Tuesday, March 25, 2014

የነቀዙት ‹‹ሃይማኖተኞች›› የመጨረሻዋ ጥይት



(አንድ አድርገን መጋቢት 16 2006 ዓ.ም)፡ከዛሬ ዐሥራ አምስት ዓመት በፊት በጦቢያ መጽሔት ንቅዘትን አስመልክቶ በቀረበ መጣጥፍ ውስጥ በሃይማኖተኝነት ሽፋን «ሃይማኖተኞች» ንቅዘትን እንዴት እንደሚፈጽሙ የምትገልጥ ትንሽ ታሪክ አስፍሯል፡፡ ታሪኩ እንዲህ ነው፡፡ በ፲፱፻፶ዎቹ መጀመሪያ ላይ የየረርና ከረዩ አውራጃ ገዢ የነበሩት ባለሥልጣን ናዝሬት ላይ የቅድስት ማርያምን ቤተ ክርስቲያን በምእመኑ መዋጮ አሠሩ፡ ፡ በወቅቱ የተደነቀውን ቤተ ክርስቲያን ጃንሆይ ከጎበኙ በኋላ ፊት ለፊት የተሠራውን ድንቅ  መኖሪያ ቤትም ተመለከቱና «ይህን ያሠራው ማነው?» ብለው ይጠይቃሉ፡፡ የአውራጃው ገዢ ምንም ዐይነት መልስ እንደማይሰጡ የተረዱት አረጋዊው ነጋድራስ ተሰማ እሸቴ «ጃንሆይ፤ ማርያም ሠራችው» ብለው አግድሞሽ መልስ ሰጡ ይባላል፡፡ ቤተ ክርስቲያን አሠሪ የሆኑ የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴ የሆኑት በገዢነታቸው ሳይሆን በሃይማኖተኝነታቸው ነው፡፡ ምእመኑም ገንዘቡን አውጥቶ በእምነት ሲሰጥ ሃይማኖተኛ ናቸው ብሎ እንጂ ገዢ ናቸው ብሎ አይደለም፡፡ የሆነው ግን ሃይማኖተኝነት ያጎናጸፋቸውን መታመን እንደምቹ አጋጣሚ በመጠቀም «ማርያም ሠራችው» ዐይነት ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ሠርተው፣ በንቅዘት የራሳቸውንም ጎጆ ቀልሰዋል፡፡

ይህ ትናንት ነው፤ ዛሬ አይደለም፡፡ ትርፋማ ንቅዘት ልንለው እንችላለን፡፡ ቢያንስ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑ ተሠርቷል፡፡ ባይሆን ዋናው ጉዳይ ለምልክት እንኳን ታይቷል፡፡ እንደዛሬው የአመጽ አቀጣጣች «በጠልፎ ኪሴዎች» እጅ ሙሉ በሙሉ አልወደቀም፡፡ በእርግጥ በሃይማኖት የንቅዘት ትንሽና ትልቅ ኖሮ ሳይሆን አሁን ካለው ነቀርሳዊ ንቅዘት /Malignant Corruption/ አኳያ የተሻለ ነው ለማለት ነው፡፡ ምክንያቱም እንደ ዘመነኞቹ ሃይማኖተኞች ምኑንም ሳይዙ ፣ ምኑንም ሳይጀምሩ ለኪስ ማሰብ ብቻ አልታየም፡፡ ከመቶ ዐሥሩን ወስዶ ዘጠናውን ለሥራ የሚያውል ቢገኝ መልካም ነበር፡፡ አሁን እኛ ይህን እንኳን ማግኘት ቸግሮናል፡፡ በድሬ ደዋ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን የተዘረፈው ገንዘብ ሌላ ሦስትና አራት ቤተክርስቲያኖችን የሚሰራ ነው፡፡ ነገር ግን አሁን የሚታየው አዲሱ ንቅዘት ከወትሮው ሁሉ እጅግ የከፋና የተለየ ይመስለናል፡፡ የንቅዘቱ ደረጃ እንደሻገተ እህል ሆኗል፡፡  ካለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ወዲህ ቀስ ብሎ በቤታችን ባሕል የሆነው ነቀርሳዊ ንቅዘት ጫፍ ላይ ከመድረሱ የተነሣ የበሽታው ተጠቂዎች እየበረከቱ ሲመጡ ተመልክተናል፡፡ የበጎ ፈቃድ አገልግሎቱን ትተን ነቀርሳዊ በሆነ ንቅዘት በነቀዞቹ የተሾመው ሹም የወደፊት ሁኔታ ስንመለከት እርሱም ያወጣውን ገንዘብ እያሰላና ያወጣውን እስኪያወራርድ በሃይማኖተኝነት ስም ንቅዘትን እየፈጸመ «ሃይማኖተኛ» መስሎ ይኖራል፡፡ የንቅዘታዊ ሙስና ጥቅም በሹማምንት ደም ሥር ውስጥ እንደ አስፈላጊ ቅድመ ሁኔታ ይታያል፡፡ ጉቦን፣ ሙዳይ ምጽዋት ማድፋፋትን፣ የሹም ዘረፋንና የመሳሰለውን እንደ ባሕል ይዘው የቀጠሉ ይመስላሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች ይህን አካሄዳቸውን የሚያረግብ ነገር ፈጽሞ መስማትም ሆነ ማየት አይፈልጉም ፤ በመንገዳቸው ላይ የተገኙትን ሰዎች በአንድም በሌላም መንገድ መጋፈጥ የህልውና ጉዳይ ሆኖባቸው ይታያል፡፡

በንቅዘት የተዘፈቁና ሃይማኖታዊ ብኩርናቸውን ለከበርቴም ሆነ ለመንግሥት ሹም እንዲሁም ለአፅራረ ሃይማኖት ጭምር መሸጥን የያዙ የትናንትም ሆነ የዛሬ /በሃይማኖተኝነት ስም የነቀዙ ሃይማኖተኞች/ ሹሞች እውነትን ለመናገር፣ እውነትን ለመወሰንና ትክክለኛ ዳኝነትን ለመስጠት የሞራል የበላይነት አይኖራቸውም፤ ሊኖራቸውም አይችልም፡፡ አሁንም እንደ ቀድሞ በቅዱስ ፓትርያርኩ ዙሪያ ተሰልፎና  ተጠግቶ አብረዋቸው ከቤተ ክህነቱም  ማዕድ እንደአሻቸው እየጎረሱ ያሉትን ሁሉ ማሰብ ይቻላል፡፡ እነዚህን የመሰሉ ሰዎች ናቸው በቤተክርስቲያኒቱ ሊካሄድ የታሰበውን መዋቅራዊ ለውጥን አጥብቀው በመቃወም አንዱን ከሌላው ጋር ለማጋጨት በሆቴሎች የሚሰበሰቡት ፤ አድብተውና አስልተው ጠልፎ መጣያ ያሉትን ገመድ በመጠቀም የማያዋጣ ቁማር በመጫወት መሰረታዊ መናወጥን በቤተክርስቲያኒቱ ሊያመጡ ያሰቡት፡፡
ርካሽ ኬጂቢያዊ ስልት  የእኛዎቹ ሽፍቶች  የሚፈልጉትን ውሳኔ ለማስወሰን ሲጠቀሙበት በተደጋጋሚ ታይተዋል፡፡ በተለይ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት የሚወሰኑት ውሳኔ ቤተ ክርስቲያኒቱን ጠቅሞ የእነርሱን ምጣኔ ሀብታዊና አስተዳደራዊ ተጠቃሚነታቸውን የሚጎዳ ሆነው ካገኙት ተጽዕኖ ፈጣሪ ወደ ሆኑ አባቶች ስልክ በመደወል ማስፈራራት ይጀምራሉ ፤ ውሳኔዎች ተፈጻሚነት እንዳይኖራቸው በግልም ሆነ በቡድን በመሆን ሰዎችን ያስፈራራሉ ፤ እንደ አሁኑ ጊዜ መዋቅራዊ ለውጥን ሲሰሙ ይህን ያደረገው ማኅበር ይህ ነው በማለት የለመዱት ጥቅሞቻቸው እንዳይቀርባቸው ከመንግሥት ጋር ለማላተምና በሚፈጠረው ቀውስ የታሰቡት ለውጦች እንዲንጓተቱ ብለውም እዲቀሩ የማድረግ ስራ ይሰራሉ፡፡
 
ነቀርሳዊ ንቅዘት ወይስ «ነጭ ለባሽነት»?
በእርግጠኝነት ግን አንድ ነገር መናገር እንችላለን፡፡ እኚህን የመሰሉ በሃይማኖተኝነት ስም የነቀዙ «ሃይማኖተኛ» ሹማምንትን ተጠግተው በንቅዘት መዘፈቃቸውን ብቻ ሳይሆን በቤተ ክህነቱ ውስጥ ለሚታየው ለኦርቶዶክሳዊ ሞራል መላሸቅ አስተዋፅኦ እያደረጉ መሆናቸውን ፡፡ በእነዚህ ሰዎች ዙሪያ ያሉ ሰዎችን ስንመለከት ቤተ ክርስቲያኒቱን ለማጥፋት በአቋም የተነሡ መሆናቸው ይገባል ፤  እናም ሰዎቹ ከምጣኔ ሀብታዊ ተጠቃሚነታቸው ባሻገር በሃይማኖተኝነት ሽፋን ቤተክርስቲያኒቱን የማፍረስ «ነጭ ለባሽነት» ሚና እየተጫወቱ ይገኛል፡፡ ከተዘፈቁበት ነቀርሳዊ ንቅዘት በላይ «ነጭ ለባሽነት» ሚናቸው እስከምን ነው? የሚለው ጥያቄ መመለስ እንዳለበት ጽኑ እምነታችን ነው፡፡ ሚናቸው ኢኮኖሚያዊ ድልቦችን በማደለብ ብቻ የተወሰነ አይመስለንም፡፡ ይሁንና ቤተክርስቲያኒቱ ከተዘፈቀችበት ችግር፣ ከወደቀችበት አዘቅት ሳትወጣና ሳታገግም እነዚህ ሰዎች ለሕዝበ እሥራኤል ከወረደው መና የበለጠ በንቅዘት ከብረው ታይተዋልና፡፡



ጊዜው ሲደርስ በቀድሞው መንገድ መቀጠል አይቻልም
ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት በሃይማኖተኝነት ስም የነቀዙ «ሃይማኖተኞች» በቤተክርስቲያኒቱ ላይ ጥላቸውን ጥለውባታል፤ አሻራቸውን አሳርፈውባታል ፤ ነጋዴ ነግዶ ከሚያተርፈው በላይ የቤተክርስቲያንን ብር በተለያዩ ባንኮች በስማቸው ዘርፈው አስቀምጠዋል ፤ በአዲስ አበባ በሙዳይ ምጽዋት ብር የተሰሩ ሁለትና ከዚያም በላይ የሆኑ ቪላዎችን ያከራያሉ ፤ ቤተክርስቲያኒቱ የምታከራያቸውን ቤቶች በሞኖፖል ተቆጣጥረው የቤተሰብ እስኪመስል ድረስ በከፍተኛ ብር እያከራዩ ከገቢውም ተጠቃሚ እየሆኑ ይገኛሉ ፤ ይህን ጉዳይ ፓርላማ ድረስ ምዕመኑ አቤቱታውን ቢያደርስም የአፈጉባኤው አማካሪ  ‹‹ፓርላማው ይህን ጉዳይ የማየት ስልጣን አልተሰጠውም ፤ ስለዚህ መልስ ልሰጥበት አንችልም›› በማለት መልስ ሰጥቶበታል፡፡ እነዚህ ሰዎች በትውልድና በታሪክ ፊት ምስክርነት ይቆያቸዋል፤ ፍርድ ይጠብቃቸዋል፡፡ እምነት አጥተው በሠሩበት ሳይከበሩና ሳይወደዱ በሥልጣን በቆዩበት ዘመን ላደረሱት ግፍና ለፈጠሩት ትርምስ እስካሁን የተፈጠረውን ጥላቻ በአይነት እንደመመለስ ብንወስድ እንኳን ውርደቱ ገና ነው፡፡ የመንግሥት ሹሞችን ምርኩዝ በማድረግ በፈጠራ ድራማ አንጻራዊ ሰላምን ለማደፍረስ  መጣር ከታሪክ ተወቃሽነትና ተጠያቂነት አያድንም ፤ የቤተክርስቲያኒቱ ልዕልና መደፈር አንድ ምልክት ይህ ነው፡፡

ይህ ደግሞ ቤተክርስቲያኒቱ የምትመራው ሕይወት ረጋ ያለ የሚመስል ዳሩ ግን በእሳተ ገሞራ ላይ የተቀመጠች ከተማ ሕይወት ነው፡፡ ምክንያቱም በዛሬው ዘመን ያለው መቆርቆዝ፣ በመሪዎቻችን አማካኝነት የቤተክርስቲያኒቱ መዋረድ፣ የቤተክርስቲያን ጥቅም የሚባል ነገር ትርጉም ማጣት፣ የቤተ ክርስቲያን ሀብት ወደ ጥቂት ሰዎች ኪስ የመግባቱ ሒደት አለመገታት፣ የቤተክርስቲያን አንድነትና ሰላም ዋስትና ማጣት ይችን ቤተክርስቲያን ለአዲስ ዓይነት መከራ የሚያዘጋጅ ይመስለናል፡፡ ግፍ ሲጠራቀም፣ ጊዜው ሲደርስ በቀድሞው መንገድ መቀጠል አይቻልምና፡፡

………………………………………………..
አሁን ላይ በታሪክ የመጀመሪያዋ ገናናዋ ቤተክርስቲያን ሕልምና ዓላማዎች ያጣች ትመስላለች፡፡ የጀግኖች እናት፣ የሰማዕታት ቤት ቤተክርስቲያን ዛሬ የብዙሃን ሰብሳቢነትና ተንከባካቢነት አልተሰማትም፡፡ ካህናቱ፣ ምእመኑና ገዳማቱ ያለባቸው መከራ መጪውን ጊዜ ይጠቁማሉ፡፡ ክርስቶስ «ምልክቱን ከበለስ ፍሬ ታውቁታላችሁ» ነበር ያለው፡፡ የቤተክርስቲያኒተን መጪ ጊዜ ከወቅቱ ጥላ ለማወቅ ይቻላል፡፡ ያለንበት የፕትርክና ዘመን ካለፈው የሚከብድና የሚያስጨንቅ አለመሆኑን እርግጠኛ ሆነን መናገር አንችልም፡፡ በሃይማኖተኝነት ስም ሙዳይ ምጽዋት ላሽና ጀርባ ነካሽ «ሃይማኖተኛ» እስካሁን አላጣንም፡፡ ሰዎቹ አእምሮ ውስጥ ዘወትር ያለውም ላሽነትና ነካሽነት ነው፡፡ ከትምህርት ትምህርት፣ ከልምድ ልምድ፣ ከሃይማኖት ሃይማኖት የሌላቸው ግለሰቦች ወንበሮችን ያለአግባብ ሲይዙ ምን ያህል ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደ ኋላ እንደሚጎትቱ ፣ ምን ያህልም አንድነቷንና የታሪክ ቅሪቷን እንደሚያፈራርሱ ለመረዳት አያዳግትም፡፡

በዚህ ረገድ ሲታይ ቤተክርስቲያኒቱ ሁነኛ አመራር አጥታ ቆይታለች ብቻ አይባልም፡፡አጥፊ አገዛዝ ሥር ወድቃ ነበር ማለት ያስደፍራል፡፡ የአስተዳደራችን አካሔድ መለወጥና ከነቀርሳዊ ንቅዘት ሥርዐት መውጣት አለበት፡፡ ለዚህ ደግሞ ሥልጣንን የቤተክርስቲያኒቱ ቀኖና በሚፈቅደው አግባብ አግኝቶ ፣ ራሱን ችሎና ቀና አድርጎ የሕዝብ አገልጋይነት ሓላፊነትን የሚረከብና በገዳማዊ ሕይወቱ የተፈተኑ አባቶች ያሿታል፡፡ ዛሬ ምእመኑ በሙሉ የተሳፈረበትን የአመራር መርከብም እናስብ፡፡ በሃይማኖተኝነት ስም የነቀዙ «ሃይማኖተኞች» ያሰናከሉት መርከብ ነው፡፡በሰፊው ውቅያኖስ ላይ እንደልብ ሊንሳፈፍ አይችልም፡፡ አውሎ ነፋሱ፣ ወጀቡና የባሕሩ ቁጣ ጠንካራ መርከብ ይፈልጋል፡፡ ይህ ዘመነ ፕትርክና መርከቢቱን ወዳልሆነ መስመር እንዳያነጉዳት መልሕቁን ጥሎ ቆም ብሎ ማሰብን ይጠይቀዋል፡፡ የምእመኑና የሊቃውንቱ ዕድል፣ የቤተክርስቲያን አመራር መጫወቻ ስላልሆነ  ንቅዘት ያላገኛቸው ፣ብቃት ያላቸውና ኦርቶዶክሳዊ ፍቅራቸው የተፈተነ ሰዎችን በማስጠጋት እንዲሞክሩት ማድረግ ተገቢ ነው፡፡ 

እስከመቼ አስተዳደራችን የነቀዘ? የላዕላይና የታህታይ መዋቅር ሹማምንቶቻችን እምነት የዱር ሆኖ ይቀጥላል? የአመራር አስተሳሰብ በንቅዘት ሲሻክርና ቤተክህነታዊ ሽብር ሲበዛበት ወደ ሕዝባዊ አመፅ፣ ወደ አባታዊ ክብር መንሣት መፍትሔነትና የጉልበት ተግባር ይዛወራልና፡፡ ከዚህ አኳያ በሃይማኖተኝነት ስም የነቀዘው አስተዳደርና አስተዳደሩን የከበቡት ነቀዞች ወይም የንቅዘቱ አጫዋችና አልቢተር ደስተኛ ተመልካች ሆነው ይህን ሁሉ ጨዋታ በድል አድራጊነት መንፈስ ይመለከቱታል፡፡ ምክንያቱም የምንጋራቸውን ግቦች፣ የምናከብራቸውን ኦርቶዶክሳዊ እሴቶች ተገንዝበን ለተፈጻሚነታቸው ፈቃደኞች መሆናችንን እስካሁን አላረጋገጥንም፡፡ ማረጋገጫው መንገድ ደግሞ በጥቃት ጊዜ አብሮ መሰለፍ፣ አብሮ መሥራት አብሮ መታገል ሊሆን ይገባዋል፡፡

ኦርቶዶክሳዊ ጥቅምን፣ የቤተ ክርስቲያን አንድነትን፣ የአስተምህሮ ጥበቃን ማዕከል አድርገን ከታገልን በአንድነትና በኅብረት በቤተክህነቱ የተንሰራፋውን የንቅዘት ባርነት ቀንበርን ለመስበርና አማናዊውን ሃይማኖተኝነትን አንዲት በሆነች ቤተ ክርስቲያናችን ለማስፈን የሚያግደን ኃይል አይኖርም፡፡ ይህን የምለው መልካም ካለሆኑት ሃይማኖተኛ ሹማምንት የኃይል አሰላለፍና ከቤተክርስቲያኒቱ ወቅታዊ ሁኔታዊ ግንዛቤ አንጻር ብቻ ነው፡፡ ስንነጋገርበት እንደ ባጀነው የቤተ ክህነቱ አስተዳደር ሕመምተኛ መሆኑን አውቀናል፡፡ ሕክምናውም «አንተ የንቅዘት ርኩስ መንፈስ ልቀቀው ብዬሃለሁ፡፡ ቤተክህነቱን ለቅቀህ ሒድ» ከሚለው ጸሎት ዘዘወትር ባሻገር ሁሉን አቀፍ ትግል ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን፣ ቀናኢ ምእመናንና ልዩ ልዩ ማኅበራት ስልታዊ በሆነ መንገድ አዲሱን አስተዳደራዊና መዋቅራዊ ለውጡን ለማስፈን መንቀሳቀስ ይኖርባቸዋል፡፡ መገፋትን ከመኖር ጋር የመላመድ ባሕሉና እዬዬን አርግዞ መቆዘሙ መቆም አለበት፡፡ ተናግሮ ሳይሆን በነቀዘው አስተዳደር ላይ ክፉ አስበሃል እባላለሁ በሚል መጨነቅ መቆም አለበት፡፡ በአጭሩ ቤተክርስቲያኒቱ የሐቀኛ ልጆችዋ እንድትሆን መታገል ይገባል፡፡ ከዚህ አንጻር ኦርቶዶክሳውያን ብዙ ሥራ ይጠበቅብናል፡፡

የነቀዙት ‹‹ሃይማኖተኞች››  የጀመሩት ስም ማጥፋት ፤ የማይቀረውን መዋቅራዊ ለውጥ መሸሽና ከጀርባ ጋር መወዳጀት የመጨረሻዋን ጥይት እንደመጠቀም ይቆጠራል፡፡

5 comments:

  1. የነቀዙት ‹‹ሃይማኖተኞች›› የጀመሩት ስም ማጥፋት ፤ የማይቀረውን መዋቅራዊ ለውጥ መሸሽና ከጀርባ ጋር መወዳጀት የመጨረሻዋን ጥይት እንደመጠቀም ይቆጠራል፡፡

    ReplyDelete
  2. ......... በንቅዘት መዘፈቃቸውን ብቻ ሳይሆን በቤተ ክህነቱ ውስጥ ለሚታየው ለኦርቶዶክሳዊ ሞራል መላሸቅ አስተዋፅኦ እያደረጉ መሆናቸውን

    ReplyDelete
  3. ‹‹ ማርያም መጣች ተሳለሙ ››

    እውነት ነው፡፡ በህልውናቸው ላይ ሲመጣ ስምና ግብራቸው አደባባይ ላይ ሲሰጣ ምናልባትም ነገ ወደ ወኅኒ ሊመራ የሚችል ሲመስላቸው የመጨረሻውን ጥይት አይደለም ተበድረውም ቢተኩሱ አይደንቅም፡፡ እርግጥ ነው እድሜ ለፌዴራል ጉዳዮች አንዳንድ ሹመኞች ይሁንና ሙሰኞቹና ወንጀለኞቹ ሲከሰሱና ወንጀለኛ ሊባሉ ሲሉ በሚሰጡት ድንገተኛ ትዕዛዝ ክስ ስለሚቋረጥላቸውና ፋይል ስለሚዘጋላቸው መታሰርን ሊረሱት ይችላሉ፡፡

    ማርያም ሰራችው የሚለውን ሳነብ ‹ ማርያም መጣች ተሳለሙ › ብሎ አዲስ ተገዝቶ ወደ ወረዳው የገባን አይሱዙ መኪና የሳመ አውቆ አበድ ታሪክ ትዝ አለኝ፡፡ አይሱዙ የጭነት መኪና የገዛው ሰው ወንድም ከዚያው ወረዳ አንድ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ቤ/ክ ጽላት ሰርቆ እጅከፍንጅ ተይዞ ታስሮ ነበርና መኪናዋ ደግሞ ድንገት ተገዝታ ስትመጣ ‹ እልል እያለ ኑ ማርያም መጣች ተሳለሙ › እያለ መኪናዋን ሲስም የነበረውን አስታወሰኝ፡፡ እኛም በሙሰኞች ላይ የልባችንን ለመናገር ‹ እብድ › ወይንም ‹ ዘመናይ › መሆን አለብን ማለት ነው እንዴ!

    እኛም ያደረጃቸው ከቤ/ክ በዘረፉት ገንዘብ የሲኖ ትራክ ባለቤት የሆኑትን ስናስብ መኪናውን ስናይ ‹ ኑ ማርያም/ ሚካኤል …. መጡ እንሳለም › እንበል እንዴ፤ የገነቧቸውን ፎቆች እንሳለም እንዴ፤….. አቤቱ የሆነብንን አስብ!!!!!!! ቅዱስ ፓትርያርካችን በያዙት አማሳኞችን ባመታስ አቋም መጽናታቸው ይናፍቀናል፡፡ መንግስት ጸረ ሙስና አቋሙን የቤ/ክንን የጸረ ሙስና አቋም በመደገፍ ማሳየት አለበት፡፡ ሙሰኞችን የሚደግፍ ሥራው ግን ግለሰቦችን ከመንቀፍ አልፈን ጥቅል መንግስት ላይ እንድናኮርፍ እንደሚያደርገን ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ አሁንም ጀማምሮናል… የቤ/ክ አምላክ ለመሪዎቻችን ልብንና ልቡናውን ያድልልን!!!!!! ‹‹‹‹‹ በእና ኃጢያት ምክንያት ነውና ክፉ መሪ የሚሾምብን እኛንም ይቅር ይበለን፡፡ ››››››››
    ‹‹ ማርያም መጣች ተሳለሙ ››

    እውነት ነው፡፡ በህልውናቸው ላይ ሲመጣ ስምና ግብራቸው አደባባይ ላይ ሲሰጣ ምናልባትም ነገ ወደ ወኅኒ ሊመራ የሚችል ሲመስላቸው የመጨረሻውን ጥይት አይደለም ተበድረውም ቢተኩሱ አይደንቅም፡፡ እርግጥ ነው እድሜ ለፌዴራል ጉዳዮች አንዳንድ ሹመኞች ይሁንና ሙሰኞቹና ወንጀለኞቹ ሲከሰሱና ወንጀለኛ ሊባሉ ሲሉ በሚሰጡት ድንገተኛ ትዕዛዝ ክስ ስለሚቋረጥላቸውና ፋይል ስለሚዘጋላቸው መታሰርን ሊረሱት ይችላሉ፡፡

    ማርያም ሰራችው የሚለውን ሳነብ ‹ ማርያም መጣች ተሳለሙ › ብሎ አዲስ ተገዝቶ ወደ ወረዳው የገባን አይሱዙ መኪና የሳመ አውቆ አበድ ታሪክ ትዝ አለኝ፡፡ አይሱዙ የጭነት መኪና የገዛው ሰው ወንድም ከዚያው ወረዳ አንድ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ቤ/ክ ጽላት ሰርቆ እጅከፍንጅ ተይዞ ታስሮ ነበርና መኪናዋ ደግሞ ድንገት ተገዝታ ስትመጣ ‹ እልል እያለ ኑ ማርያም መጣች ተሳለሙ › እያለ መኪናዋን ሲስም የነበረውን አስታወሰኝ፡፡ እኛም በሙሰኞች ላይ የልባችንን ለመናገር ‹ እብድ › ወይንም ‹ ዘመናይ › መሆን አለብን ማለት ነው እንዴ!

    እኛም ያደረጃቸው ከቤ/ክ በዘረፉት ገንዘብ የሲኖ ትራክ ባለቤት የሆኑትን ስናስብ መኪናውን ስናይ ‹ ኑ ማርያም/ ሚካኤል …. መጡ እንሳለም › እንበል እንዴ፤ የገነቧቸውን ፎቆች እንሳለም እንዴ፤….. አቤቱ የሆነብንን አስብ!!!!!!! ቅዱስ ፓትርያርካችን በያዙት አማሳኞችን ባመታስ አቋም መጽናታቸው ይናፍቀናል፡፡ መንግስት ጸረ ሙስና አቋሙን የቤ/ክንን የጸረ ሙስና አቋም በመደገፍ ማሳየት አለበት፡፡ ሙሰኞችን የሚደግፍ ሥራው ግን ግለሰቦችን ከመንቀፍ አልፈን ጥቅል መንግስት ላይ እንድናኮርፍ እንደሚያደርገን ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ አሁንም ጀማምሮናል… የቤ/ክ አምላክ ለመሪዎቻችን ልብንና ልቡናውን ያድልልን!!!!!! ‹‹‹‹‹ በእና ኃጢያት ምክንያት ነውና ክፉ መሪ የሚሾምብን እኛንም ይቅር ይበለን፡፡ ››››››››

    ReplyDelete
  4. አሁን ላይ በታሪክ የመጀመሪያዋ ገናናዋ ቤተክርስቲያን ሕልምና ዓላማዎች ያጣች ትመስላለች፡፡ የጀግኖች እናት፣ የሰማዕታት ቤት ቤተክርስቲያን ዛሬ የብዙሃን ሰብሳቢነትና ተንከባካቢነት አልተሰማትም፡፡ ካህናቱ፣ ምእመኑና ገዳማቱ ያለባቸው መከራ መጪውን ጊዜ ይጠቁማሉ፡፡

    ReplyDelete
  5. የነቀዙት ‹‹ሃይማኖተኞች›› የጀመሩት ስም ማጥፋት ፤ የማይቀረውን መዋቅራዊ ለውጥ መሸሽና ከጀርባ ጋር መወዳጀት የመጨረሻዋን ጥይት እንደመጠቀም ይቆጠራል፡፡

    ReplyDelete