Saturday, September 17, 2011

“አንተም ተው አንተም ተው” - አርዮስንና ቅዱስ ቄርሎስን?!


  • አርዮስ ተፀፅቻለሁ እያለ ይቅር ሲባል ወደ ቀደመ ምንፍቅናው እንደሚገባ ሁሉ ተሃድሶወችም በእምባ ሆነው ይቅርታ ይጠይቁና መልሰው ቅዱሱንና ማደሪያውን ያሳዝናሉ ፤
  •  የአርዮስ ትምህርት የረከሰና የተጠላ የማይጠቅምም እንደሆነ ሁሉ የተሃድሶወችም ትምህርት መልካምን ፍሬ የማያፈራ የማይጠቅም ዘር ነው፡፡
  •  የአርዮስ እውቀት ከዲያቢሎስ እንደሆነ ጥበቡም ለክርስቲያኖች የማይሆን እንደሆነ ሁሉ የተሃድሶወችም ጥበብ ለመንግስተ ሰማያት የማያበቃ ባዶ ጥበብ ከንቱ ጩኅት ነው፡፡ 
  • ስለዚህ ቅዱስ ቄርሎስና አርዮስ ህብረት የላቸውምና ይቅር ተባብላችሁ በአንድነት ስሩ አትበሉ ፡አይባልምና!! ወይንስ ቅዱስ ቄርሎስን አንተም ተው ስትሉ ቤተክርስቲያንህን ከመጠበቅ ቸል በል ማለታችሁ እንደሆነ ታስተውላላችሁ? የከበረ ማእድን የተከማቸበትን ቤት ለሌባ አሳልፋችሁ እየሰጣችሁ እንደሆነ አታውቁምን? 


በስመ አብ ወወልድወመንፈስ ቅዱስ አሃዱ አምላክ አሜን፡፡

ፍቅርን አውቃለሁ በተግባርም እገልፃለሁ የሚል - - - ነገር ግን ፍቅሩ የይምሰል የዲያቢሎስ ያልሆነበት የመንፈስ ቅዱስን ፍቅር የተገነዘበ በማስተዋልም የከበረ በተዋህዶ እምነቱ የሚኮራ በእውነት ፊት ፡ በፍቅር ሽንጎ ፡ በማስተዋልም ጥበብ ዳኛ ይሁንና ይህንን ይዳኝ ፦ በሽንጎው ላይ ቅዱስ ቄርሎስና አርዮስ ቆመዋል፡፡ ስለጥንተ ነገራቸው፦

1) አርዮስ የክርስቶስን አምላክነት የሚጠራጠር በተዋህዶ የምታምን ቤተክርስቲያንንም በአዲስ ትምህርት ለመለወጥ የሚተጋ ሲሆን ከአንድም ብዙ ጊዜ ትምህርቱ ስህተት እንደሆነ ሊቃውንቱ በመፅሃፍ ቅዱስ አስረጅነት በመንፈስ ቅዱስ ምስክርነት ቢያስረዱትና ቢመክሩት እምቢ ያለ ፡ ክርስቶስን ከአብ አንድነት የለየ ሲሆን ፡ ቤተክርስቲያን በዚህ እምነቱ ከአንዴም ሁለት ሶስት ጊዜ ብትለየውም አርዮስ ግን በገንዘብ የሚታለሉትን ካህናት ፡ ባለማስተዋል የሚሄዱትን ምእመናንና አለማዊ ነገስታትን በትምህርቱና በወቅቱ በነበረው የግጥም ፡ የዜማና የስነፅሁፍ እውቀት ደጋፊ አድርጎ ከአንድም ሁለት ሶስት ጊዜ ተፅፅቻለሁ እያለ ወደ መቅደስ ይገባ የነበረ ነው፡፡ ይቅርታንም ካገኝ በኅላ ምንፍቅናውንና በልቡ ያደረ ሰይጣንን ከራሱ ሊያስወግድ አልፈቀደምና መልሶ መላልሶ ወደቀደመ ክህደቱ የሚመላለስ ነው፡፡ ትምህርቱ ይህ ሲሆን ህይወቱ ደግሞ በቀደመው እድሜው የቤተክርስቲያን ዲያቆን በነበረበት የወጣትነት ጊዜ በዘመኑ የነበሩ የአህዛብ ነገስታት ቤተክርስቲያናት ወደ ጣኦትነት እንዲቀየሩ የቤተክርስቲያን ካህናትም የጣኦት ካህናት እንዲሆኑ ሲታዘዝ እውነተኞቹ ካህናት ገሚሱ ሰማእት ሲሆን ገሚሱ ሲሰደድ አንዳንዶች ግን የክርስቶስን ቤተመቅደስ እጣን ባጠኑበት እጃቸው ቅዱስ ወንጌሉን ባስተማሩበት አፋቸው ሰማእትነት ርቋቸው ፡ መፅናት አቅቷቸው ፡ የመንፈስ ፍሬ ታጥቶባቸው ነበርና የጣኦት አገልጋይ ለመሆን አላፈሩም፡፡ ከነዚህ ውስጥ አንዱ አርዮስ ነበር፡፡

2) ቅዱስ ቄርሎስ ክብር ይግባውና በኢየሱስ ክርስቶስ ፍፁም አምላክነት የሚያምን ፤ ቃልም በፍፁምና በማይመረመር ጥበብ ከስጋ ጋር እንደተዋሃደ አምኖ የሚያስተምር የኦርቶዶክስ ጠበቃ የአለም ሁሉ መምህር የሆነ ነው፡፡ ቅዱስ ቄርሎስ በተዋህዶ እምነቱ ፍፁም የፀና ፣ ማንም አዲስን ትምህርት ሊያመጣ እንደማይገባ የሚታገል ሲሆን ከሃዋርያት ስትያያዝ የመጣች እምነት ንፅህት ናት ርትእት ናት ሙሉእ ናት ስለዚህም ማንም ሊለውጣት አይነሳ የሚል ነው፡፡ በወቅቱ የሃይማኖት መሰረትን ካወጡት ከ318ቱ ሊቃውንት አንዱ የነበረ በእውነት በትምህርቱና በህይወቱ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን እስከ እለም ፍፃሜ የምትኮራበት ቅዱስ ነው፡፡የአርዮስንም የምንፍቅና መርዝ እንዲህ ብሎ በመንፈስ ቅዱስ መድሃኒትነት አረከሰ “ የማያምኑ መናፍቃንስ ከእውነት የተለየ የሃሰት ነገርን ይናገራሉ ፤ ንፁሃን አባቶቻችን ግን የክርስቶስን ነገር አንድ አካል አንድ ባህርይ ነው በማለት ፈፀሙ ፤ በአብ በወልድ እናምናለን እንዳሉ በመንፈስ ቅዱስም እናምናለን አሉ ፡ በአንድ መለኮት ከአብ ከወልድ ጋር ትክክል ነውና፡፡ - - - የንፁሃን አባቶቻችን የቀናች ሃይማኖት ይህቺ ናት ፤ ያማረ የተወደደ ሃይማኖታችን ይህ ነው፡፡ ”ሃይማኖተ አበው ዘ ቄርሎስ

ምንም እንኳን በመንፈስ ቅዱስ ፍርድ አርዮስ ከቅዱስ ቄርሎስ ፊት መቆም የማይገባው እንደሆነ ቢታወቅም ፤ ምንም እንኳን ቅዱስ ቄርሎስ በፆም በፀሎትና በመልካም እረኝነት ስጋው ደክሞ ሲታይ አርዮስ ደግሞ እንደስጋ ፈቃድ በመብል እና በመጠጥ የሚኖር ነውና በአለማዊ ሰወች እይታ ውስጥ ጎላ ብሎ ቢታይም - - - አሁን ግን እኩል ቆመዋል፡፡ አቤቱታ አቅራቢው አርዮስ ነው፡፡

አርዮስ በሚያባብል ድምፅ እንዲህ አለ ፦ ”አባቶቼ እናቶቼ ወንድሞቼና እህቶቼ እኔ በቤተክርስቲያን ከልጅነቴ ጀምሮ እንደኖርኩ ታውቃላችሁ ፡ ቤተክርስቲያንም አስተምራኛለች ፡ እኔም እንዲሁ በሰው ትምህርት ብቻ ሳይሆን በፅጋ እያገለገልኩ እንደሆነ ታውቃላችሁ፡፡ ብዙ ሰወችንም በፀጋየ ወደ እግዚአብሄር አቅርቤያለሁ ፡ አሁንም አላማየ ይሄ ነው ፤ ነገር ግን የማምነው የአባቶችን ተረት ሳይሆን መፅሃፍ ቅዱስን ነው፡፡ አሁንም ከነቅዱስ ቄርሎስ ጋር ሆኜ መስራት እፈልጋለሁ ፤ በመቅደሱ ቅዳሴ መቀደስ እፈልጋለሁ ፤ ስጋወ ደሙን ተቀብየ ማቀበል እሻለሁ፡፡ እኔም ሆንኩ ሌሎቻችን አላማችን አንድ ነው፡፡ ሰውን ሁሉ ወደ ቤተ እግዚአብሄር ማቅረብ፡፡ ስለዚህ መነካከሱን እንተወውና ሁላችንም እንደፀጋችን እናገልግል፡፡ ገና ለገና በነገረ መለኮት ተለየሁና ከቤተክርስቲያን መለየቴ ልክ አይደለም፡፡ በማንኛውም የሃይማኖት ድርጅት ውስጥ የሃይማኖት ልዩነት ይኖራል፡፡ የኔ ምን አዲስ ነገር ሆኖ ነው፡፡ ይልቅ መበላላቱን እንተወው ፡ መነካከሱን እንተወው ይህ የመንፈስ ፍሬ አይደለምና፡፡ እናንተም ይህን አይታችሁ አስማሙኝ፡፡” ይህን ብሎ ዘወር አለ ፤ አሁን ደግሞ ቅዱስ ቄርሎስ ይናገር ዘንድ ፈቀዱለት፡፡

ቅዱስ ቄርሎስም እንዲህ አለ ፦ “ በአብ ስም አምኜ አብን ወላዲ ብየ ፡ በወልድ ስም አምኜ ወልድን ተወላዲ ብየ ፡በመንፈስ ቅዱስም ስም አምኜ መንፈስ ቅዱስን ሰራፂ ብየ በአንድ አምላክ በማመን ነገሬን እጀምራለሁ፡፡ የአርዮስን ሃሳብ ሰምታችኅል እኔም እስከዛሬ ከተናገረውና ካስተማረው እየጠቀስኩ አላደክማችሁም ፤ ይልቁንም አሁን በተናገረው እሞግተዋለሁ እንጂ፡፡ አርዮስ በቤተክርስቲያን እንደኖረ ቢናገር እኔ ደግሞ የቀደመው መልአክ ሳጥናኤል የአሁኑ የወደቀው ዲያቢሎስ በቀደመው ጊዜ ኑሮው በሰማያት የመላእክት አለቃ እንዲሆን በእግዚአብሄር የተሾመ ቢሆንም የተሰጠውን እጅግ የበዛ ስጦታ ትቶ ያልተሰጠውንና የማይገባውን አንድ ነገር ስለሻተና ስለቀጠፈ ወደ ጥልቁ እንደወረደ ከስልጣኑም እንደተሻረ እናገራለሁ፡፡ ስለዚህም ምክንያት ዲያቢሎስ በቀደመ ስልጣኑ ሳይሆን በአሁኑ ግብሩ የሚፈረድበት እንደሆነ ልብ እንበል፡፡ ስለዚህም አርዮስን በቀደመ ግብሩ የቱንም ያክል ፃድቅ ቢሆን ወይንም የቱንም ያክል የረከሰ ቢሆን ልንፈርድበት አልቆምንም ፡ ነገር ግን በአሁን ግብሩ የምንሞግተውና የምንፈርድበት እንደሆነ ይወቅ፡፡ አርዮስ በትምህርቴ ብዙ ሰወችን ወደ እግዚአብሄር አቅርቤአለሁ ብሏል ነገር ግን የእግዚአብሄርን አንድነትና ሶስትነት ለያይቷል ፤ የወልድን ክብር ከአብ አሳንሷል ፤ የመንፈስ ቅዱስንም ክብር ከወልድ አሳንሷል ፤ ስለዚህም የማይከፈል መለኮትን ከፍሏልና እግዚአብሄርን አላወቀም፡፡ የአስተማራቸውም ሰዎች ከእግዚአብሄር ከመቅረብ ይልቅ ርቀዋል ፡ እርሱ ስለሌለ አምላክ ያወራልና፡፡ እኛስ የምናመልከው አምላክ አንድ ነው በመለኮቱም መከፈል የለበትም፡፡ አብም ከወልድ አይበልጥም ፡ ወልድም ከመንፈስ ቅዱስ አይበልጥም በስልጣን በልእልና በክብር አንድ ናቸው እንጂ፡፡አርዮስ መቅደስ እቀድስ ዘንድ ስጋወ ደሙን አቀብል እቀበል ዘንድ ፍቀዱልኝ ይላል ፤ ነገር ግን አርዮስን እጠይቀው ዘንድ እወዳለሁ፡፡ አርዮስ ሆይ ፦ ቤተክርስቲያን በቤተመቅደስ የምታገለግለው ፍጡርን ነው ወይንስ ፈጣሪን? ፈጣሪን ነው ካልክስ ታዲያ አንተ ክርስቶስን ፍጡር አድርገኅው የለምን? ታዲያ እኛ ቤተክርስቲያን ምን ትሰራለህ? አንተ ፍጡር ነው የምትለውን ጌታ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ግን የጌቶች ጌታ የነገስታት ንጉስ የአማልክት አምላክ ብላ በፈጣሪነቱ አምና ስሙን እየጠራች ለቅዳሴ ትቆማለች ፡ የክርስቶስ ስጋውም ደሙም መለኮት የተዋሃደው እንደሆነ አምና በክርስቶስ አምላክነት ለሚያምኑት ብቻ የዘላለም ህይወትን ያገኙ ዘንድ ታቀብላለች፡፡ ታዲያ አንተ ክርስቶስ ፍጡር ነው ፡ ሰው እንጂ አምላክ አይደለም ካልክ የሰው ስጋ ልትበላ ትወዳለህን? ወይንስ ክብር የሚገባውን የክርስቶስን ስጋና ደም ለመዳን ሳይሆን ለመታሰቢያ ያክል ብቻ ነው የምትል ስትሆን ቤተክርስቲያን ካንተ ምን ህብረት አላትና ልትመጣ ትወዳለህ? ወይንስ ክርስቶስ ፈጣሪየ ነው ብሎ የሚመጣውን ምእመን ፈጣሪ አይደለም እያልክ በመስቀል ልታሳልመው ነውን? አለዚያስ ስጋወ ደሙ አማናዊ ነው ብሎ አምኖ የሚመጣውን ምእመን ይህ መለኮት የተለየው የፍጡር ስጋና ደም ነው ለመዳኛም ሳይሆን ለመታሰቢያ ነው ልትል ነውን? ስለዚህ ከቤተክርስቲያን ወገን አይደለህምና ከእኛም ወገን አይደለህም ፤ እኛም ካንተ ጋር አብረን ልንሰራ አንችልም ፤ በጓደኘትም ልንኖር አንችልም ፤ ከአንተም ጋር የሚኖሩት በትምህርትህ የተስማሙና የተባበሩ ብቻ ናቸው፡፡ አርዮስ ሆይ ፦ መነካከስ ፡ መለያየት ፡ መበላላት ምን ይሰራል ያልከውን ግን እባብ የተባለ ዲያቢሎስን ባገኝን ጊዜ ራስ ራሱን እንቀጠቅጠው ዘንድ እሱም የያዘን ጊዜ ሰኮናችንን እንደሚነክሰን የታወቀ እንደሆነ እነግርሃለሁ፡፡ ክርስቶስም በመስቀሉ የዲያቢሎስን ራስ እንደቀጠቀጠው እመሰክራለሁ፡፡ እኛም የክርስቶስና የቅዱሳን ነንና ከዲያቢሎስና ከተላላኪወቹ ምንም ህብረት የለንም፡፡ ጠላትነታችንም እስከ ዘላለም የሚቀይ ነው፡፡ ዲያቢሎስ በሰወች ላይ አድሮ ቤተክርስቲያንን ሊያጠፋ እስከዘላለም ድረስ ዝናሩን ያርከፈክፋል ፤ እኛም በከርስቶስ ደም የተመሰረተችውን ቤተክርስቲያችንን እስከሞት ድረስ ፀንተን ሰማእታትን አብነት አድርገን እንጠብቃታለን፡፡ ስለዚህም መለያየት በወንድሞች መካከል ከሆነ መልካም አይደለም ፡ ነገር ግን በጎ ከክፉ ጋር ህብረት እንደሌለው እወቅ ፤ ክርስቶስ ከዲያቢሎስ ጋር ክርስቲያንም ከመናፍቅ ጋር አንድነት እንደሌለው ተገንዘብ፡፡ አንድ ነገር የተናገርካት ነገር ግን ተዋህዶን አይመለከትም - - -በሃይማኖት ደርጅቶች ውስጥ ሁልጊዜ ልዩነት ይኖራል ብለሃልና፡፡ ተዋህዶ ውስጥ ግን የሃይማኖት ልዩነት የለንም የሃይማኖት መሰረታችንም አንዲት ናት አምላካችንም አንድ ነው - - - ህጓም ትእዛዟም የታወቀች ናት - - - እምነቷም ፍፅምት ነች ስለዚህ በተዋህዶ ውስጥ ሆኖ የሃይማኖት ልዩነት አለ የሚል ይኖር ዘንድ አይገባም፡፡ እምነቷን የሚያምን ፀንቶ በቅጥሯ ይኖራል - - - በእምነቷ የማይታመን ግን ከቅጥሯ ይወጣ ዘንድ የተገባ እንደሆነ እወቅ፡፡ ልብ ያለው ልብ ይበል፡፡ ስለሁሉ እግዚአብሄር ይመስገን፡፡ አሜን፡፡” ብሎ ነገሩን ቋጨ፡፡

ሁለቱም በዚህ መልክ ነገራቸውን አስረዱ ፤ እንግዲህ ዳኛው ሆይ እስኪ ፍረድ - - - የአርዮስ ሃሳብ ገዝፎብህ አርዮስን አንተም ተው ቅዱስ ቄርሎስንም አንተም ተው ፡ ተስማሙ ፡ በህብረትም ቁሙ ፡ በአንድነት ብትቆሙ ጠላትን ታሽንፋላችሁ ፤ ቤተክርስቲያናችሁ ትሰፋለች ቄርሎስም ክርስቶስ የሞተው ወንድማማቾች ሊያደርገን ሊያዋድደን እንደሆነ ዘንግተህ አርዮስን ጓደኛየ አይደለህም ማለት የለብህም ትላለህን? ወይንስ የቅዱስ ቄርሎስ የረቀቀ ማስተዋልና አርቆ አሳቢነት ገብቶህ ስለቤተክርስቲያንም ቀንተህ ፡ ያለስርአት እየሄዱ ስርአት ለምእመናን እናስተምራለን የሚሉት ፤ ያለእምነት ሄደው እምነትን ለምእመናን እናስተምራለን የሚሉት ፤ እሾህ ሆነው ወይን እናፈራለን የሚሉት ቅጥፈት እንደሆነ ተገንዝበህ ለቅዱስ ቄርሎስ ትፈርዳለህን? ወይንስ ምን ትል ዘንድ ትወዳለህ?

ከፋ ትምህርትን ያመጣ አርዮስን “አንተ የክርስቶስ ጠላት መሆንህን እወቅ ፡ የክርስቶስንም የክብር ልብሱን እንደቀደድክ ተረዳ ፤ በቤተክርስቲያንም እድል ፈንታ የለህም ፡ ይልቅ ክርስቶስ ይቅር ይልህ ዘንድ ራስህን አዋርድ ፡ በትምህርትህ ያጠፋሃቸውን ሰወች ከእግራቸው ወድቀህ ይቅርታ ጠይቅ ፡ ንስሃም ግባ ፡ከሰውም ተለይተህ በገዳም ኑር ፡ ቅዱስ ቄርሎስም የሃይማኖትን ትምህርት ያስተምርህ ዘንድ ድንጋይ ተሽክመህ ለምነው ፡ አስለምነው ፤ ነገር ግን ማእረግህና ስልጣንህ የተሻረ እንደሆነ እወቅ ፤ በቤተክርስቲያንም ታስተምርና ትቀድስ ዘንድ አይገባህም፡፡ መጀመሪያ ራስህን አድን ተማርና እመን ለማስተማሩ እነቅዱስ ቄርሎስ አሉ፡፡ አንተ ግን ሂድ፡፡ደግሞ አንተ በወሬ ብቻ አስር ጊዜ የምትደጋግመውን ፍቅር ቅዱስ ቄርሎስ ክርስቶስን ለብሶ ፍቅርን ገንዘቡ ማድረጉን ዘንግተህ ስለፍቅር ቄርሎስን ታስተምረው ዘንድ እንዴት ደፈርክ? ” ትላለህን? ወይንስ ፍቅርን ገንዘብ ያደረክ መስሎህ “አርዮስም ተው ቄርሎስም ተው - - - በተለይ ቄርሎስ መነካከሱን አቁም” ልትል ትደፍራለህ? ይሄው ፍርዱን ትፈርድ ዘንድ ጀምር፡፡

እኔም እንግዲህ የዘመኑን ተሃድሶወችን በአርዮስ መስየ ፡ እውነተኛ የተዋህዶ ዶግማና ቀኖናዋን ለመጠበቅና ለማስጠበቅ የሚፋጠኑትን ደግሞ በቅዱስ ቄርሎስ መስየ አስቀምጫቸዋለሁ፡፡ምናልባት የአርዮስን ያክል ፍፁም ክህደትን የካደ ተሃድሶ ላይኖር እንደሚችል ሁላ የቅዱስ ቄርሎስን ያክል ቅድስናና ጥበብ ያለው የተዋህዶ አማኝ ላይኖር እንደሚችል እሙን ነው፡፡ ነገር ግን አንዳንዶች በማወቅም ባለማወቅም በአንድነት ሊኖሩ የማይገባቸውን አንተም ተው አንተም ተው እያሉ ለተሃድሶወች ሳያውቁት ክፍተት እየፈጠሩ ላሉት ማንቂያ ይሆን ዘንድ ፃፍኩት፡፡እናስተውል ፦ አርዮስ ተፀፅቻለሁ እያለ ይቅር ሲባል ወደ ቀደመ ምንፍቅናው እንደሚገባ ሁሉ ተሃድሶወችም በእምባ ሆነው ይቅርታ ይጠይቁና መልሰው ቅዱሱንና ማደሪያውን ያሳዝናሉ ፤ የአርዮስ ትምህርት የረከሰና የተጠላ የማይጠቅምም እንደሆነ ሁሉ የተሃድሶወችም ትምህርት መልካምን ፍሬ የማያፈራ የማይጠቅም ዘር ነው፡፡ የአርዮስ እውቀት ከዲያቢሎስ እንደሆነ ጥበቡም ለክርስቲያኖች የማይሆን እንደሆነ ሁሉ የተሃድሶወችም ጥበብ ለመንግስተ ሰማያት የማያበቃ ባዶ ጥበብ ከንቱ ጩኅት ነው፡፡ ስለዚህ ቅዱስ ቄርሎስና አርዮስ ህብረት የላቸውምና ይቅር ተባብላችሁ በአንድነት ስሩ አትበሉ ፡አይባልምና!! ወይንስ ቅዱስ ቄርሎስን አንተም ተው ስትሉ ቤተክርስቲያንህን ከመጠበቅ ቸል በል ማለታችሁ እንደሆነ ታስተውላላችሁ? የከበረ ማእድን የተከማቸበትን ቤት ለሌባ አሳልፋችሁ እየሰጣችሁ እንደሆነ አታውቁምን? የቤተክርስቲያንን መንፈሳዊ ሃብቷን ለዘራፊ እያዘረፋችሁ እንደሆነ እንዴት አትገነዘቡም፡፡ይልቅስ በአርዮስ ጥበብ የሚመላለሱትን ተሃድሶወች እሹሩሩ ማለት ትተን አስቀድመው የሃይማኖትን ትምህርት ይማሩ ዘንድ ይለዩ ፡ ቅዳሴን ካልቀደስኩ ፡ ንኡስ ክርስቲያናትን ካላጠመኩ ፡ በሰገነቱ ወጥቼ ምእመናንን ካላስተማርኩ ሲሉም ሳይማሩ ማስተማር አይገባም ፡ ሳያምኑ ማሳመን አይሆንም ፡ ያለስርአት ስርአት ማስያዝ አይቻልም በማለት በቅዱስ ቄርሎስ ጥበብ ሃይማኖታችንን እንጠብቅ ዘንድ መትጋት ይጠበቅብናል፡፡

በመጨረሻም ቅዱስ ቄርሎስና አርዮስ ይህን እየተነጋገሩ ተሟገቱ ብየ የፃፍኩት ከእምነታቸው ተነስቼ ነጥቤን ያብራራልኛል ያልኩትን እንጂ እነሱ የተናገሩትን አግኝቼ በቀጥታ የጠቀስኩ እንዳልሆነ ይታወቅልኝ፡፡ በተለይ ቅዱስ ቄርሎስ እንዲህ አለ እያልኩ ስናገር በክርስቶስ ጥበብን ገንዘብ ያደረገ ጠቢብ ቄርሎስን አላዋቂ እኔ አሳዝኜው እንደሆነ የተወደደ የአለም መምህር የኦርቶዶክስ ጠበቃ ቅዱስ ቄርሎስ ይቅር ይለኝ ዘንድ ለምኑልኝ፡፡ እግዚአብሄር አምላክ ማስተዋሉን ይስጠን፡፡አሜን፡፡

የአብ ፀጋ ፡ የወልድ ፍቅር ፡ የመንፈስ ቅዱስ አንድነት ከሁላችን ጋር ይሁን፡፡አሜን፡፡

ታምራት ፍስሃ

መስከረም 5/2004

2 comments:

  1. Very Very Very informative and expressive. KHY God bless you.

    ReplyDelete
  2. ውድ ዘመድኩን በእውነት እንዲህ ብለሃል ካልክ በእውነት ሃይማኖት የለህም፡፡ ‹‹እርሱ የመሰረትብኝ ክስ ወህኒ ብቻ ሳይሆን ሲኦል የሚያወርደኝ ቢሆን እንኳን ሲኦል እገባለሁ እንጂ በሃይማኖቴ አልደራደርም የምፈጽመው ዕርቅ የለኝም፤ህጉ ነፃ ያወጣኛል፡፡›› የያዝከው መንገድ ሲኦል የሚያገባ ከሆነ ንስሃ መግባት መንፈሳዊ እና ኦርቶዶክሳዊ እሴት ነው፡፡ ለንግድህና አጠገብህ ለተኮለኮሉ ጥቅመኞች ጥቅማቸው ከሚነካ ሲኦል መግባት ምርጫቸው እንደሆነ ያሳያል፡፡ ምእመናን እነዚህ እንደዚህ ናቸውና ከእነዚህ ራቁ!!!!! ይህን መልእክት ልኬለት ሲመልስ ያው ነበር አሁንም ሲኦል ነው ያልከው በጋሻው አንድ ግለሰብ ነው ይቅርታ መጠየቅ ሃይማኖት ነው አንተ በጋሻው ቀኖና ጣሰ እያልክ ነው ስትናገር የነበረው አንድ ሰውን የሃይማኖት ችግር ቢኖርበት እንዴት እንደሚሆን አባቶቻችን ያስቀመጡት ቀኖናን መጣስ በምን መስፈርት ነው ተሃድሶ የማያስብለው የእናንተን ተቀብለን ብንሄድ ይህስ ቀኖና መጣሱ ምን ሊባል ነው፡፡ ለነገሩ አንተም ምን ተምረሃል ቢባል መልሱ በተናገርከው ይመዘናል፡፡ ዳንኤል ክብረት ተመራማሪ የተባለው የት ተምሮ ነው ቲኦሎጊ ነው መይስ የአብነት ት/ቤት ይህስ ከመጋቤሐዲስ በምን ይለያል የግል ጠብ የለንም ትላለህ ይህ ነው ብትል ላንተ ጆሮውን የሰጠን ሁሉ ታጣለህ በዚህ የምታተርፈው ይቀራል ስለዚህ በቻልከው መጠን መንፈራገጥህ ነው እውነት ነው አንድ ቀን ንስሃ ስላልገባህ እግዚአብሔር ይመጣብሃል ውጤቱም እንደምኞትህ ይሆንልሃል ግን እነበጋሻው ችግር የለባቸውም እያልኩህ አይደለም አንተም ተመሳሳይ ችግር አለብህ እያልኩህ ነው ዛሬ ካልገባህ ልቡናህ የእውቀት ብርሃን ሲነካው ያኔ ይገለጥልሃል
    ውድ ዘመድኩን ሁለታችሁ (አንተና በጋሻው) የተጋፋችሁት በግል ጉዳይ አይደለም ብለሃል እኔ የሁለታችሁ መጋፋት ሳይሆን ችግሬ በኦርቶዶክሳዊ ትምህርት ቀኖና መሰረት አንተ ያልከው ስህተት መሆኑን ላንተና መሰሎችህ መንገር ነው፡፡ ሲኦል የሚያስገባ ስህተት ካለብህ ንስሐ መግባት ነው፡፡ አይ እኔ እንደ ሮሙ ፓፓ አልሳሳትም ከሆነ መልካም ከመሰሎችህ ጋር መጓዝ ነው ቤተክርስቲያንን ተጠግቶ ግን የሚያዋጣ አይመስለኝም፡፡ የአንተን አለመሳሳት ማን አረጋገጠልህ!! እኔ ቤተክርስቲያን አለች የምለው ህጋዊው አካል በህጋዊ እና አባቶቻችን ባስቀመጡት ቀኖናዊ መንገድ ሲመጣ ብቻ ነው፡፡ ግርግር መፍጠር ግን ዓላማው ሌላ ነው፡፡ ጲላጦስ ይፍረድልን ብለው ጌታችንን ባመጡት ሰዓት ፈራጃቸው ንጹህነቱን ሲመሰክር ምርጫቸው ህዝቡን በማደናገር ሁከት ማስነሳት ሆነ፡፡ ይህ ለማንም ካለመጥቀሙም ሌላ ሌላው የክህደት መገለጫ ነው፡፡ ቤተክርስቲያንንና ቀኖናዋን ማክበር፤አለበለዚያ ከሃይማኖታችን ሁለታችሁም ገለል በሉልን፡፡ ቤተክርስቲያን ቀኖና አላት አንተ እንደልብህ የምትዘውረው አይደለም ሊሆንም አይችልም፡፡ ቀኖናው ይጠበቅ ብለው ቅ/ፓትርያርኩ መመሪያ ሲያስተላልፉ አንተና መሰሎችህ ታጣጥላላችሁ፡፡ ፓትርያርኩን አለአግባብ መዘርጠጥም ቀኖናዊ ስህተት ነው፡፡ ስልጣኑ ካለህም ክህነትን ሁሉ ያሽራል፡፡ ሚዛኑ ለሁሉም ይሰራል፡፡ ያኔ አንተ ለባህታዊ ገ/መስቀል በገብርኤል ብስራት መወለዳቸውን በመጥቀስ ገድል አስጻፊ አልነበርክ እንዴ? ህገወጥ ሰባክያንን በህጋዊ ማእቀፍ እንዲንቀሳቀሱ ማስቻል አስፈላጊ ነው፡፡ አንድ ቀን ጌታ አንተንና ሰባክያን ተብዬዎችን በአባቶቻችን አድሮ ከነሸቀጣችሁ…….

    ReplyDelete