭ አገር ዜጐችና በውጩ ዓለም ኑረው በተመለሱና በሚመለሱ አንዳንድ ኢትዮጵያውን ጭምር መሆኑን ጥናቶች ይጠቁማሉ፡፡ እነዚህ ወገኖች የዚህ አጸያፊ ድርጊት ሰለባ የሆኑትና ሰለባ የሚያደርጉት ቀደም ሲል በእነርሱ ላይ ካለፈቃዳቸው በግብረሰዶማውያን ተገደው በመደፈራቸው በመሆኑ ይነገራል፡፡ በተለያዩ ጥቅማጥቅም በመታለል በተፈጸመባቸው ወሲባዊ ጥቃት የእነርሱን የሕይወት መስመር ለመከተል እንዳበቃቸው ከግብረሰዶማውያኑ የተገኙ መረጃዎች እንደሚጠቁሙ በዘርፉ የተደረጉ ጥናቶች ያስረዳሉ፡፡ ግብረሰዶማውያኑ ዛሬ በአዲስ አበባና በተለያዩ ከተሞች ኅቡዕ ድርጅት በማቋቋም፣ በካፌዎች እና በተለያዩ የመዝናኛ ቦታዎች ድርጊቱን እያስፋፉ ይገኛሉ፡፡

‹‹ውግዘት የሚገባው ተግባር›› በሚል ርእስ ማኅበረ ቅዱሳን ባወጣው ጥናት፣ በተለያዩ ወገኖች ታዝሎ ኢትዮጵያ የገባው ግብረሰዶማዊነት በተለይም ዕድሜያቸው ከ10-14 በሚደርሱ የጐዳና ተዳዳሪዎች፣ በአንዳንድ መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት እገዛ በሕፃናት ማሳደጊያ ማዕከል በሚኖሩ አዳጊዎች ላይ ሳይቀር ድርጊቱ እየተፈጸመባቸው ነው፡፡ የድርጊቱ ፈጻሚዎች ሕፃናትንና ወጣቶችን ለማማለል የተለያዩ አደንዛዥ ዕፆችን፣ ከረሜላ፣ ቸኮላት መሳይ ማደንዘዣ፣ ጫት፣ አልኮል እና የሚጤስ ነገር በመጠቀም ካደነዘዙአቸው በኋላ ድርጊቱን ይፈጽሙባቸዋል፡፡ እንዲሁም ጐልማሶችን በተለያዩ መሣሪያዎች በማስፈራራት እንደሚደፍሯቸው ጥናቶች ያመለክታሉ፡፡

ዓለም በቴክኖሎጂ ምጥቀት ወደ አንድ መንደር እየተለወጠች በመምጣቷ በዓለም ላይ የሚከሰት ሠናይም ሆነ እኩይ ለሆነ ነገር ሁሉ አገራት ተጋላጭ ናቸው፡፡ ከአንድ አገር ወደሌላ በሚደረግ ዝውውር፣ የቴክኖሎጂ የኢንፎርሜሽን እና ከዚሁ ጋር አብሮ በተለያዩ መንገዶች በሚደረጉ የእኩይ ልማድ ልውውጥ ምክንያት የምዕራባውያንን ፈለግ ለመከተል ደፋ ቀና የሚሉ አንዳንድ ወገኖች በአገራችን ብቅ ማለታቸው እየተሰማ ነው፡፡ በመንፈሳዊ ሥነ ምግባር በፈሪሐ እግዚአብሔር እየተጓዘች በኖረችው አገራችን እንደዚህ ዓይነት ድርጊት ለመፈጸም የሚንቀሳቀሱ ሰዎች መነሳታቸው እጅግ ያሳዝናል፤ ያሳስባልም፡፡ በቅድስት አገር ኢትዮጵያ የድርጊቱ ፈጻሚዎች እንቅስቃሴ ከተሰማበት ወዲህ ድርጊቱ ያሳሰባት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታኅሣሥ 13 ቀን 2001 ዓ.ም. በአንድ ግብረ ሠናይ ድርጅት አስተባባሪነት «ግብረሰዶማዊነት መብት ወይስ የዝሙት ከፍታ ጫፍ» በሚል ርእስ ከሃይማኖት ከባህል፣ ከታሪክና ከሳይንስ አኳያ በአፍሪካ ኅብረት በመከረበት ወቅት ድርጊቱን በማውገዝ አቋሟን ገልጻለች፡፡ ከተላለፈው የአቋም መግለጫ የሚከተለው ይጠቀሳል፡፡ «በሀገራችን ሕገ መንግሥት ውስጥ እንደተመለከተው ጋብቻ ክቡር መሆኑን ለቤተሰብም ጥበቃ የሚደረግለት መሆኑንና በሀገራችን ካሉ የሃይማኖት እሴቶች ተቃራኒ የሆኑ ጉዳዮች በማንኛውም መስፈርት ግብረሰዶማዊነት መብት ተደርጎ ተቀባይነት ማግኘት የማይገባው በመሆኑ ጉዳዩ የሚመለከተው አካል ይህንን አውቆ እርምጃ እንዲወስድ እንጠይቃለን፡፡» 

‹‹ግብረሰዶማዊነት›› በሚል ርእስ በዩናይትድ ፎር ላይፍ የተዘጋጀ መጽሐፍ በዓለም አቀፍ የበሽታዎች መግለጫ ዝርዝር ላይ ግብረሰዶማዊነት እንደበሽታ ተቆጥሮ ለብዙ ዓመታት መስፈሩን ያትታል፡፡ ይኸው መጽሐፍ እንደሚለው፣ በአሜሪካ የአእምሮ ሕክምና ማኅበር ግብረሰዶማዊነትን ከአእምሮ መዛባት ጋር በተያያዘ የሚፈጠር በሽታ አድርጐ ይቆጥረው ስለነበር በአእምሮ በሽታዎች ዝርዝር ውስጥ ተመዝግቦ ቆይቷል፡፡ 

ነገር ግን ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ከሁለቱም ሥፍራዎች ከበሽታዎች ዝርዝር ውስጥ እንዲሰረዝ ተደርጓል፡፡ በርካታ ባለሙያዎች ከበሽታዎች ዝርዝር አንዳይሰረዝ ያቀረቡት ተቃውሞ ተቀባይነት አላገኘም፡፡ ግብረሰዶማዊነት ከበሽታዎች ዝርዝር ሲሰረዝ የቀረበው ምክንያት አንድ ሰው ግብረሰዶማዊ መሆን ወይም አለመሆን ‹‹መብት›› ነው በሚል አመለካከት ነበር፡፡ 

መጽሐፉ በ1996 ኢትዮጵያ ውስጥ የተካሔደውን አንድ ጥናታዊ መረጃ ዋቢ አድርጎ እንደዘገበው ከሆነ፣ ሰዎችን ወደዚህ ሕይወት እንዲገቡ ያደረጓቸው የውጭ አገር ዜጎች፣ በውጭ አገር የሚኖሩና ወደ ውጭ አገር ለንግድ ብዙ ጊዜ የሚመላለሱ ኢትዮጵያውያን ናቸው፡፡ በአጠቃላይ እንደ ችግር ሲታይ መነሻ ሆኖ የቀረበው የውጭ ተጽዕኖ ሲሆን በአገራችን ሕጻናት ላይ ጥቃት ፈጽመው የተያዙ፣ አሁንም በዕርዳታ ስም ወደ አገራችን በመግባት ይህን ጥቃት እያደረሱ ያሉ የውጭ ዜጎች ለአብነት የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ 

በጥናቱም መሠረት እርስ በርሳቸው የሚጠራሩበት የተለያዩ ስሞች ሲኖራቸው አብዛኛው የሚጠቀሙበት ስም ‹‹ዜጋ›› የሚል ነው፡፡ አንዳንዴ ይህ ስያሜ ‹‹ኦፔራ››፣ ‹‹ወገን›› በሚባሉ ስያሜዎች እንደሚተኩም መጽሐፉ ከጥናት የተገኘውን መረጃ ጠቅሶ አስፍሯል፡፡ ‹‹ጅራሬ›› ለወሲብ ንግድ ወይም የአዳር ጓደኛ ፍለጋ አደባባይ መውጣት የሚያመለክት ቃል ሲሆን፤ ‹‹ብርታሎ›› (ቆምጬ) ከገጠር ለሚመጡ ግብረሰዶማውያን የወጡ መጠሪያዎች ናቸው፡፡ ‹‹ጀሲካ ሞናሊዛ›› የመሳሰሉትም ለከተሜ ግብረ ሰዶማውያን የተሰጡ መጠሪያና ‹‹ቆሚ›› ገንዘብ ለማግኛ እንደ ሥራ በመንገድ ላይ የሚቆሙ መሆናቸውን አመላክቷል፡፡ ‹‹መክተብ›› ማለት ደግሞ ይህን የሕይወት መንገድ የማያውቁትን ወደ ግብረ ሰዶማዊነት የሕይወት ልምምድ መመልመል ማለት ነው፡፡ እርስ በርሳቸው የሚጠራሩበት የቁልምጫ ስም ‹‹እሷ›› የሚል ነው፡፡

በዚህ ጥናታዊ ጽሑፍ መሠረት በአዲስ አበባ መሃል ከተማ በታወቁ መንገዶች፣ በቡና ቤቶች፣ ካፍቴሪያዎችና ኮሪደር ቦታዎች ላይ አንዱ ሌላውን እንደሚያገኙ ተጠቁሟል፡፡ በተለይ የሦስት ቡና ቤቶችና የሁለት ካፍቴሪያዎች ባለቤቶች እነሱ በመሆናቸውና የተቀጠሩት አስተናጋጆችም ግብረሰዶማውያን በመሆናቸው ዘና ብለው ለመገናኘት አስችሏቸዋል፡፡ ወደ እነዚህ ሥፍራዎች ሲመጡ ሁለት ወይም ሦስት ሆነው ተቃቅፈው ወይም እጅ ለእጅ ተያይዘው ይገባሉ፡፡  ተመሳሳይ የጾታ ጋብቻ ሕጋዊ እንዲሆን የሚታገሉ አንዳንድ ድርጅቶች እንዳሉም አንዳንድ ምንጮች ይገልጻሉ፡፡ የእነዚህ ድርጅቶች ታሪካዊ ዳራ /ጀርባ/ ሲጠና ግብረሰዶማዊነት በሕግ እንዲፈቀድ የሚንቀሳቀሱት የኢትዮጵያ ሕዝብ ችግር /ፍላጎት/ ስለሆነ ሕዝቡን ለመርዳት ብለው ሳይሆን ኢትዮጵያ የአፍሪካ መዲና በመሆንዋ ለራሳቸው ስውር ዓላማ ማስፈጸሚያ ስለምትመቻቸው ነው፡፡ ይኸውም ኢትዮጵያ ይሁን ብላ የምትፈቅደው ማናቸውም ነገሮች በሌሎች አፍሪካ አገሮች ላይ ተጽዕኖ እንደሚያመጣ በማሰብ አገራችንን እንደ መግቢያ በር አድርገው በሌሎች የአፍሪካ አገሮችም እንቅስቃሴያቸውን ለማስፋፋት ነው፡፡ 

•    ‹‹በጤናማ የኑሮ ዘይቤ ወደ ኅብረተሰቡ እንዲቀላቀሉ የበኩላችን ጥረት ማድረግ አለብን››
ዶ/ር ሥዩም አንቶንዮስ የዩናይትድ ፎር ላይፍ ኢትዮጵያ ዋና ዳይሬክተር
ዓለም አቀፍ የግብረሰዶማውያን ስብሰባ እንደሚካሔድ መነገሩን ተከትሎ ተገቢ አለመሆኑን ለማመልከት ባለፈው ሐሙስ ኅዳር 21 ቀን 2004 ዓ.ም. ሳር ቤት በሚገኘው የኢንተርናሽናል ኢቫንጄሊካል ቸርች የንስሐና የምልጃ ፕሮግራም ለቤተ ክርስቲያን መሪዎች ተካሒዶ ነበር፡፡ 

ሐኪሙ ዶ/ር ሥዩም አንቶንዮስ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ፕሮግራሙ የተዘጋጀው በግብረሰዶም ጉዳይ ቤተ ክርስቲያን ሰፊ ግንዛቤ እንድታገኝ ለማድረግ ነው፡፡ ያለው ችግር ምን ይመስላል? ግብረሰዶማዊነት ምንድን ነው? የሚያስከትላቸውስ ዘርፈ ብዙ ጠንቆች ምን ይመስላሉ? ከሳይንሱም ሆነ ከመጽሐፍ ቅዱስ እይታ ለማየት ተሞክሯል፡፡ በምድሪቱ ላይ ላለው ቀውስ ጸሎትና ምልጃ ነው የተካሔደው፡፡ ሰሞኑን በአዲስ አበባ በተከሠተው ሁኔታ ግብረሰዶማውያኑ እናደርጋለን ብለው ያሰቡት ስብሰባ በምድሪቱ ላይ መጥፎ ተጽዕኖ እንደሚያመጣ ስለሚታመን ያ እንዳይሆን በእግዚአብሔር ፊት የምልጃ ጸሎት ተደርጓል፡፡

የቁጥራቸው መብዛት ማነስ መሆኑ ብቻ አይደለም፡፡ አፍሪካን በግብረሰዶማዊነት እንዴት መድረስ እንችላለን? ብለው የሚነጋገሩ አካላት ስብሰባ ማድረጋቸው ከፍተኛ ተጽዕኖ ይኖረዋል፡፡ 

ግብረሰዶማዊነት ለትውልድ ጥፋት የሆነ፣ ጥፋትን የሚያመጣ፣ ከፍተኛ ማኅበራዊ ቀውስን የሚፈጥርና ትውልድን የሚያመክን ነገር ነው፡፡ ይኼ ነገር ኅብረተሰባችን መካከል እየተስፋፋ በመጣ ቁጥር የአገርን ልማትና ዕድገት ይጎዳል፡፡  

ኅብረተሰቡ ይኸን ነገር አይፈልገውም፤ በሕጋችንም ተቀምጧል፡፡ ሕገ መንግሥቱም አይደግፍም፡፡ ሁሉም ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ እምነቶች አጥብቀው ይቃወማሉ፡፡ ስለዚህ የውጭ ድርጅቶች በዕርዳታ ስም ይኸን ተጽዕኖ ቢያደርጉም ዕርዳታው ቢቀር ይሻላል እንጂ ይኸንን ዓይነት አስተሳሰብ መቀበላችን ለኛ ሰፊ አደጋና የከፋ ቀውስ ሊያመጣ የሚችል ነው፡፡ ተጽዕኗቸው አለ፤ በግልጽ የሚናገሩት ነው፡፡ 

ቆም ብለን በደንብ አስበን አመዛዝነን የትኛው የተሻለ ነው? የትኛው ያዋጣናል ብሎ ማሰቡ ተገቢ ይመስለኛል፡፡ መንግሥታችንም እንደዚህ ዓይነት አቋም እንዳለው እናምናለን፡፡ ከሃይማኖት መሪዎች የሚጠበቅ ሥራ አለ፡፡ እንደሚያስከትል ማስተማር ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይኸ በደንብ አልተሠራም ክፍተት አለ፡፡ 

ግብረሰዶማውያን ሰዎች ናቸው፡፡ በሰውነታቸው ሊጠሉ አይገባቸውም፡፡ ልንጠላው ወይም ልንጸየፈው የሚገባን ግብረሰዶማዊነትን ወይም ድርጊቱንና የኑሮ ዘይቤውን ነው፡፡ ሰውየውን ከድርጊቱ መለየት መቻል አለብን፡፡ በዚህ ሕይወት ውስጥ ያሉት ሰዎች በሥነ ልቦና ቀውስ ውስጥ ያሉ ለመሆናቸው ብዙ ሳይንሳዊ ምርምሮች ያረጋግጣሉ፡፡ ስለዚህ እነዚህን የኅብረተሰብ ክፍሎች ተገቢውን የምክር አገልግሎትና ድጋፍ በመስጠት ጤናማ የኑሮ ዘይቤ ወደ ኅብረተሰቡ እንዲቀላቀሉ ባለሙያዎችም የሃይማኖት አባቶችም የበኩላችንን ጥረት ማድረግ አለብን፡፡ 


ይህን የምናደርግበት ዋናው ዓላማ ግብረሰዶማዊነት ኅብረተሰብን የሚያጠፋ ነገር ስለሆነ፣ የሰውን ሰብዕና የሚያበላሽ ማንነቱን የሚያጎድፍ ለብዙ የጤና ቀውሶች የሚያጋልጥ፣ ለአካላዊና ሥነ ልቦናዊ ለማኅበራዊ ቀውስም የሚዳርግ ስለሆነ ጤናማ ሥራ ፈጣሪ ዜጋ እንዳይኖረን የሚያደርግና የአገር ልማትና ዕድገት የሚያጠፋም ስለሆነ ነው፡፡ ይህንን አደጋ ለመቀነስ ሁላችን ባለን አቅም ሁሉ መረባረብ አለብን፡፡ በዚያ ሕይወት ውስጥ ያሉት ደግሞ የሚወጡበትን መንገድ የተሐድሶ ማዕከላትን በማቋቋም መርዳት አለብን፡፡ እውነቱን ለማስተማር ሰፊ ሥራ ይጠበቅብናልና የሚመለከተን ሁላችን ባለሙያውም፣ ጋዜጠኛውም፣ አስተማሪውም፣ የሃይማኖት አባቱም፣ መንግሥትም ሁላችን ተባብረን ለዚህ ነገር መፍትሔ መፈለግ ይጠበቅብናል፡፡


  • •    ‹‹የሃይማኖት መሪዎች ሊጮሁ ይገባል››
ሼክ አደም ካሚል የእስላማዊ ጥናት ተመራማሪ     
እስልምና ግብረሰዶምን በጣም ይኮንነዋል፡፡ ማንኛውም ሃይማኖት አይደግፈውም፤ የተጠላ ነው፡፡ 

ምዕራባውያን እንደፋሽን አድርገው የሚጠቀሙበት በእነርሱ አገር እንደ ሕገ መንግሥትም አድርገው ከመብት ጋር የተያያዘ ነው የሚሉት ከሃይማኖቱ ውጭ የሆኑ ፓርቲዎችና መሪዎች የሚሰነዝሩትና የሚቀይሱት ስልት ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ 

ኢትዮጵያ በታሪክ የታወቀች ሦስቱን ታላላቅ ሃይማኖቶች የተቀበለችና ያስተናገደች አገር ነች፡፡ ከዚህ አንጻር መሠረተ እምነቱን ይዞ የሚሔድ ሕዝብ ያለባት የረዥም ጊዜ ታሪክ ያላት አገር እንደነዚህ ያሉ አስቀያሚና ቆሻሻ ነገሮች በአገራችን ባለፈው ትውልድ ታይቶም ታስቦ ታልሞ አይታወቅም ነበር፡፡ አሁን የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ በረቀቀ ቁጥርና ሦስተኛው ዓለም ትውልድ አልባ፣ ዘር አልባ እንዲሆን በተለይ የተለያዩ ነገሮች ይቀይሱብናል፡፡ ለአገራችን ተስማሚ ያልሆኑ ባህሎች፣ ወጎችና ልምዶች እንዲንፀባረቁ ዕቅድ ተነድፎ ልምዳችንን፣ ክብራችንን ጠብቀን እንዳንሔድ የሚደረግ ሴራና ዳባ የተዘረጋ ይመስለኛል፡፡ መነሻ የሚያደርጉት ድህነታችንን፣ ችግራችንን ነው፡፡ እና በዕርዳታና በበጎ አድራጎት ስም የሚገቡት ድርጅቶች ሁሉ ነፃ ናቸው ማለት አንችልም፡፡ ይኼ ዴሞክራሲ ማለት አይደለም፤ የሰው መብት ነው ማለትም አይደለም፡፡ ሰውን የሚያጠፋ፣ ሰውን የሚያዳክም ነው፡፡ ችግራችን ኋላቀርነትና ድህነት ነው፡፡ ከዚያ ለመውጣት በሚጥርበትና ሕዝቡ ወደ ሥራ ገብቶ በተለያዩ እምነቶቹ ተቻችሎ የሚኖርበት አገር ስለሆነ ይኸንን ክብራችንን ጠብቀን መሔዳችን የሚያስኮርፋቸው አካሎች በውጩ በተለይ በምዕራቡ ዓለም ያሉ ይመስለኛል፡፡ በእስልምና በቅዱስ ቁርዓን በግልጽ የተቀመጠ አንቀጽ አለ፡፡


ሉጥ የተባሉ ነቢይ ነበሩ፡፡ በዚያን ጊዜ ዜጎቻቸው እንዲህ ያለ ተግባሮች በሚፈጽሙበት ጊዜ አላህ በጅብሪል አማካይነት ማስጠንቀቂያ ሰጥቶ ባለመቀበላቸው መሬቱን ገልብጦ እንዲቀጡና እንዲጠፉ አድርጓቸዋል፡፡ ስለዚህ እንደዚህ ያሉ ነገሮች የመጥፊያችን ዋዜማ ነው ማለት እችላለሁ፡፡ ስለዚህ ሕዝቡ ሊያውቀው የሚገባው የራሷ የሆነ ባህል አላት፡፡ በክርስትናም፣ በእስልምናም ተከብሮ የቆየ ለሌላው አርአያ የሆንበት ሌላው ቀርቶ በክርስትና በዓላት ከአውሮፓ እየመጡ እምነታቸውን፣ ባህላቸውንና ልምዳቸውን እየቀሰሙ እየተማሩ የረሱትን የእምነት ባህላቸውን እንኳ እያዩ ነው ያሉት፡፡ 

እኛን የሚያሳስበው ሌላው ነገር በከተማችን ሴተኛ አዳሪ መብዛት ነው ትዳር አልባ ከሆንን ወቅቱ አሁን የምንጮህበት ጊዜ ይመስለኛል፡፡ መቅሰፍቱ ለተወሰነ እምነት ተከታይ ብቻ የመጣ አይደለም፡፡ በኢትዮጵያውያን ላይ ያንዣበበ የተከሠተ አደጋ ነውና የሃይማኖት መሪዎች ሊጮሁ ይገባል፡፡


ቤተ ክርስቲያንም፣ መስጊዶችም መጮህ አለባቸው፡፡ ለዚህ ጉዳይ ተብሎ አጀንዳ ተቀርጾ ኮንፈረንስ መካሔድ አለበት፤ በተለይ ወጣቱ የሚሳተፍበት መድረክ ተከፍቶ የሃይማኖት መሪዎች ተሳትፈውበት ከእምነት አንጻር አደጋው ምን እንደሆነ መግለጫ የሚሰጡበት መድረክ መከፈት ይኖርበታል፡፡ መንግሥትም ኋላቀርነትን እዋጋለሁ እያለ ዕቅድ በሚያወጣበትና አገራችን መካከለኛ ገቢ ወዳላቸው አገሮች ትሔዳለች ሲባል እንደዚህ ያሉ መቅሰፍቶች መከሠታቸው ለምናፈራው ትውልድ አደጋና አገሪቱን የሚጎትት ስለሆነ ዕርምጃ ሊወሰድበት ይገባል፡፡ ሆቴሎችን፣ ቡና ቤቶችን፣ ምሽት ቤቶችን መቆጣጠር እንጂ ከመብት አንጻር ብቻ መታየት የለበትም፡፡ 


በውጭ አገር ካሉት ኢትዮጵያውያንም ለአገራችን ባዕድ የሆነ ነገርም የሚያመጡ አሉ፡፡ የኢትዮጵያ ማኅበረሰብም ነገሩ ሊያሳስባቸው ሊነጋገሩበትም ይገባል፡፡ ኤምባሲዎችም እየሰበሰቡ ማነጋገር ቱሪስቶች ወደ አገር ቤት በሚመጡበት ሰዓትም የአገራችን ባህልና ክልክል የሆነውን ነገርንም ማሳወቅ ይገባቸዋል፡፡ 

•  ‹‹ጢሱ እንዳይታይ ከመጣር ይልቅ እሳቱ እንዲጠፋ ብንሠራ የተሻለ ውጤት እናመጣለን››

ዲያቆን ዳንኤል ክብረት
ኢትዮጵያ የሃይማኖት ሀገር ናት፡፡ ከ90 በመቶ በላይ የሆነው ሕዝቧ በእምነቱ ግብረ ሰዶምን ይቃወማል ብቻ ሳይሆን ይጸየፋል፡፡ የሀገሪቱ ሕጎችም ግብረ ሰዶማዊነትን በወንጀልነት ይፈርጃሉ፡፡ ከሕዝቡ እምነት ብቻ ሳይሆን ከባህሉ ጋርም የሚጣረስ ጉዳይ ነው፡፡

እንዲህ ያለውን ነገር በማኅበረሰቡ ውስጥ እንዲስፋፋ የሚሠሩ፣ ሕዝቡም ያልበላውን የሚያክኩ ተቋማት እና ግለሰቦች አጋጣሚዎቹን እንዳይጠቀሙ የሚመለከተን ሁሉ በርግጠኛነት መከላከል ይጠበቅብናል፡፡

ግብረሰዶማዊነትን ካልተቀበላችሁ፣ የግብረሰዶማውያንን መብት ካልደገፋችሁ አንረዳም እያሉ የሚያስፈራሩ ምዕራባውያን ኃያላን አሉ፡፡ ራሳችንን አጥተን የሚመጣ ርዳታ ለቀብር ማስፈጸሚያነት ብቻ የሚውል ነው፡፡ እናም እንዲቀርብን እንንገራቸው፡፡

የጉባኤው አዘጋጆችም ቢሆኑ ወደ ጉባኤው ለሚመጡ እንግዶች የኢትዮጵያን ሕግ እና የሞራል እሴቶች አስቀድመው የመግለጽ እና የማስጠንቀቅ ግዴታ አለባቸው፡፡

የሀገራችን ሰው እሳቱ ከሌለ ጢሱ አይታይም ይላል፡፡ አሁንም ቢሆን ምናልባት በጎላ መልኩ አልወጣ ይሆናል እንጂ ያለ ምክንያት የግብረ ሰዶማዊነት ጉዳይ በዚህ ወቅት አልተነሣም፡፡ ጢሱ እንዳይታይ ከመጣር ይልቅ እሳቱ እንዲጠፋ ብንሠራ የተሻለ ውጤት እናመጣለን፡፡

የኢትዮጵያ ሕግ ምን ይላል?

በኢትዮጵያ የወንጀል ሕግ (1996) ክፍል ሁለት ‹‹ለተፈጥሮ ባሕርይ ተቃራኒ የሆነ የግብረ ሥጋ ግንኙነቶች›› በሚል ርእስ በአንቀጽ 629፣ ግብረሰዶም እና ለንጽሕና ክብር ተቃራኒ የሆኑ ሌሎች ድርጊቶች በሚል ርእስ፣ ‹‹ማንም ሰው ከእርሱ ጋር አንድ ዓይነት ጾታ ካለው ከሌላ ሰው ጋር ግብረሰዶም ወይም ለንጽሕና ክብር ወይም ለመልካም ጠባይ ተቃራኒ የሆነውን ሌላ ድርጊት የፈጸመ ማንኛውም ሰው ከቀላል እስራት እስከ ከባድ ወንጀል ቅጣት እንደሚጠብቀው ይደነግጋል፡፡

በአንቀጽ 631 ደግሞ ‹‹ለአካለ መጠን ባልደረሱ ልጆች ላይ የሚፈጸሙ የግብረሰዶም ጥቃትና ለክብረ ንጽሕና ተቃራኒ የሆነ ሌላ ድርጊት›› በሚል ርእስ፣ ንኡስ አንቀጽ 1. ማንም ሰው ከእርሱ ጋር አንድ ዓይነት ጾታ ባለውና ለአካለ መጠን ባልደረሰ ልጅ ላይ የግብረሰዶም ጥቃት የፈጸመ እንደሆነ፤ የተበዳዩ ዕድሜ አሥራ ሦስት ዓመት ሆኖ አሥራ ስምንት ዓመት ያልሞላው ሲሆን፣ ከሦስት ዓመት እስከ አሥራ አምስት ዓመት በሚደርስ ጽኑ እሥራት ይቀጣል፡፡ የተበዳዩ ዕድሜ ከአሥራ ሦስት ዓመት በታች ሲሆን፣ ከአሥራ አምስት ዓመት እስከ ሃያ አምስት ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት ይቀጣል፡፡ በተጨማሪም አንዲት ሴት ለአካለ መጠን ባልደረሰች ልጅ ላይ የግብረሰዶም ጥቃት የፈጸመች እንደሆነ፣ ከአሥር ዓመት በማይበልጥ ጽኑ እስራት ትቀጣለች በማለት ደንግጓል፡፡ በተሻሻለው የቤተሰብ ሕግም አንቀጽ 13 መሠረት ይህ የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻ በሕግ የተከለከለ መሆኑም ተደንግጓል፡፡

3 comments:

  1. Where is aba paulos minew zim Alu lelaw yehaymanot meri sinager ersachew benegeru tesmamtew yihon?

    ReplyDelete
  2. እግዚአብሄር ሃገራችንን ይጠብቅልን!!!!

    ReplyDelete
  3. Nigusie Dz

    igizio marene keresetos

    ReplyDelete