Wednesday, March 19, 2014

የፓትርያርኩ የለውጥ ተስፋዎች ወዴት ገቡ?




የአንድ ምዕመን አስተያየት

በመጀመሪያ የአክብሮት ሰላምታዬን ለቅዱስ ፓትርያርኩ በማቅረብ የተሰማኝን  ለመግለጽ እወዳለሁ፡፡ ቅዱስነትዎ በመጀመሪያ የቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ አባት ሆነው ወደ መንበሩ በመምጣትዎና አንድ ዓመትዎን በማክበረዎ እንኳን ደስ አለዎ በማለት መልዕክቴን አስተላልፋለሁ፡፡ 

ወደ ኃላፊነት ሲመጡ ብዙ የለውጥ ተስፋዎችን በተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን አስተላልፈዋል፡፡ አይዟችሁ፣ ለውጥ ይመጣል፣ ሲሉ ተናግረውም ነበር፡፡ እኔም በቤተ ክርስቲያናችን የተስፋፋውን ጎጠኝነትና ሙሰኝነት በአጠቃላይ ያለው ብልሹ አሠራር ይለወጣል ብዬ እጅግ ተስፋ አድርጌ ነበር፡፡ እርሶዎም በቤተ ክርስቲያናችን አስተዳደራዊ መዋቅር ላይ ከፍተኛ ለውጥ ያመጣሉ ብዬ ተስፋ አድርጌ ነበር፡፡ ነገር ግን ከተወሰኑ ወራት በኋላ ድምፅዎትን መስማት፣ እርስዎንም ማየት ባለመቻሌ ፍርሃት አደረብኝ፡፡ 

በእርግጥ ቀደም ሲል የነበረው የዘረኝነትና የሙሰኝነት ሰንሰለት በአንድ ጊዜ በጥሶ አዲስ ለውጥ ለማምጣት ከባድ ሊሆንብዎ እንደሚችል እገምታለሁ፡፡ አቡነ ጳውሎስን ሲያሳስቱና ከምዕመናን ጋር ሲያጋጩ የነበሩ ጎሰኛና ሙሰኛ ግለሰቦች አሁን ምናልባት ከዚያ ቦታ ሳይነሱ እርስዎንም ወደዚያ የጥፋት ሳጥን ውስጥ አስገብትዎት መውጫ አሳጥትዎት ከሆነ እባክዎ ወደ ልቡናዎ ተመልሰው፣ ቃል የገቡባቸውን የለውጥ ተስፋዎች ለመተግበር ይነቃቁ፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ሲነሱ መሰናክሉ ብዙ እንደሆነ ይሰማኛል፡፡ እርስዎም አሁን በአገራችን የተፈጠረው የዘር በሽታ ሳያደናቅፍዎና ለአሉባልታ ወሬ ጆሮ ሳይሰጡ፣ ለመስዋዕትነት እንደመጡ ተናግረዋል፡፡ የመንግሥት ፖለቲካዊ ጫናም ሳያስፈራዎ፣ መንፈሳዊ የለውጥ አባትነትዎን በተግባር ያሳዩን፡፡ የለውጥ ሥራዎ አብቦና ፍሬ አፍርቶ ለማየትና ለመጠቀም ከፍተኛ ጉጉት አለን፡፡ 

በፈጣሪም፣ በሰውም በታሪክም እንዳይወቀሱ ቃል ከገቡበት የለውጥ ጐዳና ወደ ኋላ እንዳይሉ አስተያየት ለማቅረብ እወዳለሁ፡፡ 

(አቶ መብራቱ መረሳ፣ ከአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ

2 comments:

  1. https://www.eotc-trinity.se/am/news-am/39-previous-parish-council

    ReplyDelete
  2. YE ZAREW SEW GIN RASUN KE PATRYARIC ENA KE BITSIAN ABATOCH BELEAY ADRGO ENDIYAY MINDNEW YANESASAW

    ReplyDelete