Saturday, March 16, 2013

“ነብዩ ኤልያስ በአራት ኪሎ” አዲስ ሃይማኖት ?



  • ኤልያስ ብቻውን አይመጣም ፤ አብሮት ሄኖክም ይመጣል ::
  • “የኢትዮጵያ ትንሳኤ ሊያረጋግጥ ኃያል ባለስልጣን ቅዱስ ኤልያስ ከብሔረ ሕያዋን መጥቷል”  አርቲስት ጀማነሽ ሰለሞን ለሚዲያዎች የበተነችው መልዕክት
  • ሐሳዊ መሲሕ የሚነግሠው ፤ ኄኖክና ኤልያስም የሚገለጡት ‹በተቀደሰችው ከተማ” በኢየሩሳሌም ነው፡፡ በኢየሩሳሌምም ሐሳዊ መሲህ ገና አልነገሰም፡፡
  • በ2012 የተደረሰ አንድ ጥናት ባለፉት 3 ዓመታት በአሜሪካ ውስጥ 132 ሰዎች መሲሕ ነን ብለው ተነስተው ወደ 4.5 ሚሊየን የሚደርስ ሕዝብ አስከትለዋል፡፡


(አንድ አድርን መጋቢት 7 2005 ዓ.ም)፡- አንድ አድርገን  ኤልያሳውያን የዛሬ አመት በመሀል አዲስ አበባ አራት ኪሎ ላይ ሲያቆጠቁጡ በነበረበት ጊዜ ከተማ ውስጥ ሰዎችን ለመሳብ የበተኑትን ወረቀት ብሎጋችን ላይ በመለጠፍ በጊዜው ሰዎች ከእዚህ አይነት እንቅስቃሴ ራሳቸውን እንዲጠብቁ መልዕክት አስተላልፋ ነበር፡፡ ማኅበረ ሥላሴ ዘደቂቀ ኤልያስ የጽዋ ማኅበር ስብስባቸውን የጀመሩት ጥቂት ሰዎች ዛሬ ቁጥራቸው እየጨመረ ይገኛል ፡፡ በቅርቡ እጅጉን ብዙ ሰው ለመሳብ ይረዳቸው ዘንድ በአዲስ አበባ ኢግዚቢሽን ማዕከል ትልቅ የሚባል ፕሮግራም እንዳዘጋጁና የኢትዮጵያንም ትንሳኤ እንደሚያበስሩ እየገለጹ ይገኛሉ፡፡ ተሀድሶያውያን ከውስጥም ከውጭም ያሉ ሰዎች ላይ መረባቸውን ጥለው አንዴ በአውደ ምህረት ፤ አንዴ በአዳራሽ ፤ ሌላ ጊዜ ደግሞ በስታዲየም እየጠሩ ሰዉን ውዥንብር ውስጥና ጥርጣሬ ውስጥ መክተታቸው ይታወሳል፡፡ የአሁኖቹ “ተዋሕዶ” ነን ባዮች ኤልያሳውያን ደግሞ ከእዚህ ለየት ያለ አካሄድ አላቸው ፡፡ ኤልያሳውንን በቅርብ ሆነን እንደተመለከትነው ስለ ትምህርተ ሃይማኖቱ ጠለቅ ያለ እውቀት አለው ብለው የሚያስቡት ሰዎች ላይ ፤ ሚስጥራትን የሚያውቁ ፤ የመንፈሳዊ ኮሌጅ ተማሪዎች እና ረዥም ጊዜ በአገልግሎት የቆዩት ሰዎችና ታዋቂ አርቲስቶች አባሎቻቸው ሆነው ተመልክተናል፡፡ ሳምንት በፊት ይህን በሚመለከት ያቀረብነው ጽሁፍ ከሀገር ውስጥም ይሁን ከሀገር ውጪ ያሉ ሰዎች እንቅስቃሴው አዲስ ነገር እንደሆነባቸውና እጅጉንም መገረማቸውን ገልጸውልናል ፡፡ምእመኑን እንደ ተሀድሶያውያን ለማስኮብለል እና ሌላ ውዥንብር ፤ ሌላ መከፋፈል ፤ ሌላ የህብረት ማጣት ውስጥ ለመክተት የተዘጋጁ ቡድኖች ከአዲስ አበባ አልፈው ወደ ክልል ከተሞች ፤ ከኢትዮጵያ አልፈው በአውሮፓ እና በአሜሪካ ሊንቀሳቀሱ ስለሚችሉ ምእመኑ መረጃውን አውቆ ራሱን ፤ ቤተሰቡንና ቤተክርስቲያንን ከእንዲህ አይነት እንቅስቃሴ አስቀድሞ በመንቃት ይጠብቅ ዘንድ መልዕክታችን ነው፡፡
የአርቲስት ጀማነሽ ሰለሞንን የሚሼሪያን ቆይታ ካወጣን በኋላ ይህን እንቅስቃሴ በሚመለከት አዲስ ጉዳይ መጽሔት ዲያቆን ዳንኤል ክብረትን ምላሽ እንዲሰጥበት በመጠየቅ አንድ ጽሁፍን ይዛ  ወጥታለች፡፡  ዲ/ን ዳንኤል የተነሱ ጥያቄዎች ተንተርሶ  ጥቂት ጉዳዮችን ይዳስሳል፡፡ “ነብዩ ኤልያስ ወደ ኢትዮጵያ መጥቷል የሚለው” ጉዳይን በመፈተሸ ሃይማኖታዊ ትንታኔ ሰጥቶበታል፡፡“ተዋህዶ” ነን ባዮች አስተምህሮዋቸውን በሚመለከት አዲስ ጉዳይ ላይ የወጣውን እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡

(አዲስ ጉዳይ መጋቢት 7)፡- ተዋናይት ጀማነሽ ሰለሞን የካቲት 25 ቀን 2005 ዓ.ም ለአዲስ ጉዳይ መጽሔትና ለሌሎች ሚዲያዎች በበተነችው ጥሪ “የኢትዮጵያ ትንሳኤ ሊያረጋግጥ ኃያል ባለስልጣን ቅዱስ ኤልያስ ከብሔረ ሕያዋን መጥቷል” ብላለች፡፡ ጀማነሽ “ይህንን እጅግ ታላቅ አስፈሪና ጥልቅ ሃይማኖታዊ ምስጥር በተመለከተ ትንታኔና ትምህርት የሚሰጥበት ጉባኤ ከጽዋ ማኅበሬ ጋር በመሆን አዘጋጅቻለሁና በኢግዚቢሽን ማዕከል ተገኝታችሁ ተካፈሉልኝ” በማለት ነው ግብዣውን የላችው፡፡ በግዕዝ በአማርኛ እና በእንግሊዘኛ በተጻፈውና ማኅበረ ሥላሴ ዘደቂቀ ኤልያስ .. ብሎ የሚጀምረው  የጽዋ ማኅበሯ  አማካኝነት በበተነችው ጥሪዋ “በጉባኤው የኢትዮጵያ ትንሳኤ ይታወጃል” ብላለች፡፡ የተለያዩ አርቲስቶችና ሌሎች ታዋቂ ሰዎች እየተሳተፉበት መሆኑ የሚነገረው በዚህ ጉባኤ ላይ  የተለያዩ ወገኖች ጥያቄ በማንሳት ላይ ይገኛሉ፡፡በብዙዎች ዘንድ ይህ እንቅስቃሴ ከዚህ ቀደም ተሐድሶ በሚል ስያሜ እንደተካሄደው ዓይነት በኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ጥላ ስር አዲስ ሃይማኖት ፤ አዲስ አስተምህሮ የመመስረት አላማ ያለው ነው የሚል አስተያየት እየተሰነዘረበት ነው፡፡ ለመሆኑ ይህ “ተዋሕዶ” የሚል ስያሜ በመካሄድ ላይ ያለው እንቅስቃሴ ከኦርቶዶክስ እምነት አንጻር ምን ያህል ተቀባይነት አለው? የነብዩ ኤልያስ ወደ ኢትዮጵያ መምጣትስ ምን ያህል ተዓማኒ ነው? የዚህ እንቅስቃሴ መሰረታዊ ባህርያት ምን ምን ናቸው? እነዚህንና ሌሎች ጥያቄዎች እንዲመልስን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን  የእምነት መሰረቶችና ከኦርቶዶክስ ሃይማኖት ጋር የተያያዙ በርካታ መጽሀፍት ደራሲ የሆነው ዲያቆን ዳንኤል ክብረትን ጋብዘናል፡፡

ዲ/ን ዳንኤል ከላይ ያነሳናቸውን ጥያቄዎች ተንተርሶ በላከልን ጽሁፍ በርካታ ጉዳዮችን ይዳስሳል፡፡ “ነብዩ ኤልያስ ወደ ኢትዮጵያ መጥቷል የሚለው” ጉዳይን በመሰረቱ በመፈተሸ ሃይማኖታዊ ትንታኔ ሰጥቶበታል፡፡

ሰሞኑን በከተማችን አዲስ አበባ “ነብዩ ኤልያስ መጥቷል ፤ የአለም ፍጻሜ ቀርቧል”  የሚሉ አካላት ተነስተዋል፡፡ እነሱ እንደሚሉት ነብዩ ኤልያስ መጥቶ አዲስ አበባ ይገኛል፡፡ ቤተመንግሥቱንና ቤተክህነቱን ለማጥራት ተዘጋጅቷል ፡፡ ከሚያጠራቸው የቤተክህነት ጉዳዮችም ሦስቱ ትኩረት አግኝተዋል ይላሉ፡፡ “የመጀመሪያው ኦርቶዶክስ የሚለው ስም ስህተት ነው  ፤ ስማችን ተዋህዶ ነው ፤ መለበስ ያለበት ልብስ ነጭ ብቻ ነው ፤  እሱም ቢሆን ጥለቱ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ መሆን መቻል አለበት ፤ አሁን ያሰርነውን ክር በመበጠስ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ክር ማሰር አለብን” የሚል ነው፡፡ በየአጋጣሚው ቤተክህነቱንና ቤተ መንግሥትን በመንቀፍ አሁን የሚታዩትን ችግሮች መሰረት አድርጎ ህዝቡ መጥቷል የተባለው ኤልያስን መከተል እንጂ ወደ ቤተክርስቲያን መሄዱ ጥቅም እንደሌለው እየተነገረ ነው፡፡ የሚከናወኑ ማናቸውም የፖለቲካ እንቅስቃሴዎችም የኤልያስን መምጣት የሚያመላቱ እንጂ ምዕመና ሊሳተፍባቸው የሚገቡ አለመሆናቸው ይነገራል ፡፡ እስኪ እነዚህ ነገሮችን በዝርዝር እንመልከታቸው፡፡

ኤልያስ ማነው?
ኤልያስ ማለት “እግዚአብሔር አምላክ ነው” ማለት ነው፡፡ከክርስቶስ ልደት በፊት በስምንተኛው መቶ ክፍለ ዘመን አካባቢ ከእስራኤል የተነሳ ነብይ ነው፡፡ኤልያስ የሚታወቀው በሶስት ሃይማኖታዊ ተግባሮች ነው፡፡የመጀመሪያው በእስራኤል ተንሰራፍቶ የነበረውን የባአድ አምልኮ ያጠፋና አምልኮተ እግዚአብሔርን ያጸና መሆኑ ሲሆን ፤ ሁለተኛው ደግሞ ንጉስ አክአብ አሕዛባዊት ኤልዛቤልን አግብቶ ይፈጽም የነበረውን ግፍና ጥፋት ሳይፈራና ሳያፍር ፊት ለፊት የገሰጸና ለእውነት ብቻ የቆመ ነብይ መሆኑ ነው፡፡ በዚህ አቋሙ ምክንያት በሰሜን እስራኤል በሚገኙ ሰንሰለታዊ ተራሮች ፈፋ ለፈፋ ሲንከራተት ኖሯል፡፡ መጀመሪያ ቁራዎች ሲመግቡት ቆይተው ከዚያ በሰራፕታ የምትገኝ አንዲት መበልት አገልግለዋለች፡፡
ይህ ቆራጥነቱና ለአምልኮተ እግዚአብሔር ቋሚ መሆኑ በእግዚአብሔር ዘንድ ባስገኝለት ሞገስ የተነሳ ኤልያስ ከኄኖክ ቀጥሎ ሳይሞት ወደ ብሔረ ሕያዋን በመወሰዱ ይታወቃል፡፡ ዮርዳኖስን ወንዝ ከደቀ መዝሙሩ ከኤልሳዕ ጋር ከተሻገረ በኋላ የእሳት ሰረገላ መጥቶ ኤልያስን ወስዶታል፡፡ ይህ ኤልያስ የሚታወቅበት ሦስኛው ነገር ነው፡፡

ኤልያስ ይመጣል ?
ከ470 እስከ 440 በኢየሩሳሌም ትንቢት የተናገረው ነብዩ ሚልኪያስ “የእግዚአብሔር ቀን ነብዩ ኤልያስን እልክላችኋለሁ” ብሎ ትንቢት ተናግሮ ነበር፡፡ (ሚል 4፤5) ይህንንም በመያዝ አይሁድ በፋሶች ፤ በግሪኮች ፤ በሶሪያውያንና በሮማውያን መከራ በተፈራረቁባቸው 400 ዓመታት ውስጥ ነብዩ ኤልያስን ሲጠባበቁት ነበር፡፡  በየምኩራባቸውም የኤልያስ መንበር የተባለ ከፍ ብሎ የተሰራ ባለ መከዳ ወንበር ያስቀምጡ ነበር፡፡ ከክርስቶስ ልደት 6 ወራት ቀድሞ ተወለደውና  ከበረሀ የመጣው መጥምቁ ዮሐንስ በብዙ መልኩ ኤልያስን ይመስለው ስለነበረ የተወሰኑት የአይሁድ ክፍሎችና በኋላም ክርስቲያች ይመጣል የተባለው ነብዩ ኤልያስ እርሱ ነው ብለው ተቀብለውታል፡፡

ዮሐንስ መጥምቅ እንደ ኤልያስ ሁሉ በርኽኛ ባህታዊ ነው፡፡ እንደ ኤልያስ ሁሉ ጸጉር የለበሰ ነው ፤ እንደ ኤልያስ ሁሉ እስራኤል ተስፋ የቆረጠችበት ዘመን የመጣ ነው ፤ እንደ ኤልያስ ሁሉ ሄሮድስን ሳያፍርና ሳይፈራ የገሰጸ ነው ፡፡ በእነዚህ እና በሌሎች ምክንያቶች መጥምቁ ዮሐንስ ኤልያስን ይመስለው ነበር፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ይመጣል የተባለው ኤልያስ መጥምቁ ዮሐንስ መሆኑን መስክሮለታል፡፡(ማቴ 11፤14 17፤10-13 ፤ ሉቃ 1፤17)

ስለ ኤልያስ መምጣት የሚነግረን ሌላው መጽሀፍ የዮሐንስ ራዕይ ነው፡፡ ዮሐንስ ራዕይ በምዕራፍ 11 ላይ ዓለምን የሚያጠፋው ሀሳዊ መሲህ  ከመጣ በኋላ ዙፋኑን አደላድሎ የዓለምን ክርስቲያኖች ሲጨርስና ምስክር ሲጠፋ ሁለት ምስክሮች መጥተው 1260 ቀናት ምስክርነት እንደሚሰጡና በመጨረሻም በሐሳዌ  መሲህ እንደሚገደሉ ይገልጣል፡፡ ከሁለተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ የተነሱ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን እነዚህን ሁለት ምስክሮች ኄኖክና ኤልያስ መሆናቸውን ተርጉመዋል፡፡

ሐሳዊ መሲሕ ሲነሳና ሁሉንም እንደ ሰም አቅልጦ እንደ ገል ቀጥቅጦ ሲያጠፋ ፤ ለእውነት የሚመሰክርም ሲጠፋ ፤ ምዕመናንም በሚደርሰው መከራ ምክንያት የሚከተሉት የእምነት መንገድ  “ስህተት ይሆን…” ብለው ሲጠራጠሩ እነዚህ ሁለቱ ሳይሞቱ ወደ ብሔረ ሕያዋን ያረጉ ነብያት መጥተው እውነትን በመመስከርና የሐሳዌ መሲሕን ነገር በማጋለጥ ምስክርነታቸውን በደም እንደሚያጸኑ የሊቃውንቱ ትርጓሜ ያብራራል፡፡

ዮሐንስ አፈወርቅ ፤ አቡሊዲስ ዘሮምና ቪክቶሪያንስ እንደሚገልጡት ኤልያስና ኄኖክ በኢየሩሳሌም ያስተምራሉ ፤ በኢየሩሳሌም ተዓምራት ያደርጋሉ ፤ በኢየሩሳሌም ይገደላሉ ፤ በኢየሩሳሌም ይነሳሉ ፤  በኢየሩሳሌም ያርጋሉ ፡፡ ይህም ለጌታችን መምጣት የመጨረሻው ምልክት ነው፡፡ ከኤልያስና ኄኖክ  መምጣት በኋላ የሚጠበቀው የክርስቶስ ለፍርድ መምጣት ነው፡፡

ነብዩ ኤልያስ  በአራት ኪሎ
በአሁኑ ሰዓት ኢትዮጵያ ውስጥ ነብዩ ኤልያስ መጥቷል ይባላል፡፡ የሚኖረው አራት ኪሎ ነው፡፡ አንዳንድ ታዋቂ የሆኑ ሰዎች  በተለይም አርቲስቶች ተከታዮች ሆነናል ይላሉ፡፡ ይህንን ሁኔታ ከቅዱሳት መጻህፍትና ከሊቃውንት ትምህርት ጋር ስናነጻጽረው ትክክል ሆኖ አናገኝውም፡፡

መጀመሪያ ነገር ኤልያስ ብቻውን አይመጣም፡፡ በነብዩ ሚልኪያስ ለብቻው እንደሚመጣ  የተነገረለት  ኤልያስ መጥምቁ ዮሐንስ መሆኑን ራሱ ጌታችን ኢየሱስ ስለ መሰከረ ሌላ ምስክር ማምጣት አያስፈልግም፡፡  በሌላ በኩልም አሁን መጥቷል ተባለው  በመጨረሻው ዘመን የሚመጣው ኤልያስ  ከሆነ ደግሞ እንደ ሊቃውንቱ ትምህርት ብቻውን አይመጣም ፤ አብሮት ኄኖክም ይመጣል፡፡ አሁን ግን  ኤልያስ ከኄኖክ ተነጥሎ ነው መጣ የተባለው፡፡

ይህ ብቻ አይደለም፡፡ ነብዩ ኤልያስ የሚመጣበት ጊዜ በራዕይ ዮሐንስ ላይ ምዕራፍ 11 ተገልጧል፡፡  አስቀድሞ ሐሳዊ መሲህ ይመጣል፡፡ ዙፋኑንም በተቀደሰችው ከተማ በኢየሩሳሌም ይዘረጋል፡፡ ምዕመናንም(በተለይም የስድስት ስድሳ ስድስትን አምልኮ ያልተቀበሉትን) በግፍ ይገድላቸዋል፡፡ በዚህም ጊዜ እውነት ትቀጥንና ምስክር ታጣለች ፤ ኤልያስና ኄኖክ የሚመጡትም እውነትን በአደባባይ ለመመስከር ነው፡
ይህ ከሆነና በአዲስ አበባ እየተባለ እንዳለው ኤልያስ ከመጣ ሐሳዊ መሲህ መጥቷል ማለት ነው፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን ምዕመናን በግፍ ተገድለዋል ፤ በዓለምም ላይ አማኞች በአብዛኛው አልቀዋል ማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ ሲፈጸም አላየነውም፡፡ በኢየሩሳሌምም ሐሳዊ መሲህ ገና አልነገሰም፡፡

ሌላም ሦስተኛ ነገር መነሳት አለበት፡፡ ሐሳዊ መሲሕ የሚነግሠው ፤ ኄኖክና ኤልያስም የሚገለጡት ‹በተቀደሰችው ከተማ” በኢየሩሳሌም ነው፡፡ የሚሠውትም  እዚያ መሆኑን “እርስዋም  በመንፈሳዊ ምሳሌ ሶዶምና ግብጽ የተባለችው  ደግሞ ጌታችን የተሰቀለባት ናት› ብሎ ኢየሩሳሌም መሆኗን  ነግሮናል(ራዕይ 11፤8) ፡፡ አሁን ግን ኤልያስ ተገለጠ የተባለው ያለው አዲስ አበባ አራት ኪሎ ላይ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ተልዕኮውም ከመጽሀፍት ጋር የሚጣረስ ነው፡፡ ጌታ የተሰቀለው አራት ኪሎ ነው ካላልን በቀር፡፡

ራዕይ ዮሐንስ እንደሚነግረን ኄኖክና ኤልያስ ምስክርነት የሚሰጡት ለ1260 ቀናት ወይም ለ42 ወራት ወይም ለሦስት ዓመት ከስድስት ወራት ነው፡፡ አሁን ግን አዲስ አበባ መጣ የተባለው ኤልያስ መጣ ከተባለ አራት ዓመት ሊያልፈው ነው፡፡

ምጽአትና መሲሕን መናፈቅ
በዓለም ሆነ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የምጽአትን ቀን የመናፈቅና የምጽአትን ምልክቶች ደርሰዋል ብሎ የመጨነቅ አዝማሚያ የሚከሰትባቸው ምክንያቶች አሉ፡፡ እነዚህም ኢኮኖሚያዊ ፤ ማህበራዊ እና ፖለቲካዊ ቀውሶች ሲከሰቱና ሕዝብ ተስፋ ሲቆርጥ ነው፡፡

እስራኤራዊያን ከፋርሶችና ከግሪኮች ወረራ በኋላ ሀገራቸው ስትመሰቃቀል ፤ መንፈሳዊነት ሲጎድልና መንግሥታቸው ፈርሶ ተስፋ ወደ መቁረጥ ሲመጡ “መሲሕ እየመጣ ነው ፤ ኤልያስ እየደረሰ ነው” የሚል አስተምህሮ ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በ2ኛው መቶ ክፍተ ዘመን ጀምረው ነበር፡፡ በዚህ የተነሳ አንዳንድ ሰዎች ይመጣል የተባለው መሲሕና ኤልያስ እኛ ነን እያሉ አጋጣሚውን ሊጠቀሙበት ሞክረው ነበር፡፡ ከእነዚህ መካከል ከክርስቶስ ልደት በፊት በ2ኛውና አንደኛው መ.ክ.ዘ ላይ የተነሱ ቴዎዳስና ይሁዳ ይጠቀሳሉ፡፡ ቴዎዳስ አራት መቶ ሰዎችን አስከትሎ ነበር ፡፡ በኋላ ግን ሐሰተኛ መሆኑ ሲታወቅ ሕዝቡ ተወው ፡፡ ይሁዳም ሕዝቡን አስነስቶ እስከ ማሸፈት ደርሶ ነበር፡፡ መጨረሻው ግን አላማረም(የሐዋ 5፤37-39)

በቅርብ ጊዜ በኡጋንዳ ኢኮኖሚ ሰደቅና የእርስ በርስ ጦርነት ሲባባስ ይህም የሕዝቡ ማኅበራዊ ሕይወት ሲያቃውሰው “እኔ ክርስቶስ ነኝ” የሚል ሰው ተነስቶ በአንድ አዳራሽ ውስጥ  የነበሩ ተከታዮች መንግሥተ ሰማያት ለመግባት ሲሉ በእሳት ተቃጥለው እንዲያልቁ አድርጓቸው ነበር፡፡ በአሜሪካ የደረሰው ኢኮኖሚ ድቀት ካስከተላቸው መዘዞች አንዱ በየአካባቢ “እኔ መሲሕ ነኝ” የሚሉ እና  ሕዝቡ ችግሩን  ከማሸነፍ ይልቅ ችግሩን እንዲረሳው የሚያደርጉ ሰዎች  መከሰታቸው ነው፡፡ በ2012 የተደረሰ አንድ ጥናት ባለፉት 3 ዓመታት  በአሜሪካ ውስጥ 132 ሰዎች መሲሕ ነን ብለው ተነስተው ወደ 4.5 ሚሊየን የሚደርስ ሕዝብ አስከትለዋል፡፡

በሀገራችን ታሪክ በ15ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በተከሰተው የግራኝ ጦርነት በኋላ ሕዝቡ መንፈሳዊ ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ተስፋ መቁረጥ ደረጃ ደርሶ ነበር፡፡ አብያተ ክርስያናቱ ተቃጠሉ ፤ ኢኮኖሚው ወደመ ፤ መንግስት ተዳከመ ፤ ትዳና መስተጋብር የመሰሉ ማኅበራዊ ተቋማት ፈረሱ፡፡ ብዙ ሰዎች ሞቱ ፡፡ ይህ ሕዝቡ ላይ ባስከተለው ተስፋ መቁረጥ የተነሳ ከዚህ መከራ እና ስቃይ የሚያወጣውን አንዳች ሰማያዊ ኃይል ይጠብቅ ነበር፡፡

በሀገራችን ላይ የበልጥ ራዕይ ዮሐንስ የታወቀውና በገልባጮች እጅ በብዛት የተገለበጠው በዚህ ጊዜ ነው፡፡ በሚሰሩት አብያተ ክርስቲያናትም የሐሳዊ መሲህ ፤ የኤልያና የኄኖክ ፤ የአዲሲቱ ሰማይና ምድር ስዕሎች በብዛት ተሳሉ፡፡

ከግራኝ ጦርነት በኋላ በአጼ ሰርጸ ድንግል ወራሾች መካከል በተፈጠረው የርስ በርስ ውጊያ ሀገሪቱ ስትታመስና  ሕዝቡ በተደጋጋሚ ጦርነትና የሕዝብ ፍልሰት ሲታወክ እኔ ክርስቶስ ነኝ ፤ ሕዝቡንም ከችግር ላወጣውና መንግሥተ ሰማያት ላወርሰው መጥቻለሁ የሚል ሐሳዊ መሲሕ በአማራ ሳይንት አካባቢ ተነስቶ ነበር ፡፡ አስራ ሁለት ሐዋርያት ፤ 72 አርእድትንና 36 ቅዱሳት አንስትንም መርጦ ነበር፡፡ ብዙውም ሕዝብ በተስፋ መቁረጥ ላይ ስለነበረ ተከትሎት ነበር፡፡ በኋላ ግን በሞት መቀጣቱን አቡነ ጎርጎርዮስ በኢትዮጰያ ቤተክርስቲያን ታሪክ መጽሐፋቸው ጠቅሰውታል፡፡

በቅርቡ በሀገራችን ታሪክ ዐጼ ምኒሊክ አርፈው ሞታቸው በተደበቀበት ጊዜ ፤ በታህሳስ ግርግር ጊዜ ፤ በአብዮቱ ዋዜማና ማግስት ፤ እንዲሁም ኢሕአዴግ አዲስ አበባ በገባበት ጊዜ አያሌ “ባሕታውያን” ተነስተው ነበር፡፡ ይህ ነገር መጣ ፤ ብላቴን ጌታ ኅሩይ ስለ ንግሥት ዘውዲቱ  ዘመን በጻፉት የትዝታ መጽሀፋቸውም ይህንን ገልጠውታል፡ ይህም ያም ነገር ታየ ፤ ተገለጠ የሚለው ብሂልም  ነባርና የሀገር አለመረጋጋትና በኑሮ ተስፋ መቁረጥ ተገን አድርገው የሚመጡ ናቸው፡፡

የኤልያሳውያን ሁለት አስተምህሮዎች
አሁን በዘመናችን የተከሰቱ ኤልያሳውያን ሁለት ነገሮች ላይ አተኩረው እየሰሩ ነው፡፡ የመጀመሪያው “ኦርቶዶክስ” ትክክለኛ ስም አይደለም የሚለው ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ሰንደቅ አላማን ከጽድቅና ከኩነኔ ጋር ማያያዛቸው ነው፡፡

ኦርቶዶክስ የሚለው ቃል የግሪክ ሲሆን “ኦርቶ” ርቱዕ “ዶክስ” ደግሞ እምነት ፤ መንገድ ፤ ጠባይ ፤ ባህል ማለት ነው፡፡ ይህንን ስም የክርስቲያን አብያ ክርስያናት መጠቀም የጀመሩት በ325 ዓ.ም በተደረገው ጉባኤ በኋላ ነው፡፡ ከጉባኤ ኬልቄዶን የ451 ዓ.ም ጉባኤ በኋላ ደግሞ የምዕራብ አብያተክርስቲያናት ካቶሊክ ሲባሉ ምስራቆቹ “ኦርቶዶክስ”  የሚለውን ስም ይዘው ቀሩ ፡፡ በምስራቆቹ መካከል  የጉባኤ ኬልቄዶንን  ውሳኔ በመቀበልና ባለመቀበል መካከል ልዩነት ስላለ የግሪክ መሰል አብያተክርስቲያናት የምስራቅ ኦርቶዶክስ ሲባሉ  ፤ አርመን ፤ ግብጽ ፤ ሕንድ ፤ ሶሪያና ኢትዮጵያ ደግሞ “ኦሪየንታል ኦርቶዶክስ” ተባሉ፡፡

ኦርቶዶክስ ፤ ኦርዶክሳዊ የሚለው ስም በሀገራችን ቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ በሁለት መንገድ ተገልጠዋል፡፡ በአንድ በኩል ጥሬ ቃሉ እንዳለ የተቀመጠ ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ ወደ ግዕዙ ተተርጉሞ “ርቱዕ ሃይማኖት” እየተባለ ተቀምጧል፡፡ ፍትሐ ነገስት ‹ይኩን ምእመነ ኦርቶዶክሳዌ ይላል› (42፤2) ያዕቆብ ዘእልበረዲም ‹ሃይማኖት ኦርዶክሳዊት› ሲል እምነቱን ይገልጣል፡፡ መጽሐፈ ቄርሎስም ‹ሃይማኖተ ርቱዕ› እያለ ተርጉሞ ይገልጠዋል፡፡

‹ተዋሕዶ› የሚለው ቃል ነጥሮ የወጣው በጉባኤ ኤፌሶን በ431 ዓ.ም ነው፡፡ በጉባኤው ንስጥሮስን ባሕል ለማየት የተሰበሰቡ አበው በእስክንድርያ ቄርሎስ የተሰጠውን ትምህርት በመቀበል ሁለት ባሕርይ የሚለውን አውግዘው  መለኮት ከስጋ ተዋህዶ ሥግው ቃል ሆነ የሚለው ርቱዕ እምነት መሆኑን መሰከሩ፡፡ ይህ ቃል የእምነት ዶክትሪን መገለጫ ሆኖ ነው የኖረው ፡፡ በኬልቄዶን ጉባኤ በኋላም ይህ ስያሜ የኦርቶዶክሶቹ ዋና መጠሪያ እየሆነ መጣ፡፡ በኢትዮጵያ ጥንታዊ መጻሕፍት ላይ ተዋህዶ እምነት ሆኖ እንጂ የቤተክርስቲያ መጠሪያ ሆኖ አናገኝውም ‹ኦርቶዶክሳዊ› የሚለው ቃል የምናገኝውን ያህል  ‹ተዋህዶ› የሚል መገለጫ አናገኝም ተዋሕዶ የሚለው ቃል በነገረ ሥጋዌ ትምህርት ላይ በሀገር ውስጥ የተነሳ የተለየ አስተያየት ስላልነበረ መጠሪያነቱ አልጎላም፡፡

በ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ከአውሮፓ በመጡ ካቶሊካውያን ምክንያት የተፈጠረውን የእምነት ክፍፍል ተከትሎ ይህ የእምት መጠሪያ የአማያንና የወገን መጠሪያ እየሆነ መጣ፡፡ በ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ቅባትና ጸጋ የሚባሉ ባሕሎች መጥተው ነበር፡፡ እነዚህን ባሕሎች የሚቃወሙትና ኢየሱስ ክርስስ መለኮት ከስጋ በተዋሕዶ ሥግው ቃል እንጂ እንደ ነገስታትና ነቢያት በመቀባት አይደለም ያሉት ደግሞ መጠሪያቸው ከእምነታቸው ተወስዶ “ተዋሕዶዎች” ተባሉ፡፡ ከቦሩ ሜዳ ጉባኤ በኋላም የቤተክርስቲያኒቱ ሕጋዊ ስም ‹‹ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ›› የሚለው ጎላ፡፡

ኦርቶዶክስ የሚለው ስም  ቤተክርስቲያኒቱ በዓለም የምትታወቅበት የወገን ስሟ ነው፡፡ ሌሎችም ‹የግብጽ ኦርቶዶክስ› ፤ ‹ የሕንድ ኦርቶዶክስ› ብለው ይጠሩ እና ከአካባቢያቸው ራሳቸውን ለመለየት ደግሞ ‹የግብጽ ኮፕት ኦርቶዶክስ› ፤ ‹የሶርያ ያዕቆባዊት ኦርቶዶክስ› እያሉ ይጠራሉ፡፡ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያንም  ‹ኦርዶክስ ተዋሕዶ› ትባላለች ፡፡

አንዳንድ ሰዎች በዘመናውያን መዛግብት ቃላት ስለ ‹ኦርቶዶክስ› የተሰጡ ፍቺዎችን ይዘው ይሞግታሉ፡፡ ኦርቶዶክስን ‹ከአክራሪነትና ከለውጥ አለመቀበል› ጋር እያዛመዱ ይፈቱታል፡፡ በዚህ ምክንያት ኦርቶዶክስ የሚለው ቃል ለኮንሰርቫቲቭ ፓርቲዎችና ለአይሁድ ሲሰጡት ይታያሉ፡፡ ይህ ግን ኦርቶዶክስ የሚለው ስም ከመነጨበት ጠባይ በእጅጉ የራቀ ነው፡፡

አሁን ወደ ሁለተኛ ነጥብ እንመለስና ሰንደቅ አላማን እንመልከት፡፡ የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ የኢትዮጵያውያን መለያ ናት፡፡ ለዚች ሰንደቅ አላማ  ብዙዎች ውድ ሕይወታቸውን  ከፍለዋል፡፡ ከእነዚህ ውድ ሕይወታቸውን ከከፈሉ መካከልም የቤተክርስቲያኒቱ አባቶችና ልጆች ይገኙበታል፡፡ ቤተክርስቲያኒቱ ታሪክን ከማቆየት ፤ ባሕልን ከማሻገርና ኢትዮጵያዊነትን ከማስረጽ ሚናዋ አንጻር ሰንደቅ አላማንም  በማስከበርና ለትውልድ በማስተላለፍ የበኩሏን ድርሻ ተወጥታለች፡፡

የኢትዮጵያ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ  ሰንደቅ አላማ ከሀገራዊ እሴትነቱ ፤ መስዕዋትነትና ነጻነት ከማንጸባረቁም ፤ ለኢትዮጵያውያን ከደማቸው ጋር የተዋህዶ ልዩ ምልክት ከመሆን አልፎ ግን ጽድቅና ኩነኔ ውስጥ የሚገባ ፤ እርሱን ያልተቀበለ እና ያላደረገ ሰማያዊ ዋጋ የሚቀርበት ፤ ከእርሱ ውጪ ቀለም ያለው ነገር የለበሰና ማህተብ ያሰረ ሃጥያት እንደሰራ ተቆጥሮ ንስሃ የሚገባበት ግን አይደለም፡፡ ከኢትዮጵያ ውጪ ያለ ዜጋ የቤተክርስቲያኒቱ አባል ለመሆን የቤተክርስቲያቱን ዶግማ እና ቀኖና መቀበልን እንጂ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ባንዲራን መቀበል ግዴታው አይደለም፡፡ በኡጋንዳ ባንዲራ ፤ በአሜሪካ ባንዲራ ፤ በሶማሊያ ባንዲራ አሸብርቆም ቢሆን የኦርዶክስ ተዋሕዶ ልጅ መሆን ይችላል፡፡ አስከ አሁን በቀኖና በሚደነገጉ መጻህፍቶች ውስጥ ሰንደቅ አላማን የተመለከተ ቀኖና የለንም፡፡ 

በመሆኑም ሰንደቅ አላማችን ከኢትዮጵያዊነታችን ጋር እንጂ ከኦርቶዶክስ  እምነታችን ጋር  የታሪክ እንጂ የድኅነት ተዛምዶ የለውም፡፡

እንደዚህ አይነት አመለካከቶች የሚያይሉት እንዲሁ አይደለም፡፡ በሕዝቡ ዘንድ ኢትዮጵያዊ ስሜት  ደብዝዟል ፤ ለሰንደቅ አላማና ለሀገራ እሴቶች የሚሰጠው ዋጋ ቀንሷል ተብሎ ሲታሰብ ሰንደቅ አላማን የመሰሉ ሀገራዊ እሴቶች ጉልበት ያገኙ ዘንድ ተጨማሪ ሃይማኖታዊ ኃይል ይሰጣቸዋል፡፡ ቤተክርስቲያቱ የሰንደቅ አላማን ክብርና ትርጉም ማስተማርዋ እና በትውልድ ውስጥ ማስረጿ ባልከፋ ፡፡ አስተምህሮ ግን ከሀገራዊ ግዴታ የሚመጣ እንጂ ከሃይማኖታዊ ግዴታ የሚመጣ መሆን የለበትም፡፡ ከሕዝብ እሴቶች እንደ አንዱ ሆኖ እንጂ ከጽድቅና ኩነኔ ጋር መሆን ለበትም፡፡

ምን ይደረግ ?
የሃይማኖት ትምህርት በሚገባ መሰጠት ሲያቆምና ሰዎችም በተደላደለው እምነት መንገድ ላይ በእውቀትና በእምነት እየተመሩ መጓዝ ሳይችሉ ሲቀሩ ‹ባለ ተስፋዎች ይሆናሉ› ቅዱስ ጳውሎስ ለኤፌሶን ሰዎች በላከው መልዕክቱ መጀመሪያ ላይ ‹በኤፌሶን ላሉት ቅዱሳን ፤ በክርስቶስ ኢየሱስ ባሉት ምዕመናን›  በማለት የገለጠው አባባል ታላቅ ነገር አለው፡፡ ምእመናኑ በሁለት ዓለም መኖራቸውን እንዳይረሱ ለማድረግ ነው፡፡ ‹በክርስቶስና በኤፌሶን› ክርስቲያችም ምድራዊነታቸውንም ሰማያዊነታቸውንም  መርሳት የለባቸውም፡፡ አንዳንድ ጊዜ ግን ምድራዊ ጎዳና ሲያቅተንና ፈተና ሲበዛበት ፤ የኢኮኖሚ የፖለቲካ ሁኔታ አልቃና ሲል ፤ የምናየው የምንሰማው ተስፋ ሲያሳጣን ፤ ምድር ላይ መሆናችንን ፈጽመን ረስተን ኅሊናችን ወደሚፈጥረው ልዩ አለም እንገባለን፡፡ ያንንም እጅግ ከመመኝታችን የተነሳ የደረስንበት ይመስለናል፡፡

በዚህ ጊዜ የሚሰጡ ትምህርቶች ለሰዎች ቀላል የሆኑ ፤ ንባብና ትምህርትን የማይጠይቁ ፤ በቀላሉ የሚተገበሩ ፤ የሚነኩና የሚዳሰሱ ይሆናሉ፡፡ ቡና መጠጣት አለመጠጣት ፤ አረንጓዴ ቢጫ ክር ማሰር አለማሰር ፤ በባዶ እግር መሄድ አለመሄድ ፤ ጸጉርን ማስረዘም አለማስረዘም ፤ መቁጠሪያ አለስርዓቱ ማሰር አለማሰር ፤ ከመምህራን ቃል ይልቅ የሰይጣንን ቃል መቀበልና ማመን እየሰለጡ ይመጣሉ፡፡
ለዚህ ትልቁ መፍትሔው የእምነት ተቋማት የራሳቸውን ሥራ (ወንጌል ማስተማር) ትተው በሰዎች ስራ ውስጥ መግባታቸው ነው፡፡ ስለዚህ ተቋማቱ መጀመሪያ ራሳቸውን ወደ ተልዕኳው መልሰው ፤ የማይጨበጥ ተስፋ የሚዋልለውን ሕዝብንም ወደ ትክክለኛ ኑሮ እና ተስፋ መመለስ አለባቸው፡፡  እዚህ ኤልያስ ነኝ ፤ እዚያ ድንግል ማርያም ነኝ ፤ እዚያ አቡዬ ነኝ የሚሉ በተነሱ ቁጥር ሕዝቡ ስራና ትዳር ፈትቶ ተንከራቶ አይዘልቀውም፡፡ ይህ አዲስ እንቅስቃሴ ለምእመናኑ የተለየ ፋይዳ ይዞ አልመጣም፡፡

ይህ አስተያየት ሰዎቹ ከሚያራምዱት አስተምህሮ ከብዙ በጣም ጥቂቱ ብቻ እንደሆነ ለመግለጽ እንወዳለን፡፡  የእነዚህን ቡድኖች አስተምህሮ እዚህ ጽሁፍ ላይ በርካታ ያልተዳሰሱ ነጥቦችን በማካተት ወደፊት ይዘን የምንቀርብ መሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡ እኛ መረጃዎችን በጊዜያቸው ምዕመናን ዘንድ በማድረስ ሃላፊነታችንን ተወጥናል እርስዎም ባሉበት ራስዎን ቤተሰብዎን እና ቤተክርስቲያንን ከዚህ እንቅስቃሴ ይጠብቁ፡፡

ቸር ሰንብቱ

39 comments:

  1. This website gives a clear discussion on the issue as well as Dn. Daniel's argument:

    ethkogserv.org

    ReplyDelete
    Replies
    1. ይህ የተጠቀሰ ብሎግ ምንን ያስተምራል? ዓላማውና መዳረሻውስ ምንድር ነው ? ሰንደቅ ዓላማችንን እግዚአብሔር ነው የሰጠን በማለት "The Testimonial of the Ethiopians on the Holy Covenant in Ethiopic”፤ ርዕስ ሥር ጽፈዋል ፡፡ ለአለቃ አያሌው በጻፉት መልስ ላይ ደግሞ ድንግል ማርያም ማለት ኢትዮጵያ ፣ ኢትዮጵያ ሲባልም ድንግል ማርያም ናት እንጅ አገር አይደለችም የሚል ትምህርት አላቸው ፡፡ ይኸ ከቤተ ክርስቲያናችን ትምህርት ጋር እንደምን ይዛመዳል ፤ ወይንስ የተለየ አዲስ መጥ ትምህርትና ሃይማኖት ነው ? ለንባብ ተጋብዤም የተሰጠኝ አድራሻ ስለነበረና ዛሬ ከዚህ ተለጥፎ ሳየው ፣ የምታውቁ እንድታብራሩልን ስለፈለግሁ ነው ፡፡ ጐበዝ የምንጠበቅበት አበዛዙ!

      በሚከተለው አድራሻ የቀረበውንም ጽሁፍ ቃኙትና የምትሉንን አቅርቡልን
      "http://www.ethkogserv.org/messages/Lelaw%20Msrach/Lelaw%20M'ss'rach!%20Leh'wa%20seledach'n%20Mel'ikt!.pdf"

      Delete
    2. gobez egzeabher tinatun yesten lela men yebalal

      Delete
  2. hiyente abewuki teweldu leki dikik ... Dani e/her yibarikih be-ewunetu bezihwuzinbir libu yetekefelewun yewah miemen bjigu tadigehal tebarek.

    ReplyDelete
  3. ሰላም ጤና ይስጥልኝ አምላክ እግዚአብሔር ለዛሬ ቀን ስላደረሰን የተመሰገነ ይሁን። እስካሁን ከጋዜጣው ላይ እንዳነበብኩት ከአንድ ነጥብ በቀር ወይዘሮ አቦነሽ ያቀረበችው መሠረታዊ የልዩነት ምክንያት የለም። ኦርቶዶክስ የሚለው ቃል የግሪክ መሆኑ እነ ወይዘሮ አቦነሽን ምቾት ካልሰጣቸው ርቱእ ብለው ሊጠሩት ይችላሉ። መሠረታዊው ነጥብ ጸጋ፣ ቅባት ወዘተ የሚባሉት በቤተክርስቲያን ተቀባይነት የሌላቸው እምነቶች መሆናቸው ነው። እንደዚህ አይነት ጥቃቅን ምክንያት በመፍጠር ቤተ ክርስቲያንን ማወክ ተገቢ አይመስለኝም። ከወይዘሮ አቦነሽ የጋዜጣ ቃለ ምልልስ ያገኘሁት አንድ ልዩነት ቢኖር ኤጲስ ቆጵስ የሚሆነው ካህን ያገባ መሆን አለበት የሚለው አስተያየቷ ነው። ይህ ከፕሮቴስታንቶች ጋር የሚያመሳስል አስተያየት ነውና ወዲያውኑ ሊወቀስ ይገባል። እኔ እንደሚመስለኝ ለዚህ አይነቱ ጉዳይ መልስ መስጠት ያለበት በተዋህዶ ተአማኒነት ያለው ካህን የሆነ የቤተ ክርስቲያን ሊቅ ነው። ዲያቆን ዳንኤል የሰጠው መልስ አጥጋቢ አይደለም። በተለይ በኢየሩሳሌም ሃሳዊ መሲህ ገና አልነገሰም በማለት የሰጠው ትንታኔ አለማዊ (ሴኪዩላር) ብቻ ሳይሆን አሜሪካ ያሉ የፕሮቴስታንት ፓስተሮች የሚሰጡት አስተያየት ቅጂ ነው። ይህን በተመለከተ ወይዘሮ አቦነሽ የተናገረችው የተሻለ አስተያየት ነው። ሃሳዊ መሲህ በኢየሩሳሌም ነግሷል። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተሰቀለባት ምድር አሁን በመምራት ላይ ያለው የአስቆሮቱ ይሁዳ፣ ሊቀ ካህናቱም ቀያፋ አይደለም ወይ? በሃያላን መንግሥታት መሪነት ዓለም በሙሉ በአሁኑ ሰዓት “እስራኤል፣ እስራኤል” እያለ የሚጠራው ጸረ ክርስቶሱን ይሁዳን አይደለም ወይ? እስራኤል ማለት የተሰቀለው ክርስቶስ ነው ወይስ ሰቃዩ ከያፋ? ክርስቶስ በሥጋ ወደዚች ዓለም መጥቶ፣ ለኛ ሲል ተሰቅሎ፣ ሞትን ድል አድርጎ ተነስቶ፣ ሞትን ከኛ ወስዶ ህይወቱን ለኛ አልሰጠንም ወይ? ክርስቶስ ከፈሪሳውያን ስሙን ወስዶ ስሙን ለኛ ለክርስቲያኖች አልሰጠንም ወይ? እስራኤል ማለት ክርስቲያን እንደሆነ አናውቅም ወይ? ክርስትና ማለት ተዋህዶ አይደለም ወይ? ታዲያ እስራኤል ማለት ተዋህዶ አይደለም ወይ? ርትእ የሆነች የአንዲት ኃይማኖት የተዋህዶ ክርስትና አማኝ ሆኖ ይሁዳን “እስራኤል” ብሎ የሚጠራ ክርስቶስን አልካደውም ወይ?

    ታዲያ በሥጋዊ አካል ወደ አገራችን ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ኃይማነቷን እና አንድነቷን የበታተኑ እነማን ናቸው? ኤርትራ ከኢትዮጵያ ስትገነጠል ተዋህዶ አልተከፈለችም ወይ? ሃያ አራት ሰዓት እግዚአብሄር በሚመሰገንባት ኢትዮጵያ፣ ከጥንት ጀምሮ በየቤቱ፣ በየመንደሩ፣ በየደብሩ፣ በየተማሪ ቤቱ፣ በየቀኑ፣ በየአመቱ፣ ከደቂቅ እስከ ልሂቅ፣ ከህጻን እስከ አዛውንት፣ ከቤት ልጅ እስከ ንጉሥ ድረስ በአንድ ላይ በተመስጦና በዝማሬ እግዚአብሔር እየተመሰገነ በነገሠባት ኢትዮጵያ፤ አፈሯ ተቆፍሮ የዝንጀሮ አጽም ከአፈሯ ተፈልጎ “የሰው ልጅ የመጣው ከጦጣ እንጂ እግዚአብሔር አልፈጠረውም” እየተባለ ፈጣሪ እግዚአብሔር እየተሰደበ በዓለም ዙሪያ አዋጅ አልተነገረም ወይ? እነዚህን የመከፋፈልና የማርከስ ግፎች ለመፈጸም የአስቆሮቱ ይሁዳ፣ የምእራቡ ሉተር እና የዓረቡ መሀመድ ተባብረው በአንድ ላይ ወደ ኢትዮጵያ አልመጡም ወይ? አልፈጸሙም ወይ? ታዲያ እስራኤል ተዋህዶ ናት ወይንስ ፈሪሳዊነት?

    ምነው እናስተውል እንጂ።
    እግዚአብሔር ኃይምኖታችን ይጠብቅ።
    ኃይለሚካኤል።

    ReplyDelete
    Replies
    1. ኃይለሚካኤል እውን እንዳልከው “መጽሐፍ ቅዱስ የሚለው ሃሳዊ መሲህ በኢየሩሳሌም ነግሷልን?”

      የዛሬ ሁለት ሺህ ዓመት ገደማ ወንጌላዊው ዮሐንስ “ልጆች ሆይ፥ መጨረሻው ሰዓት ነው፥ የክርስቶስም ተቃዋሚ ይመጣ ዘንድ እንደ ሰማችሁ አሁን እንኳ ብዙዎች የክርስቶስ ተቃዋሚዎች ተነሥተዋል፤ ስለዚህም መጨረሻው ሰዓት እንደ ሆነ እናውቃለን። ክርስቶስ አይደለም ብሎ ኢየሱስን ከሚክድ በቀር ውሸተኛው ማን ነው? አብንና ወልድን የሚክድ ይህ የክርስቶስ ተቃዋሚ ነው።” 1 ዮሐ 2፡18፡22 ፤ “ኢየሱስ ክርስቶስም በሥጋ እንደ መጣ የማይታመን መንፈስ ሁሉ ከእግዚአብሔር አይደለም፤ ይህም የክርስቶስ ተቃዋሚው መንፈስ ነው፤ ይህም እንዲመጣ ሰምታችኋል፥ አሁንም እንኳ በዓለም አለ።” 1 ዮሐ 4፡3 ፤ እንዲሁም “ብዙ አሳቾች ወደ ዓለም ገብተዋልና እነርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ እንደ መጣ የማያምኑ ናቸው፤ ይህ አሳቹና የክርስቶስ ተቃዋሚው ነው።” 2 ዮሐ 1፡7 ፤ በማለት የሐሰተኛው ክርስቶስን ማንነትንና መንፈሱ ምንን እንደሚያስከትል ገልጿል ፡፡

      ሰዓቱንና ጊዜውን ለማመልከትም “ከምልክቶች መሃከልም ፣ ጦርንም የጦርንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠበቁ፥ አትደንግጡ፤ ዳሩ ግን መጨረሻው ገና ነው። ለአሕዛብም ሁሉ ምስክር እንዲሆን ይህ የመንግሥት ወንጌል በዓለም ሁሉ ይሰበካል፥ በዚያን ጊዜም መጨረሻው ይመጣል። ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ ፣ ዘመኑም ቀርቦአል እያሉ በስሜ ይመጣሉና ፣ ብዙዎችንም ያስታሉ ፡፡ በነቢዩ በዳንኤል የተባለውን የጥፋትን ርኩሰት በተቀደሰችው ስፍራ ቆሞ ስታዩ፥ አንባቢው ያስተውል፥” ማቴ 24፡6፡14-15 ፤ ፣ ማር 13፡6-7፡14 ፣ ሉቃ 21፡8-9 ፤ ዳን 9፡24-27 ፣ 11፡31 ፣ 12፡1ዐ-12 ፡፡ ታድያ ዛሬ ክርስቶስ ነኝ በማለት የተነሳ ግለሰብ ኖሮና ተከታይ አፍርቶ ይሆንን?

      በመጨረሻው ሰዓት ክርስቶስ ነኝ ባይ ቢመጣብን እንኳን ደግሞ ፣ “በዚያን ጊዜም ማንም። እነሆ፥ ክርስቶስ ከዚህ አለ፥ ወይም። እነሆ፥ ከዚያ አለ ቢላችሁ አትመኑ፤ ሐሰተኞች ክርስቶሶችና ሐሰተኞች ነቢያት ይነሣሉና፥ ቢቻላቸውስ የተመረጡትን እንኳ ያስቱ ዘንድ ምልክትና ድንቅ ያደርጋሉ። በዚያን ወራት ግን ከዚያ መከራ በኋላ ፀሐይ ይጨልማል ጨረቃም ብርሃንዋን አትሰጥም፥ ከዋክብትም ከሰማይ ይወድቃሉ፥ የሰማያትም ኃይላት ይናወጣሉ። በዚያን ጊዜም የሰው ልጅ በብዙ ኃይልና ክብር በደመና ሲመጣ ያዩታል።” ማር 13፡21-25 ፤ በማለት መጠበቅ እንደሚገባን ተጽፏል ፡፡ ምልክቱም በአንድ አገርና መንደር ብቻ ሳይሆን የሚገለጸውና የሚታወቀው በጠቅላላ የዓለም ህዝብ የፀሃይ ነጸብራቅ እንደሚታይ በደመና ሲመጣ ይሆናል ፡፡

      እንዲያውም “በመጨረሻው ዘመን እንደ ራሳቸው ምኞት የሚመላለሱ ዘባቾች በመዘበት እንዲመጡ ይህን በፊት እወቁ”፤ 2 ጴጥ 3፡3 ፤ ይሁዳ 1፡18 ፤ ያለው ይፈጸም ዘንድ ዛሬ ወንጌልን እየቀነጨቡ የሚተረጉሙት በዝተዋልና በፈተና ላለመሳሳት መጠንቀቁ ይጠቅማል ፡፡ ጌታ ለመንገር ያልፈቀደውን ዕለትና ሰዓት ፣ ዛሬ መጨረሻው ነው የሚሉ ብዙ ወገኖች አሉ ፡፡

      ጳውሎስ የጊዜው ሰዎች በዚህ ዓይነት ትምህርት እየታወኩ ቢያስቸግሩት “ነገር ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ስለ ጌታችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ መምጣትና ወደ እርሱ ስለ መሰብሰባችን፥ በመንፈስ ወይም በቃል ወይም ከእኛ እንደሚመጣ በመልእክት። የጌታ ቀን ደርሶአል ብላችሁ፥ ከአእምሮአችሁ ቶሎ እንዳትናወጡ እንዳትደነግጡም እንለምናችኋለን። ማንም በማናቸውም መንገድ አያስታችሁ፤ ክህደቱ አስቀድሞ ሳይመጣና የዓመፅ ሰው እርሱም የጥፋት ልጅ ሳይገለጥ፥ አይደርስምና። እኔ እግዚአብሔር ነኝ ብሎ አዋጅ እየነገረ በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እስኪቀመጥ ድረስ፥ አምላክ ከተባለው ሁሉ፥ ሰዎችም ከሚያመልኩት ሁሉ በላይ ራሱን ከፍ ከፍ የሚያደርገው ተቃዋሚ እርሱ ነው።” 2 ተሰ 2፡1-4 ፤ በማለት ለዘመኑ ሰዎች ያስተማረው ዛሬም በትርጉም እንዳንሳሳት ይጠቅማል ፡፡ ታድያ ማንኛው ነው እግዚአብሔር ነኝ ፣ ክርስቶስ ነኝ ብሎ የተነሳና በእግዚአብሔር መቅደስ የተቀመጠና መጨረሻው ነው ለማለት የምንደፍረው ?

      በመጨረሻም “ይድኑ ዘንድ የእውነትን ፍቅር ስላልተቀበሉ ለሚጠፉ፥ የእርሱ (የሐሰተኛው ክርስቶስ ማለት) መምጣት በተአምራት ሁሉና በምልክቶች በሐሰተኞች ድንቆችም በዓመፅም መታለል ሁሉ እንደ ሰይጣን አሠራር ነው።” 2 ተሰ 2፡9-1ዐ በማለት ሐሳዊው መሲህ ሲመጣ ፣ ተከታይ ለማፍራት ክርስቶስ ነው ለማለት የሚያበቃውንና የሚፈጽማቸውን አያሌ ድንቃ ድንቅ ምልክቶች ገልጿቸዋል ፡፡

      ሰፊውን የመጨረሻ ዘመን ምልክቶች ንባብ በሚከተሉት ምዕራፍ መመልከት ይቻላል
      1. ማቴዎስ 24 ፤
      2. ማርቆስ 13 ፤
      3. ሉቃስ 21 ፤
      4. 2 ጢሞቴዎስ 3

      እግዚአብሔር ኃይምኖታችንንና ቤተ ክርስቲያናችንን ይጠብቅልን። አሜን

      Delete
    2. ebakihin atizelabid wendim Hailemichael. Antem dekike elias nen endemilut gira gebtohal. Ethiopiawinet ayadinim menfesawinet enji. yesafkew enkuan lenga lantem yegebah aymeslenigim.

      Delete
    3. ለAnonymous March 19, 2013 at 8:46 PM
      የተጻፈው የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ነው ፡፡ ከሌላ ላለመሆኑ ማስረጃው ደግሞ የተገኘበት ምዕራፍና ቁጥር መጠቀሱ ነው ፡፡ ቅዱስ ቃሉ እንደምትለው ምንም ስላልተጨመረበት አይዘላብድም ፤ ለማያያዝ ተሞክሯል ፤ ማብራሪያ ቢገኝ በማለት ጥያቄ ቀርቧል ፡፡ የሚለውንና የተጻፈውን ያለመረዳት ድክመት ያለ ይመስለኛል ፡፡ በቀረበው ወንጌል ቃል ውስጥ ኢትዮጵያዊነት አልተሰበከም ፤ ኢትዮጵያዊነት ያድናልም አልተባለም ፡፡ መልዕክቱ ጠቅለል ቢደረግ ሐሳዊ መሲህ የሚባለው እኔ እግዚአብሔር ነኝ ወይም ክርስቶስ ነኝ ብሎ ስም ይዞ የሚመጣ ነው ፤ እንዲታመንም ተአምር ያደርጋል ፡፡ ከዛ ውጭ ያካባቢ ገጠመኞችንና ሁናቴዎችን ያለአግባብ እየተረጐሙ አይሳቱ ለማለት ሞክሯል ፡፡ ልጅዋን በፍቅር ቆንጥጣ ያላሰደገች እናት ፣ ቢገላምጣት መጽሐፍ በመጨረሻው ዘመን ልጆች በወላጆቻቸው ላይ ይላልና ብላ የዘመን ፍጻሜን ብትጠቅስ ውሸት ነው ለማለት ተፈልጐ ነው ፡፡ የተሻለ የተረዳኸው ወይም የምታነሳው ጥያቄ ካለ በሥርዓቱ አስረዳኝ ፤ ከጥያቄም ሆነ ከመግለጫህ ለመማር ዝግጁ ነኝ ፡፡ በተረፈ እንዲህ የዘመን መቋጫ ነው እያሉ እያስፈራሩ ደግሞ ህዝብን እንዳይነዱ የምታውቁትንና የተገነዘባችሁትን ለመታደግ አካፍሉ ፡፡

      Delete
    4. Anonymous March 19, 2013 at 8:46 PM

      Yihn bilgnahn Ethiopiawinet yadinal menfesawinet ayadinim laleh sew bitwosdilet ayishalm?

      Delete
    5. ሰላም ጤና ይስጥልኝ ከላይ ያለውን ጽሁፍ ለጻፉ “ም””።

      እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን።

      በመጀመሪያ ግልጽ ለማድረግ የምፈልገው እኔ የወንጌል አስተማሪ አይደለሁም። ቅዱስ መጽሐፍ እና በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የሊቃውንት ትርጓሜ ከሚያሳየው መስመር ጋር አብሮ የማይሄድ ሌላ ትርጉም ተሰጥቶ ሳይ ይህማ እንዴት ልክ ሊሆን ይችላል ብየ እጠይቃለሁ። በተዋህዶ እምነት መሠረት በመጽሐፍ ቅዱስ እና በትርጓሜ ባገኜኋቸው ግንዛቤዎችና መድኃኒዓለምም በመራኝ መሠረት እውነት የመሰለኝን እውነት ነው እላለሁ። እውነት ካልመሰለኝ ደግሞ እውነት አይደለም ብየ እናገራለሁ። ስለዚህ አቀራረቤ እኔ አውቃለሁ ከሚል አይደለም።

      ወንድሜ የጠቀሷቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች በሙሉ የሚጠቁሙት የመጨረሻው ዘመን ላይ እንደደረስን ነው። እኔ እንደሚገባኝ ከሆነ መንፈሳዊ ትርጉማቸውን እርስዎ የተረዱት አልመሰለኝም። ያነሷቸውን ነጥቦች እስኪ በቅርበት እንያቸው።

      ወንጌል ቅዱስ ዘዜነው የወንጌል አንድምታ እንደሚያስረዳው እስመ ይተንስኡ ሐሳዊያነ መሢሕ - ሃሰተኛ ክርስቶስ ማለትም በጨመረሻ ጊዜ የሚመጡ መሢሕ ክርስቶስን የሚያሳብሉ፣ በመሢሕ በክርስቶስ የሚያብሉ ሐሰተኞች መምህራን ይነሳሉ። ማለትም እኛ የምንነግራችሁን ወንጌል ተከተሉ እያሉ ህዝበ እስራኤልን ከሃይማኖት የሚያስወጡ ይመጣሉ ማለት ነው። እንዳይዘነጉ ህዝበ እስራኤል ማለት ክርስቲያን ማለት እንጂ አይሁድ ማለት አይደለም። ትርጓሜው መጽሓፍ በዚህን ጊዜ ብዙ ስዎች በነዚህ በሐሳዊያነ መሢሕ ተመርተው ኃይማኖታቸውን ይቀይራሉ ይላል። ወንጌል ቅዱስ ዘዜነው ወንጌል ዘማቴዎስ ምዕራፍ ፳፬

      እንደገናም “ክርስቶስ ነኝ በማለት የተነሳ ግለሰብ ኖሮና ተከታይ ይሆንን” ላሉት ቅዱስ ወንጌል ትርጓሜ አርስዎ በጥሬው እንዳሰቡት አይተረጉመውም። ትርጓሜ መጽሐፍ የጥጦስን ጣኦት ስታዩ የአይሁድ ጥፋት ይሆናል ይላል። ወንጌል ዘማቴዎስ ምዕራፍ ፳፬ ቁ ፲፭ ። የጥጦስን ጣኦት ማለት ሮማዉያን (ቅዱስ ጴጥሮስ ባቢሎን ብሎታል) በእጅ ሥራቸው እየተመኩ ወይም በዘመናዊ አነጋገር “ሳይንሳቸውን እያመለኩ” የክርስቶስን እምነት በረገጡበት ዘመን ማለት ነው። በመጨረሻው ዘመን ዓለምን የሚቆጣጠረው፣ ቅዱሳንን የሚረግጠው ኃይለኛው መንግሥት ከግሪክ የሚጀምረው የምእራባውያን የበላይነት ዘመን እንደሆነ ነቢዩ ዳንኤል በትንቢቱ ተናግሯል። ትንቢተ ዳንኤል ምዕራፍ ፰ ከቁጥር ፭ እስከ መጨረሻ።

      እንዲያውም ትርጓሜ መጽሓፉ የሮም (የባቢሎን ወይም የምእራቡ ዓለም) ጉልበት ከጥፋት በፊት ለአይሁድ እንደ አበባ ያለመልማቸዋል ይላል። ይህም ማለት አይሁድ ባቢሎንን እንደመከታ ይጠቀማሉ ማለት ነው። እንግዲህ ይመልከቱ አይሁድ ነን የሚሉትን ከአውሮፓ ሰብስበው የዛሬ ፷፭ አመት ክርስቶስ በተሰቀለባት ቦታ በማስፈር ክርስቶስን እና እናቱን ብጽእት ቅድስት ድንግል ማርያምን የሚሳደቡትን እነዚህን አይሁድ ነን ባዮች “እስራኤል እስራኤል” ሲሏቸው ለነሱ ሲባልም ክርስትናን እንዴት እንደሚያጠፉ ይመልከቱ። በደንብ ላይታይዎት ከቻለ ትንሽ ምሳሌ ልስጥዎት። በምእራባውያን አስተባባሪነት በዙ ሺህ የሚቆጠሩ ፈላሻ ሙራ ብለው የሚጠሯቸውን ክርስቲያኖች ክርስቶስን አስክደው ከኢትዮጵያ አስወጥተው ወስደዋል። ይህ አንድ ምሳሌ ነው። ሌላ ብዙ ብዙ ግፍ በክርስትና ላይ ተፈጽሟል። ቦታ ለመቆጠብ ሌላ ጊዜ እሱን እንነጋገራለን።

      ስለዚህ ወዳጄ በትርጓሜው መሠረት የጥፋት ርኩሰት ማለት በእግዚአብሔር ፋንታ የሰው የእጅ ሥራና ፍልስፍና ሲመለክ ማለት ነው። ለምሳሌ በአሁኑ ሰዓት በምእራቡ ዓለም አስፋፊነት የበላይነትን ይዞ የሚገኘው የምእራቡ ኦሪት ዘፍጥረት እሱም የጢጦስ ጣኦት ኢቮሉሽን ነው። ተግባባን ወዳጄ?

      እንዳይበዛ እዚህ ላይ ላቁምና ካስፈለገ እቀጥላለሁ።
      እግዚአብሔር አምላክ ክርስትና ኃይማኖታችን ርትእት ተዋህዶን ይጠብቅልን።

      ኃይለሚካኤል።

      Delete
    6. እኔም ወንድም ኃይለሚካኤልን ሰላም ጤና ይስጥልኝ እላለሁ ፡፡
      “በመጀመሪያ ግልጽ ለማድረግ የምፈልገው እኔ የወንጌል አስተማሪ አይደለሁም።” እንዲያ ሲሆን ደግሞ ሁለታችንም የአንድ ባቡር ተሳፋሪዎች ነንና ከጠቀሱትን የአንደምታ መጽሐፍ በድጋሚ እንዲመለከቱት ጥቂት ቆነጣጥሬ አስፍሬአለሁ ፡፡

      እስመ ብዙኃን ይመጽኡ በስምየ እንዘ ይብሉ አነ ውእቱ ክርስቶስ ቁጥር 5 (በዚህ ወቅት አንድም በኢየሱስ ስም የመጣና ክርስቶስ ነኝ በማለት ተከታይ ያፈራ ሐሳዊ መሲህ የለም ፤ አለ የሚሉኝ ከሆነ አገርና ምድሩን ትምህርቱንና ተአምራቱንም ጨምረው ይግለጹልን)

      ሕዝበ ሮም (ከአራዳሚስ ጋራ የሄዱ የአርዳሚስ ወገኖች ይላቸዋል) በሕዝበ እሥራኤል ላይ በጸላትነት ይነሡባቸዋል ፡፡ አንድም ወይትነሥኡ ሕዝብ ብስሀ መልስ ሕዝበ እሥራኤል በሕዝበ እሥራኤል ላይ ነገሥተ እሥራኤል በነገሥተ እሥራኤል ላይ በጸላትነት ይነሡባቸዋል ፡፡
      ሐተታ ቀን ከጥጦስ ሠራዊት ጋራ ሲዋጉ ይውላሉ ፡፡ ማታ ከኔ ወገን አነግሥ ከኔ ወገን አነግሥ እያሉ .... አንዱ ባንዱ ሾተል እየሸጐጠበት ይሄዳል ፡፡ቁጥር 7 (ሮም የዘመኑ ኃያል መንግሥት ስለነበረች ብንልና ከዚህኛው ዘመን ኃያል ጋር ብናያይዘው አሜሪካና እሥራኤል ሰምና ወርቅ እንጅ ጸላትነት የለባቸውም ፡፡ አንዱ ለአንዱ ሊሞት ቃል የተገባባ ሆኖ ነው የምናገኘው ፡፡)

      ወይእተ አሚረ የዓልው ብዙኃን ሃይማኖቶሙ ፡፡ በዚያን ጊዜ ብዙ ሰዎች ሃይማኖታቸውን ይለውጣሉ ፡፡ ወይጸልዑ በበይናቲሆሙ ፡፡ እርስ በርሳቸው ይጣላሉ ፡፡ ወያገብኡ ቢጾሙ ለሞት ይትቃተሉ ፡፡ አንዱ አንዱን ይጸላዋል ፡፡ ቁጥር 1ዐ (ከዚህ ቃል ያያዙትን ምሳሌ መጨረሻው ላይ ገልጫለሁ ፡፡)
      ወብዙኃን ሐሳውያን ነቢያት ይመጽኡ ፡፡ በመምህራን የሚያብሉ ፣ መምህራንን የሚያሳብሉ ሐሰተኞች መምህራን ይነሣሉ ፡፡ ወያስትዎሙ ለብዙኃን ፡፡ ብዙ ሰዎችን ያስቷቸዋል ፡፡ ቁጥር 11

      ቁጥር 14 ወይሰበከ ዝ ወንጌለ መንግሥት ውስተ ኲሉ ዓለም ፡፡ የመንግሥት ወንጌል ማለት ጌትነቱን የምትናገር ወንጌል በአራቱ ማዕዘን ትነገራለች በእስላም ቤት ስንኳ ሳይቀር ትገኛለች ፡፡ ታሪክ በሀገራችን ቴዎድሮስ በሀገራቸው ዮሐንስ የሚባል ይነግሣል ፡፡ የኛም ሄዶ ያም መጥቶ በእስክንድርያ ሦስት ቀን ይዋጋሉ ፡፡ አራቱ ሊቃነ ጳጳሳት የክርስቲያን ደም ለምን ይፈሳል መሥዋዕት ሠውተን በመሥዋዕቱ ምልክት በታየለት ሃይማኖት ይጽና ይሏቸዋል ፡፡ ሁሉም በያሉበት መሥዋዕት ያቀርባሉ ፡፡ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት በሠዋው አነ ውእቱ ክርስቶስ ብሎ በርግም አምሳል ወርዶ ይመሰክራል ፡፡ ከዚህ በኋላ በሃይማኖት አንድ ይሆናሉ ፡፡ በግቢ ይገናኛሉ እንደዚህ የሚል ከምን አሉ ቢሉ ከገድለ ፊቅጦር ከራእየ ሲኖዳ ፡፡ ከመ ይኩን ስምዓ በላዕለ አሕዛብ ፡፡ ባላመኑ በአሕዛብ መፈራረጃ ይሆንባቸው ዘንድ ወይእተ አሚረ ይበጽሕ ሕልቀት ፡፡ ያልተያያዘ ይእተ አሚረ ነው የሐሳዊ መሲሕዝ ሲናገር መጥቶ የጥጦስን ይእተ አሚረ አለ ነቢይ ኢሳይያስ የጼዋዌን ነገር ሲናገር መጥቶ የሚጠትን ይእተ አሚረ እንዳል ፡፡ አለመፈጸሙን እንዲገነዘቡ ነው የተገለበጠው ፤ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ ስለሚል ነባራዊ ሁኔታን ተከትሎም የተረጐመው ይመስላል ፡፡ በጥሞና ቢያገናዝቡት እንኳንስ ወንጌል በእስላም ቤት ሊገኝ ፣ በእስላም አገር ክርስቲያን ነኝ የሚል ሰው እንኳን እንዳይኖር እየተሠራና የተፈጸመውን እየተከታተልን ያለነው ፡፡

      በቁጥር 15 ወእምከመ ርኢከሙ ትእምርተ ርኩስ ዘምዝባሬ ዘተብህለ በዳንኤል ነቢይ ዘይቀውም ውስተ መካን ቅዱስ ወዘያነብብ ለይለቡ ፡፡ ዳን 9፡27 ፤ ማር 13፡14

      ቁጥር 15ን ሲተረጉመው ሉቃ 21፡2ዐ ፡፡ በቅዱስ ቦታ የሚቆም ማለት ለቤተ መቅደስ አንባቢነት የሚሾም ያስተውል ተብሎ የተነገረውን ቤተ መቅደስ በሚፈርስበት ጊዜ የሚሆን የጥጦስን ጣዖቱን ያያችሁ እንደሆነ ያን ጊዜ ፍጻሜው ይመጣል ማለት የአይሁድ ጥፋት ይሆናል ትእምርተ በሳዖር እንዲል ፡፡ አንድም ቤተ መቅደስ በሚፈርስበት ጊዜ የሚሆን የጥጦስን ጣዖት ያያችሁ እንደሆነ ያን ጊዜ የአይሁድ ጥፋት ይሆናል ፡፡ ወዘተብሀለ በዳንኤልም ለቤተ መቅደስ አንባቢነት የሚሾመው ሰይለቡ ያለውን ያስተውል ፤ አንድም ወይእተ አሚረ ያን ጊዜ የአይሁድ ጥፋት ይሆናል ፡፡ ወእምከመ ርኢክሙ ቤተ መቅደስ በሚፈርስበት ጊዜ የሚሆንን የጥጦስን ጣዖቱን ያያችሁ እንደሆነ ወዘተብህለ ፡፡ ….


      በተረፈ የተሳሳተ ነገር ካልሆነብዎ ከንባብ ያገኘሁት መረጃ ፈላሻ ሙራ የሚባሉት ወገኖች ክርስቲያን እንዳልሆኑ የሚገልጽ ነው ፡፡ ያም በመሆኑ ነው ከኢትዮጵያዊው ክርስቲያን ኀብረተሰብ ሳይጋቡና ሳይዋለዱ ብዙ ዘመን ለብቻቸው የኖሩት (አንድን ጐሣ ለይቶ ለመምረጥ ያስቻለውም ይኸው አለመዳቀላቸው ነው) ፡፡ አሁንም በሌላው ዓለም ያሉት አይሁዶች ባህልና ወጋቸው ተመሳሳይ ነው ፤ ዘርና አንጓ መቁጠር ይወዳሉ ፤ ህጋቸው ስለሆነም ለመተግበር ይገደዳሉ ፡፡ እናማ በምድራችን የሆነውን ታሪክ ስንመለከተው ፣ ይኸኛው ወገን ጠቢብነታቸውን በመናቅ ስም አውጥቶ አግልሏቸው (ሳይጋባ ፣ ሳይዋሃድ) ኖረ ፤ እነዚያ ደግሞ በሃይማኖታቸውና በወጋቸው ምክንያት ራሳቸውን ለይተው ጠብቀው በአይሁድ ሥርዓትና እምነት አኖሩ ፡፡ አባ ወልደ ትንሣዔ ስለ ኦሪት ህግ መሻር ሲያስተምሩ ሬሣ እንኳን አጥበን ገንዘን የምናሰናዳላቸውና የምንሸከምላቸው እኛው ኢትዮጵያውያኖቹ ነን ብለው ነበር ፡፡ ምክንያት ቢሉ እሬሣ መንካት እንደሚያረክስ መጽሐፋቸው ስለሚናገር ነው ፡፡ ሌላው የማልስማማበት ደግሞ የሃሰተኛው ክርስቶስ መምጣት ምልክት በኢትዮጵያ ወንዝና ጅረት ብቻ ስለማይሆን ነው ፡፡ በዓለም ላይ ተበትኖ ያለው ወገን በሙሉ ክርስቶስ የተሰቀለለትና ደሙን ያፈሰሰለት ህዝብ ነውና የምስራቹን ሊያውቅ ግድ ይላል ፡፡ ለኢትዮጵያውያን ተለይቶ በምስጢር የመምጫውን ምልክት አይገልጽም ፡፡ አሁን እርስዎ እንዳሉን ያለውን ታሪክ ለአንድ ጃፓን ወይም አሜሪካ ለሚኖር ወይም ደቡብ አፍሪካ ላለ ክርስቲያን ቢያወጉለትና ትርጉም ቢጠይቁት ፈጽሞ እንደሚሉት አያመጣውም ፡፡

      ስለመግለጫዎ አመሰግናለሁ

      Delete
    7. ለAnonymous March 19, 2013 at 8:46 PM

      ም በሚል መለያ March 19, 2013 at 11:48 PM ስለተጻፈው አስተያየት በጣም ይቅርታ ለማለት ቀርቤአለሁ ፡፡ የአረፍተ ነገር መክፈቻው አትዘላብድ የሚል ስለሆነ ከወንድም ኃይለሚካኤል ቀጥሎ ያለውን ትንጥዬ ነጥብ ጋረደብኝ ፡፡ እንዲያ እንደጻፉት መልዕክትዎ ሰውን የለየ ቢሆንም እንኳን ከባድ ቃልን ከመጠቀም ተቆጥበን ፣ የምንቃወምበትን ምክንያት ብቻ ብናስረዳና በሥርዓቱ ብንገልጽ ፣ መግባባትና መስማማት ላይ መድረስ እንችል ይሆናልና ለወደፊቱ ሃሳብ አገላለጻችን የታረመ ቢሆን ማለት አሁንም እፈልጋለሁ ፡፡ ሰዎች የሚጽፉት ለራሳቸው እውነት የመሰላቸውን ስለሆነና ሃይማኖታችን የስንፍና ቃልን ስለማያስተምረን ይህን ለማለት እደፍራለሁ ፡፡

      Delete
    8. ሰላም ጤና ይስጥልኝ እንደምን ዋላችሁ፡ እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን።

      “ም” እንደጻፉት … “ሮም የዘመኑ ኃያል መንግሥት ስለነበረች ብንልና ከዚህኛው ዘመን ኃያል ጋር ብናያይዘው አሜሪካና እሥራኤል ሰምና ወርቅ እንጅ ጸላትነት የለባቸውም ፡፡ አንዱ ለአንዱ ሊሞት ቃል የተገባባ ሆኖ ነው የምናገኘው ፡፡”

      ወዳጄ ም ከአዲስ ኪዳን ትርጓሜ መጥቀሱንስ ጠቀሱት አሁንም ጭብጡን ያገኙት አልመሰለኝም። ስለመጽሐፍ ቅዱስ እየተነጋገርን ከግላዊ ከዓለማዊ አንጋገር መታቀብ ይኖርብናል። እንዳየሁዎት እርስዎ ብዙውን ነገር በሴኪዩላር መነጽር ነው የሚያዩት። ፕሮቴስታንቶችም እንዲሁ መንፈሳዊውን ነገር ማየት ስለማይችሉ በሴኪዩላር መነጽር ነው የሚያዩት።

      የትርጓሜ መጽሐፉ የሚለው እስራኤል የሚለው ክርስቲያንን ነው። አይሁድን አይሁድ ብሎ ነው እንጂ የሚጠራው እስራኤል አይልም። እርስዎ ግን እስራኤል ማለት አይሁድ ነው ብለው ነው እንደ አይሁዶችና እንደ ፕሮቴስታንቶች በመተርጎም ላይ የምናይዎት። በጣም ትልቅ ስህተት ነው። አእምሮዎት ይህን ስህተት ሳያርም ምንም ያህል መጻህፍ ቅዱስን ደጋመው ቢያነቡ መንፈሳዊ መልእክልቱን በፍጹም ሊያገኙት አይችሉም።

      ሕዝበ ሮም በሕዝበ እሥራኤል ላይ በጸላትነት ይነሡባቸዋል ፡፡ ይህ ማለት ሮም (ባቢሎን) በክርስትና ላይ ይዘምታሉ ማለት እንጂ ባቢሎን በአይሁድ ላይ ይነሳሉ ማለት አይደለም። ይህ ደግሞ በዘመናችን ተፈጽሟል። መጽሐፉ ስለአይሁድ መናገር ሲፈልግ “የጥጦስን ጣዖቱን ያያችሁ እንደሆነ ያን ጊዜ ፍጻሜው ይመጣል ማለት የአይሁድ ጥፋት ይሆናል ትእምርተ በሳዖር እንዲል” ይላል ፡፡ እንዲያውም የሚለው በዚህ ጊዜ የአይሁድ ጥፋት ይሆናል ይላል። ለተመረጡት ሲል ለህዝበ እስራኤል ማለትም ለክርስቲያኖችሲል ያች የጭንቅ ጊዜ ታጥራለች የሚለው እራሱ ፍርዱ የአይሁድን ጥፋት የክርስቲያንን ግን መጠበቅ የሚያሳይ ነው።

      ወዳጄ “ም” ይታረሙ። በክርስትና ታሪክ አይሁድ እስራኤል ሆነው አያውቁም። አይሁድን እስራኤል ብለው የተነሱ በቅርብ ጊዜ ከባቢሎን የፈለቁት ፕሮቴስታንቶችና አይሁድ እራሳቸው ብቻ ናቸው። የትኛውንም ጥንታዊ የክርስትና መጽሐፍ ያንብቡ - አይሁድ በክርስትያኖች ዘንድ እስራኤል ተብለው በፍጹም አያውቁም።

      “በዚህ ወቅት አንድም በኢየሱስ ስም የመጣና ክርስቶስ ነኝ በማለት ተከታይ ያፈራ ሐሳዊ መሲህ የለም” ያሉት ሐሰት ነው። አልጨበጡትም እንጂ ከላይ አቅርቤልዎት ነበር። ሃሰተኛ ክርስቶስ ማለትም በጨመረሻ ጊዜ የሚመጡ መሢሕ ክርስቶስን የሚያሳብሉ፣ በመሢሕ በክርስቶስ የሚያብሉ ሐሰተኞች መምህራን ይነሳሉ። ማለትም እኛ የምንነግራችሁን ወንጌል ተከተሉ እያሉ ህዝበ እስራኤልን ከሃይማኖት የሚያስወጡ ይመጣሉ እንደተባለው ፕሮቴስታንት የሚባሉ መሢሕ ክርስቶስን የሚያሳብሉ፣ በመሢሕ በክርስቶስ የሚያብሉ ሐሰተኞች መምህራ ከባቢሎን ተነስተው ስንቱን ከሃይማኖት እንዳስወጡት አያውቁምን። ከክርስቶስ ያልሆኑ፤ በኢየሱስ ስም የመጡ እንግዲህ እርስዎ እንዲያውቁት እነርሱ ናቸው።

      ፈላሻ ሙራ ክርስቲያን አልነበሩም ያሉት የተሳሳተ ነው። ፈላሾች ናቸው ክርስቲያን ያልነበሩት። ፈላሻ ሙራ ያሏቸው ግን ክርስቲያኖችን ነው።

      እኔ የምሰጥዎት ምክር መንፈሳዊነትን እንዲላበሱ፣ ከፕሮቴስታንቶችና ከአይሁድ መንገድ እንዲቆተቡ፣ አባቶቻችን ትተውልን የሄዱትን ትርጓሜ በቅን ልቦና እንዲያዩ ነው። ብሉይ ትርጓሜን በሴኪዩላር መንገድ ሊተቹ ሲቃጣዎት አይቻለሁ። ከእንዲህ አይነቱ አኪያሄድ ይቆጠቡ። ወደዱም ጠሉም የቀደመችዋ አንዷ መንገድ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ናት። ሌላ በሴኪዩላር አስተሳሰብ የተበከለ አመክንዮን በመጠቀም ይህችን ኃይማኖት ለመሞገት መሞከር ተገቢ አይደለም። ወንጌል በዓለም ይሰበካል እንዳለ መጽሐፉ ተሰብኳል። እራሳቸው ክርስትናን ሊያጠፏት መጽሃፍ ቅዱስን ከባቢሎን የተነሱት ሐሰተኞች መምህራን እራሳቸው ሳይቀር በዓለም አዳርሰውታል። መፈራረጃ ሊሆንባቸው ወንጌልን ያዙት እንዳሉ (አለቃ አያሌው፣ የራስ ቅል) መጽሀፍ ቅዱስን ለመተቸት እስላሞች ወንጌልን ይዘው ትችት እንድሚያወጡ አያውቁምን። ለአባቶቻችን ትርጓሜ ምን ይወጣለታል? እንዲያውም አስደናቂነቱ ከነትንቢቱ መፈጸም ጋር መሆኑ ነው።

      ምስጋና ለመድኃኒዓለም።
      ኃይለሚካኤል።

      Delete
    9. ወንድም ኃይለሚካኤል በቅድሚያ የክርስቶስ ሰላም እንዲበዛልዎ ምኞቴ ነው ፡፡

      ወደ ሃሳቤ ከመግባቴ በፊት ርሶ መደምደሚያ ያደረጉትን አስተያየት ቅሬታዬ በማድረግ መግለጽ እወዳለሁ ፡፡ እኛ ሌሎች ሰዎች የሚያቀርቡትን ሃሳብ ከመሞገትና ከማሳመን ይልቅ ዓይነትና ዘር ሰጥተን ቢቻለን ለማሸማቀቅ የመሞከር ልማድ አለን ፡፡ ይኸን አካሄድ ከጽሁፍዎ በተደጋጋሚ አይቼብዎታለሁና እኔን ታረም እንዳሉኝ ርሶም ይህን ያርሙት እልዎታለሁ ፡፡ በቅድሚያ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ተከታይና አማኝ ባልሆን በድፍረት ለመጻፍ ባልሞከርኩም ነበር ፡፡ ከዛ በላይ ደግሞ እኔም ይህን መሰሉኝ አለማለቴን ልብ ይበሉት ፡፡

      የምጽዓት ትንቢትን በዓለማዊ ቋንቋ አትተርጉመው ያሉትም አልተስማማኝም ፡፡ ምክንያቱም ጌታችን ለተከታዮቹ ሲያስተምር ምልክቶቹ ሲፈጸሙ ታያላችሁ ያለው እዚሁ በምድራችን (ምድራዊ ክስተቶች ስለሆኑ) እንጅ በሌላ የዓለም ክፍል አይደለም ፡፡ ስለሆነም ከምናየውና ከምንሰማው አያይዘን ሁኔታዎችን መገንዘብና (መተርጐም አላልኩም) የጊዜውን መቅረብ መገመት እንችላለን ፡፡ እንዲያ ካልሆነማ የምን ጦርነትና ቸነፈር ምልክትነት እንናገራለን ? እንደተረዳሁት ርሶም ከዚሁ ከነባራዊ ሁኔታ (ዓለማዊ) እይታዎ ነው ሊደመደም ነው እያሉ የሚያስፈራሩን ፡፡ ሌላ ቀርቶ የኢትዮጵያ ለሁለት መከፈልን እንደ ምልክት አድርገው ሲጠቀሙበት ሃይማኖት እንደፈረሰ አድርገው ነው ያስነበቡን ፡፡ ኤርትራውያን በመገንጠላቸው ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖታቸውን የሻሩ አስመስለው ፡፡ ከሃይማኖተኛነት ይልቅ የኢትዮጵያዊነት ስሜትዎ በብዙ ጐልቷል ፡፡

      “በክርስትና ታሪክ አይሁድ እስራኤል ሆነው አያውቁም” ያሉትም ለእኔ ትክክል ሆኖ አላገኘሁትም ፡፡ ብዙ ሳንሄድ ሐዋርያቱና ደቀ መዛሙርቱ ራሳቸው የአይሁድ ወገን ናቸው ፡፡ አይሁድ ኦርቶዶክስ (የመሲህን መምጣት ገና ወደፊት ይሆናል ብለው የሚጠብቁ) እና አይሁድ ክርስቲያን (የኢየሱስን መሲህነት የተቀበሉ) ተብለው እንደሚከፈሉ ነው ያለኝ መረጃ ፡፡ አይሁድ የሚለው ስያሜ ለምን ጐልቶ እንደወጣ ለማወቅ ቢፈልጉ ታሪካቸውን ሲፈትሹ በቀላሉ ያገኙታል ፡፡

      እሥራኤል የሚለውን ስያሜ ደግሞ ከየት እንደ መጣ ለማወቅ ስንፈልግ ለያዕቆብ እግዚአብሔር እንዳወጣለት ዘፍጥረት 32፡28 ይነግረናል ፡፡ በሰሜንና በደቡብ የመከፈላቸው ታሪክ ጋር ሳንመጣ እንኳን አሥራ ሁለቱ ነገዶች የተነሱት ከያዕቆብ አብራክ ስለሆነ እሥራኤላውያን (የያዕቆብ ነገድ ስለሆኑ) የሚለው ስም የነርሱው መለያ ነው ፡፡ ኋላ ሰሜንና ደቡብ በማለት በአምልኮ መለያየት ቢከፋፈሉም (አይሁድ የሚለውም) መነሻ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ታሪኩ ይኸው ነው ፡፡ ይኸንኑ ስምም እንደያዙ ከግብጽ መውጣታቸውም በኦሪት ዘጸአት ተዘግቧል ፡፡ ጊዜ ስለሚሻማ ከዚህ በላይ ብዙ ማለት አልፈልግም

      ሃሰተኛ ክርስቶስ ሲለን አንድን ግለሰብ ነው እንጅ ርሶ እንደሚሉት ብዙ ሰባኪዎችን አይደለም ፡፡ “እስመ ብዙኃን ይመጽኡ በስምየ እንዘ ይብሉ አነ ውእቱ ክርስቶስ” ከሚለው ውስጥ አነ ውእቱ ክርስቶስ ማለትም እኔ ክርስቶስ ነኝ ፤ እኔ ክርስቶስ ነኝ የሚሉ ማለቱን ልብ ቢሉልኝ ለማለት ነው ፡፡ ክርስቶስ ነኝ ያለ ስላልሰማሁ ነው ሙግቴ ፡፡ ኢየሱስን መካድና ትምህርቱን ማሳበል ማስረጃዬ ነው ካሉ ደግሞ ከክርስትና እምነት ውጭ ያሉት (ስም አልጠቅስም) በሙሉ ኢየሱስን የሚክዱና የሚያሳብሉ ናቸው ፡፡ ዕድሜአቸውም ሺህ ዓመት ያስቆጥረን ይሆናል ፡፡

      ስለ ፈላሻ ያነሱት ልዩነትን አላውቀውም ነበር ፡፡ ለእኔ ግን በፈላሸ ስም የሄደ የኤኮኖሚ ስደተኛው ፈላሻ ሙራ ተብሎ እንዳይሆን እጠረጥራለሁ ፡፡ ምክንያቱም ነገደ እሥራኤሎች ተለይተው በአንድ አካባቢ ስለኖሩና ፣ በቅርብ የሚያውቋቸውም ወገኖች ይኸንኑ ስለሚመሰክሩ ነው፡፡

      “ወንጌል በዓለም ይሰበካል እንዳለ መጽሐፉ ተሰብኳል።” ላሉትም እንኳን በዓለም ኢትዮጵያ ውስጥ ላለው ወገን እንኳን ስብከቱ አልተዳረሰም ፡፡ መሰበክ ማለት ተከታይ ማለቴ ሳይሆን መረጃ ማግኘትን ብቻ ነው የሚመለከተው ፡፡ ታድያ በአገራችን ዳር አገር እንኳን የሚኖረው ሕዝብ ኢየሱስ ማን መሆኑን መች ሰምቷልና ለዓለም ሕዝብ ተሰብኳል ብለው ያምናሉ?

      “መጽሀፍ ቅዱስን ለመተቸት እስላሞች ወንጌልን ይዘው ትችት እንድሚያወጡ አያውቁምን።” ከመቶ የማይበልጡ የሃይማኖት ጠበብቶች መጽሐፍን ለመመርመርና አቃቂር ለማውጣት ስላነበቡት ወደ ቢሊዮን የሚጠጋው ሕዝብ ቤት ወንጌል ገብቷል ብለው ለመተርጎም ሲሞክሩ ፣ መግለጫው ስለሚያመችዎ ብቻ ምን ያህል እንዳገዘፉት ነው የተረዳሁት ፡፡

      አመሰግናለሁ

      Delete
    10. ፩- ሐዋርያት አይሁድ ነበሩ። ከክርስቶስ በኋላ ግን ክርስቲያን ናቸው። ኢትዮጵያውያንም አይሁድ ነበሩ። እነሱም ከክርስቶስ በኋላ ክርስቲያን ናቸው። ይህም ፈላሻዎችን ሳይጨምር ነው። የውውይቱን ነጥብ ሆን ብለው በመሳት ሌላ አስፈላጊ ያልሆነና ጉዳዩን የማይመለከት ሃተታ ወስጥ ለምን እንደሚገቡ ለኔ ግልጽ ነው። እውነታን ለመቀበል አይፈልጉም። ጥያቄው እስራኤል ማነው? የሚል ነው። ጥያቄው ለአሁን ጊዜ ነው እንጂ ከክርስቶስ ልደት በፊት እነማን ነበሩ አይደለም።

      መልሱ ሊሆን የሚችለው ከሁለት አንድ ነው።
      ሀ) አይሁድ (በቴላቪቭ ሰፍረው መንግሥት መስርተው እኛ አይሁድ ነን ክርስቶስ በሥጋ እንደመጣ አናምንም የሚሉት)
      ለ) ክርስትያን

      ጭብርብር ካለው አስተያየትዎ መውሰድ እንደሚቻለው በእርስዎ እምነት እስራኤል ማለት አይሁድ ማለት ነው። ያ እምነት ካለዎት እርስዎ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ አማኝ አይደሉም ምክንያቱም ኦርቶዶክስ ተዋህዶ በክርስቶስ የማያምኑት አይሁድ እስራኤል ናቸው ብላ አታምንም። በኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነት እስራኤል ማለት የተዋህዶ አማኝ ክርስቲያን ነው።

      ካቶሊኮችም ቢሆን አይሁድን እስራኤል ናቸው ብለው አያምኑም። በኢየሱስ ስም መጥተናል ከሚሉት ውስጥ አይሁዶችን እስራኤል ናቸው ብለው የሚያምኑ ፕሮቴስታንቶች ብቻ ናቸው። እርስዎ እንግዲህ ከነሱ ጋር አንድነት ያለዎት ይመስላል።

      ማስረጃው ቀርቧል። አዲስ ኪዳን ትርጓሜ ብቻ ሳይሆን በየትኛውም የክርስትና መጽሃፍ በክርስቶስ የማያምኑት አይሁድ ከክርስቶስ ስቅለትና ማረግ በኋላ እስራኤል ተብለው አያውቁም። የትኛውንም መንፈሳዊ መጽሀፍ ማየት ይቻላል - እስራኤል ማለት ክርስቲያን ነው።


      ፪ - ሃሰተኛ ክርስቶስ ስለሚለው የአዲስ ኪዳን ትርጓሜ ተርጉሞ አቀረበልዎ። እሱን አልቀበልም ነው የሚሉት?

      ሐሳዊያነ መሢሕ (ፕሮቴስታንት) ይመጣሉ፣ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የተጠመቁትን አሳስተው ከኃይማኖት ያስወጣሉ። የጥጦስን ጣኦት (የተቀናበረ ሳይንስን) ተከተሉ ይላሉ። የጥጦስ ጣኦት ደግሞ ክርስቶስ (አምላክ) ማለት እኔ ነኝ ይላል(ሂግስ ቦሶንን እና ዳርክ ኢነርጂን ይመልከቱ)። ሐሳዊያነ መሢሕ እስራኤል ማለት አይሁድ ናቸው ይላሉ። ከአይሁድም ጋር አንድነት ፈጥረው ክርስቲያኖችን ያጠፋሉ (ሃይማኖታቸውን ያስቀይራሉ)። በዚህም በቀጥታ በጸረ-ክርስቶስነት ይቆማሉ።

      ፫ - ስለፈላሻ ካላወቁ ስለማያውቁት ነገር ለምን ያወራሉ። ለነገሩ በሁሉም ነጥብቦች ላይ እንደማይዎት የሚያወሩት ስለማያውቁት ነገር ነው። አይሁድ ከደርግ ጊዜ ጀምሮ ኦርት (ኦርጋናይዜሺን ሪሃቢሊቴሽን ትሬኒንግ) የሚባል ድርጅት በኢትዮጵያ አቋቁመው ፈላሾችንና ክርስቲያን የሆኑትን “ፈላሻ ሙራ” የሚሏቸውን ለመውሰድ ለረጂም ጊዜ ብዙ ዝግጅትና ድርጅት ሲያደርጉ ቆይተዋል። ክርስቲአን የሆኑት ክርስቶስን አስክደው ወደ አይሁድነት በመመለስ በአውሮጵላኖች እያጎሩ የወሰዱት በቅርብ ጊዜ ነው። ስለማያውቁት ነገር ሌላ ትርፍ ነገር ማውራትዎ መልካም አይደለም።

      ፬ - ለአረቦች መጀመሪያ ክርስትናን የሰበኩ ኢትዮጵያውያን ነበሩ (በቅዱስ ያሬድ ዘመን አቅራቢያ)። አረቦች ወንጌልን ትተው እስልምናን መሠረቱ። እንዳውም ክርስትናን አጠፉ። አሁንም ወንጌሉን ለማጥፋት ቃፊሮቻቸው መጽሐፍ ቅዱስን ይዘው ይተቻሉ። ወንጌል ለነሱም ተሰብኮአል አልተቀበሉም እንጂ።

      ፭ - ወደ መነሻው ሃሳብ ለመምጣት በአሁኑ ሰዓት ክርስቶስ የተናገራቸው ማስጠንቀቂያወች በሙሉ በመፈጻም ላይ ናቸው። ወደ ቀደመችው ኃይማኖት ወደ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ባስቸኳይ መመለስ ለሁሉም ይጠቅማል።

      እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን።
      ኃይለሚካኤል

      Delete
    11. ተራ ቁጥሩ ርስዎ በጻፉት ልክ ነው ፡፡
      በቅድሚያ ሙግቴ ወደ እውነት ለመድረስ እንድንችል በሚል ስሜት ስለሆነ እንዳያዝኑብኝ እጠይቃለሁ፡፡
      ፩. “በእርስዎ እምነት እስራኤል ማለት አይሁድ ማለት ነው። ያ እምነት ካለዎት እርስዎ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ አማኝ አይደሉም” ያሉኝ ስህተት ነው ፡፡ ምክንያቱም የክርስቲያንነት መስፈርቱ ውስጥ እንዲህ እርሶ እንደሚሉት የእስራኤልንና የአይሁድን ልዩነት በማወቅ የሚል በዶግማና ቀኖናችንም ሆነ በትምህርተ ሃይማኖት መግለጫ ውስጥ የተካተተ ጉዳይ ስላልሆነ ፡፡ በተረፈ እስራኤል ስለሚለው ቃል የመጽሐፍ አገባብ በመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት በሥርዓቱ ምዕራፍና ኃይለቃል እየቆጠረ ይተነትነዋልና በገጽ 18ዐ እና ገጽ 132 የሠፈረውን ልብ ብለው ቢመለከቱት ለርስዎ ተጨማሪ ዕውቀት ሊሆን ይችላል ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የመጽሐፍ ቅዱሱን ቃል ከተረጎመልን መካድ አንችልምና ወይም አይገባንምና ስለ ግብዣዬ ይመልከቱት ፡፡

      ፪. ከኘሮቴስታንቶች ጋር ያለን የነገረ ክርስቶስ ልዩነት እነርሱ ሰውነቱን አግዝፈው አሁንም በየዕለቱ አብን እየለመነ ያማልዳል ስለሚሉን ነው እንጅ በኢየሱስ ክርስቶስ ሰውና አምላክነት እምነት ላይ ክህደት የለባቸውም ፡፡ ሌሎች በነገረ ማርያም ፣ ነገረ ድኀነት ፣ ነገረ ቅዱሳንና ጻድቃን ፣ ስለ መስቀልና ቅዱሳን ስዕላት ፣ ስለ ትውፊትንና አዋልድ መጽሐፍት ፣ ስለ ምንኩስናና ስለእምነትና ምግባር አስፈላጊነት ፣ … የምንለይባቸውን ትምህርቶች ሳልጨመር ማለት ፡፡

      ፫. ስለፈላሻ አላውቅም ያልኩዎት የርሶን ዘመን አመጣሽ ክፍፍል እንጅ፣ ነባር ታሪካቸውን አልነበረም ፤ እስከ አሁንም የጻፍኩልዎት ከልቤ የፈለቀ ድርሰት ሳይሆን ከንባብና ከሰዎች የተማርኩትን ነው ፡፡ ባላውቅ ርዕሱን እንኳን አላነሳውም፤ ስለ እምነታቸውም ምንነት መረዳት አልችልም ነበር ፡፡

      ፬. የምንወያየው የነበረ ታሪክን ለመማር ስላልሆነ ፣ በተጨባጭ በአሁኑ ሰዓት ቁጥሩ ወደ ቢሊዮን ሊጠጋ የደረሰው ትውልድ ወንጌል ተሰብኮለት ፣ አንደምታ የትርጓሜ መጽሐፍ እንደሚያስነብበንም መጽሐፍ ቅዱስ ለአምልኮም ይሁን ለመመርመር ወደየቤቱ አስገብቷል ወይስ ወንጌሉ አልተሰበከም መጽሐፉም በየቤቱ የለም? በነበረ ታሪክ ከቀጠሉ ደግሞ የመጨረሻው ዘመን የጀመረው ዛሬ ሳይሆን የዛሬ ሺህ ስድስት መቶ ዓመት ገደማ ነውና ዛሬ ትኩስ ተደርጎ ሊታወጅ አይገባም ለማለት እደፍራለሁ ፡፡

      ፭. ጌታችን ማንም እንዳያስታችሁ ብሎ ስላስጠነቀቀን ፣ በምናነበውና በምንሰማው ሁሉ ተስበን እንዳንስት መጠንቀቅ ይገባል ፡፡ የፍጻሜውን ጊዜ ለይተን መናገር ባንችልም በኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነታችን መጽናትና ተዘጋጅተን መጠበቅ ይገባናል የሚለውን እኔም አስተላልፋለሁ ።
      አመሰግናለሁ

      Delete
    12. ሰላም ጤናይስጥልኝ እንደምን ዋላችሁ። እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን።

      ብዙ ኢትዮጵያውያን በፕሮቴስታንቶች አሳሳች ትምህርቶች እየተወናበዱ እስራኤል ማን እንደሆነ አለማወቅ ብቻ ሳይሆን እንዲያውም “እስራኤል ናቸው” እያሉ ከጸረ-ክርስቶስ ኃይሎች ጋር ሳያውቁ በመሰለፍ ላይ በመሆናቸው እስራኤል ማን ነው የሚለውን ግልጽ ማድረግ አስፈላጊ ነው ብየ ስላመንኩ ይህን ተጨማሪ ትንታኔ አቅርቤያለሁ።

      ከአይሁድ ጋር የነበረውን ኪዳን የሚያሳየው ብሉይ ኪዳን ነው። እግዚአብሔር ብሉይን አሳልፎ አዲስ ኪዳንን ሰጥቷል፥ የዚህ አዲስ ኪዳን ባለውሎች ክርስቲያኖች እንጂ አይሁድ አይደሉም። በአዲስ ኪዳን እስራኤል ማለት ክርስቲያን ነው - ክርስቶስ በሥጋ እንደመጣ የሚያምነው የተዋህዶ አማኝ ክርስቲያን።

      እግዚአብሔር ክርስቲያኖች የተመረጣችሁ ናችሁ ይላል። አይሁዶች ምርጥነትን የሚያገኙት ክርስቲያን ሲሆኑ ብቻ ነው።

      ወደ ቆላስይስ ሰዎች፥ ምዕራፍ ፫ - ከቁጥር ፱ ጀምሮ - እርስ በርሳችሁ ውሸት አትነጋገሩ፥ አሮጌውን ሰው ከሥራው ጋር ገፋችሁታልና፥ የፈጠረውንም ምሳሌ እንዲመስል እውቀትን ለማግኘት የሚታደሰውን አዲሱን ሰው ለብሳችሁታል። በዚያም የግሪክ ሰው አይሁዳዊም የተገረዘም ያልተገረዘም አረማዊም እስኩቴስም ባሪያም ጨዋ ሰውም መሆን አልተቻለም፥ ነገር ግን ክርስቶስ ሁሉ ነው፥ በሁሉም ነው። እንግዲህ እንደ እግዚአብሔር ምርጦች ቅዱሳን ሆናችሁ የተወደዳችሁም ሆናችሁ፥ ምሕረትን፥ ርኅራኄን፥ ቸርነትን፥ ትህትናን፥ የዋህነትን፥ ትዕግሥትን ልበሱ።

      በአዲስ ኪዳን የእግዚአብሒር ልጆች የሚባሉት ክርስቲያኖች ብቻ ናቸው። አይሁድ የእግዚአብሒእ ልጆች አይደሉም። የእግዚአብሔር ቤት ቤተክርስቲያን ናት፣ አይሁድ አይደሉም።

      ወደ ሮሜ ሰዎች ምዕራፍ ፰ ቁጥር ፲፬ - በእግዚአብሔር መንፈስ የሚመሩ ሁሉ እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸው።

      ወደ ጢሞቴዎስ ሰዎች ፩ኛ መልእክት - በእግዚአብሔር ማደሪያ ቤት መኖር እንዴት እንደሚገባ ታውቅ ዘንድ እጽፍልሃለሁ፤ ቤቱም የእውነት ዓምድና መሠረት፥ የሕያው እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ነው።

      የተመረጠው ህዝበ-እስራኤል ክርስቲያን ነው። በብሉይ ኪዳን ለአይሁድ አሁንም ቃሌን በእውነት ብትሰሙ ኪዳኔንም ብትጠብቁ፥ ምድር ሁሉ የእኔ ናትና ከአሕዛብ ሁሉ የተመረጠ ርስት ትሆኑልኛላችሁ፤ እናንተም የካህናት መንግሥት የተቀደሰም ሕዝብ ትሆኑልኛላችሁ። ያላቸውን በአዲስ ኪዳን ለክርስቲያኖች አድሷል። ክርስቲያኖች ካልሆኑ አይሁድ የእስራኤል ጠላት እንጅ እስራኢእል አይባሉም።

      የመጀመሪያው የጴጥሮስ መልእክት ምዕራፍ ፪ ከቁጥር ፮ ጀምሮ - በመጽሐፍ። እነሆ፥ የተመረጠና የከበረን የማዕዘን ራስ ድንጋይ በጽዮን አኖራለሁ በእርሱም የሚያምን አያፍርም ተብሎ ተጽፎአልና። እንግዲህ ክብሩ ለእናንተ ለምታምኑት ነው፤ ለማያምኑ ግን አናጢዎች የጣሉት ድንጋይ እርሱ የማዕዘን ራስ የዕንቅፋትም ድንጋይ የማሰናከያም ዓለት ሆነ፤ የማያምኑ ስለ ሆኑ በቃሉ ይሰናከሉበታልና፤ ለዚህ ደግሞ የተመደቡ ናቸው። እናንተ ግን ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃኑ የጠራችሁን የእርሱን በጎነት እንድትናገሩ የተመረጠ ትውልድ፥ የንጉሥ ካህናት፥ ቅዱስ ሕዝብ፥ ለርስቱ የተለየ ወገን ናችሁ።

      በኢትዮጵያ አይሁዶች በዘመነ አዲስ ኪዳን ነገደ እስራኤል ተብለው አያውቁም። ቤተ እስራኤል ብለው እራሳቸውን የሚጠሩት እራሳቸው ፈላሾች እንጂ ክርስቲያኖች ቤተ እስራኤል አላሏቸውም፣ አይሏቸውምም። እንዲያውም ክርስቲያኖች ካይላ ብለው ነበር አይሁዶችን የሚጠሯቸው። ካይላ ማለት ደግሞ የክርስቶስ ጠላት ማለት ነው።

      ካቶሊኮች ደግሞ እስራኤል ማለት ማን እንደሆነ የሚሉትን ማወቅ ለምትፈልጉ የሚከተለውን ሊንክ ተመልከቱ።

      http://catholicknight.blogspot.com/2011/01/catholic-church-is-israel.html

      http://www.preteristarchive.com/PartialPreterism/provan-charles_dd_01.html


      የግሪክ ኦርቶዶክሶች ደግሞ እስራኤል ማለት ማን እንደሆነ የሚሉትን ማወቅ ለምትፈልጉ የሚከተለውን ሊንክ ተመልከቱ። እነሱም እስራኤል ክርስቲያን ብቻ ነው ይላሉ።

      http://www.goarch.org/ourfaith/ourfaith9285

      እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን።
      ኃይለሚካኤል

      Delete
    13. ሰላምና ጤና ይስጥልኝ ፤
      “እግዚአብሔር ብሉይን አሳልፎ አዲስ ኪዳንን ሰጥቷል፥ የዚህ አዲስ ኪዳን ባለውሎች ክርስቲያኖች እንጂ አይሁድ አይደሉም።” ላሉት
      እነሆ፥ ከእስራኤል ቤትና ከይሁዳ ቤት ጋር አዲስ ቃል ኪዳን የምገባበት ወራት ይመጣል፥ ይላል እግዚአብሔር ፡፡ ኤር 31፡31 (ትኩረት ለእስራኤልና ለይሁዳ ቤት ማለቱን) ፤ ብሉይን አሳለፈ ያሉትም የመጠሪያ ስም ለውጥ ማድረግ አይደለም ፡፡ የሚሻረውን መሻር ፣ የሚሻሻለውን ማሻሻል ፣ እንዳለ የሚቀጥለውን ማጽናት ነው ይሉታል አባ ወልደ ትንሣኤ ፡፡ እርስዎ እንዳሉት ቢሆን ግን የብሉይን መጽሐፍ ለይቶ ማውጣት በጣም ቀላሉ መፍትሄ በሆነ ነበር ፡፡

      ስለ አይሁድና እስራኤል እኔም ያነበብኩትን (ብጋብዝዎትም ያላነበቡት ስለመሰለኝ) አቀርበዋለሁ ፡፡ ከኘሮቴስታንት ቤተ እምነት የተማርኩት እንዳይመስልዎት ለማለት ፣ ጽሁፉ የተገኘው ከቤተ ክርስቲያናችን መሆኑን እንዲመለከቱት አድራሻው ይኸው ፡፡
      http://ethiopianorthodox.org/amharic/holybooks/metsehafkidus/dictionarytitle/EBSDict_04.pdf

      ገጽ 158 ፤ “አይሁድ ማለት የይሁዳ ነገዶች የሚጠሩበት የብዙ ቁጥር ስም ነው ፡፡ በመጀመሪያ ቃሉ በይሁዳ የሚኖሩትን ሰዎች ያመለክታል (2 ነገ 16፡6 ፤ 18፡26)፡፡ በኋላም ከምርኮ ከተመለሱት የሚበልጡቱ ከይሁዳ ነገድ ስለሆኑ ፣ እንደዚሁም ወደ ይሁዳ አገር ስለተመለሱ ቃሉ በይሁዳም ሆነ በሌላ አገር ለሚገኙ ለያዕቆብ ዘሮች ሁሉ መጠሪያ ሆነ ፤ (ኤር 34፡9 ፤ ሥራ 2፡5 ፤ 16፡1) ፡፡ ነገር ግን ክርስቶስን ስላልተቀበሉ አይሁድነታቸው እውነተኛ እንዳልሆነ ተነግሯል (ሮሜ 2፡28 ፤ ራዕ 2፡9 ፣ 3፡9)”

      በቅድሚያ ከመጽሐፍ ቅዱስ መነሻ ታሪኩን ፡-
      … “በዚያች ሌሊትም ያዕቆብ ተነሣ፥ ሁለቱን ሚስቶቹንና ሁለቱን ባሪያዎቹን አሥራ አንዱንም ልጆቹን ወስዶ የያቦቅን ወንዝ ተሻገረ። ወሰዳቸውም ወንዙንም አሻገራቸው፥ ከብቱንም ሁሉ አሻገረ። ያዕቆብ ግን ለብቻው ቀረ፤ አንድ ሰውም እስከ ንጋት ድረስ ይታገለው ነበር። እንዳላሸነፈውም ባየ ጊዜ የጭኑን ሹልዳ ነካው፤ ያዕቆብም የጭኑ ሹልዳ ሲታገለው ደነዘዘ። እንዲህም አለው። ሊነጋ አቀላልቶአልና ልቀቀኝ። እርሱም። ካልባረክኸኝ አልለቅቅህም አለው። እንዲህም አለው። ስምህ ማን ነው? እርሱም። ያዕቆብ ነኝ አለው። አለውም። ከእንግዲህ ወዲህ ስምህ እስራኤል ይባል እንጂ ያዕቆብ አይባል፤ ከእግዚአብሔር ከሰውም ጋር ታግለህ አሸንፈሃልና። ያዕቆብም። ስምህን ንገረኝ ብሎ ጠየቀው። እርሱም። ስሜን ለምን ትጠይቃለህ? አለው። በዚያም ስፍራ ባረከው። ያዕቆብም። እግዚአብሔርን ፊት ለፊት አየሁ፥ ሰውነቴም ድና ቀረች ሲል የዚያን ቦታ ስም ጵኒኤል ብሎ ጠራው። ጵኒኤልንም ሲያልፍ ፀሐይ ወጣችበት፥ እርሱም በጭኑ ምክንያት ያነክስ ነበር። ስለዚህም የእስራኤል ልጆች እስከ ዛሬ ድረስ የወርችን ሹልዳ አይበሉም፤ የያዕቆብን ጭን ይዞ የወርችን ሹልዳ አደንዝዞአልና።” ዘፍ 32፡22-32

      ከዚህ የመጽሐፍ ቃል ተነስተው እስራኤል የሚለው ቃል ሲተረጉሙት ፡-
      1. እስራ በዕብራይስጥ - የሚያቸንፍ ማለት ነው
      2. ከእግዚአብሔር ከሰውም ጋር ታግለህ አሸንፈሃልና በማለቱ - መልአክን የሚያሸንፍ ተብሎ በአባቶች ተተርጉሟል
      3. ያዕቆብ እግዚአብሔርን ፊት ለፊት አየሁ ብሏልና እግዚአብሔርን ያየ ወይም የተመለከተ ማለትም ነው

      በገጽ 18ዐ እስራኤል የሚለውን ቃል በመጽሐፍ አገባብ ሲተነትነው ያልኩዎት ፤
      1. የአብርሃም የልጅ ልጅ (የይስሃቅ ልጅ) ያዕቆብ ከእግዚአብሔር ጋር ታግሎ ካሸነፈ በኋላ (ትርጉሙን ስለማልረዳው ስጽፈው ጨነቀኝ)፣ ካልባረክኸኝ አልለቅህም ባለ ጊዜ እግዚአብሔር እስራኤል ብሎ ሰየመው ፡፡ ትርጓሜውም ከእግዚአብሔር (መልአክ) ጋር ይታገላል ፤ ያሸንፍማል ማለት ነው ዘፍ 32፡22-32

      2. ከያዕቆብ ዐሥራ ሁለት ልጆች የተገኙት እስራኤል (ዘፍ 49፡7 ፤ ዘጸ 14፡3ዐ) የእስራኤል ልጆች (ዘጸ 3፡9) ወይም ዐሥራ ሁለት የእስራኤል ነገዶች (ዘፍ 49፡28) ይባላሉ ፡፡ ጌታችንም ለሐዋርያቱ በአሥራ ሁለቱ የእስራኤል ነገድ ስትፈርዱ በአሥራ ሁለት ዙፋን ትቀመጣላችሁ ብሏል (ማቴ 19፡28) ፡፡ የብሉይ ታሪክ ነው እንዳንል ደግሞ ራእይ 7፡5-8 ነገዶቹ እነማን እንደሆኑ በስም ይቆጥራቸዋል ፡፡

      3. ከሰሎሞን ዘመን በኋላ ከነገዶቹ ዐሥሩ በሮብዓም ላይ ባመፁ ጊዜ ኢዮርብአምን አንግሠው ያቋቋሙአት ሰሜናዊት መንግሥት እስራኤል አንዳንዴም ኤፍሬም ተብላለች (1 ነገ 12፡16-17) ፡፡ ኢዮርብአም እስራኤላውያን በጸሎት ምክንያት ወደ ኢየሩሳሌም እንዳይጓዙ በማለት የወርቅ ጥጃዎችን አሠርቶ አምልኮ ጣዖትን አስጀመራቸው ፡፡ ተከታይ ነገሥታት ሁሉ ይህንኑ ባዕድ አምልኮ ቀጠሉ ፡፡ ዋና ከተማቸው ሰማርያ ነበረች ፤ ከሁለት መቶ ዓመታት በኋላ በአሦር መንግሥት ተደመሰሰች (2 ነገ 17) ፡፡ የደቡቧ ግዛት ደግሞ ይሁዳ ትባል ነበር ፡፡ ዋና ከተማዋም ኢየሩሳሌም ነበረች ፡፡

      4. ከልዩ ልዩ ነገዶች በተለይ ከይሁዳና ከብንያም ነገዶች ከምርኮ የተመለሱት እስራኤላውያን ብዙ ጊዜ አይሁድ* ይባሉ ነበር (ዕዝ 1፡5 ፤ 5፡1 ፤ ማቴ 2፡1) ፤ በጥንት ስማቸውም እስራኤል ተብለው ይጠሩ ነበር (ዕዝ 2፡2 ፤ ዘካ 9፡1 ፤ ሚል 1፡1 ፤ 2፡11 ፤ ማቴ 2፡2ዐ) ፡፡

      5. ከእስራኤል የሚወለዱ ሁሉ እስራኤል አይደሉም እንደተባለው (ሮሜ 9፡6 ፣ 2፡28-29) ፣ የእግዚአብሔር እስራኤል የአብርሃምን የእምነት ፍለጋ የሚከተሉ ናቸው (ሉቃ 19፡8-9 ፤ ሮሜ 4፡12) ፡፡ ይህም ማለት ከአይሁድ ብቻ ሳይሆን ክርስቶስን በማመን አዲስ ፍጥረት የሆኑ ሁሉ ማለት ነው ፡፡ ገላ 3፡6-14፡29 ፣ 6፡15-16 ፤ 2 ቆሮ 5፡17 ፤ መዝ 73፡1 ፤ ኢሳ 56፡8 ፤ ዮሐ 1ዐ፡16 ፤ ዮሐ 1፡48 ፤ ራእ 7፡9

      ጌታችን ሲያስተምር ደግሞ “ከእስራኤል ቤት ለጠፉት በጎች በቀር አልተላክሁም” ብሏልና (ማቴ 15፡24) እንደ እርስዎ ትርጓሜ ቢሆን ኢየሱስ ከመምጣቱ በፊትም ክርስትናና ክርስቲያኖች ነበሩ ያሰኛል ፡፡”
      ይቀጥላል

      Delete
    14. ክፍል ሁለት
      በተረፈ ውይይቱን የከፈትኩበት ዋና ምክንያት የደቂቀ ኤልያስ አፈ ጉባኤ የሆነችው ጀማነሽ (በርስዎ አጻጻፍ አቦነሽ) ያስተላለፈችውን ግማሽ መልዕክት ደግፈው ፣ ቤተ ክርስቲያን አስተምራ ፣ ባርካ ማዕረግ የሰጠችውን የዲያቆን ዳንኤልን ገለጻ በሙሉ በመቃወምዎ ፣ የነርሱው መሥራችና አባል መስለውኝ ነው ፡፡ በሂደት ግን ኦርቶዶክስና ርትእት የሚሉ ቃሎችን በመጠቀምዎ ጭነቱ ቀለል ብሎልኛል ፡፡ በእርስዎ ሰበብም ፈላሻ ሙራ ምን ማለት እንደሆነ ተምሬአለሁ ፡፡ እኔ አገራችንን ትተው በመሄዳቸውና ዜግነት በመቀየራቸው በማዘኔ ስለነርሱ ጉዳይ አንብቤ አላውቅም ነበር ፡፡ የዘር መድልዎ ተፈጸመባቸው የሚል ነገር በቅርቡ አንብቤ ፣ በመጥቆራቸው አሞራ ሊሏቸው ፈልገው በዕብራይስጥ ሙራ ያሏቸው መስሎኝ ነበር ፡፡ አሁን ግን በርስዎ ግፊት የተሻሻለው እውቀት “ፈላሻ ሙራ ማለት በእናታቸው ወገን የአይሁድ ዘር ያላቸው ወይም አለን የሚሉ በእምነታቸው ግን እንደ አይሁድ ያልሆኑ” ማለት ነው ይላልና ገፋፍተው ስላስተማሩኝ አመሰግናለሁ ፡፡

      ሌላው ኤልያስ መጣ ባዮች “ምጽዓትን ናፋቂዎች” መስለውኛልና ፣ እነርሱን ተከትሎ ቤተ ክርስቲያን የዓለም ፍጻሜ ጊዜ ላይ ነን ብላ ሱባኤ ያላወጀችውን ፣ እኛ በነፍስ ወከፍ የመሰለንን እንደፈለገን እየተረጎምን ተሸብረን ሌላውን ባናሸብር መልካም ነው ማለትም እወዳለሁ ፡፡

      የስንብት ጥያቄዬ
      በቤተ ክርስቲያናችን ትምህርት “እሥራኤል ዘስጋ” እና “እሥራኤል ዘነፍስ” የሚሉት ቃላቶች ምንን የሚያመለክቱ ይመስልዎታል?

      አመሰግናለሁ

      Delete
    15. ሰላም፡ ጤና ይስጥልኝ እንደምን ዋላችሁ።

      እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን።

      የአይጥ ምስክሯ ድንቢጥ እንደሚባለው “ም” ደግሞ ሐሳዊያነ መሢሕን (ፕሮቴስታንትን) ለመደገፍ የሚያቀርቧቸው ምስክሮች ፕሮቴስታንቶችን ወይም ተሃድሶዎችን ነው። አባ እገሌ እንዳሉት ብለው በተዋሕዶ ስም የሚያወናብዱ ሐሳዊ መሢሕ (ፕሮቴስታንት) ለምስክር ያቀርቡልናል። ሊንክ ብለው ደግሞ ዞሮ ዞሮ መዳረሻው ተሃድሶና ፕሮቴስታንት የሆነ ሊንክ ይሰጡናል። ሐሳዊያነ መሢሕ (ፕሮቴስታንት) ያልገቡበት ቦታ የለም። ቅዱስ መጽሐፍም እንዳስጠነቀቀ የተመረጡትን ሁሉ እንስከሚያስቱ ድረስ ዓለምን በሙሉ የረከሰውን የወይን ጠጅ አጠጥተው አስክረዋል። እርስዎም የመጽሐፍ ቅዱስ ማህበር መዝገበ ቃላት እንደሚለው ይሉናል - ልክ ፕሮቴስታንቶች እንደሌሉበት። በተቀደሰው ቦታ (አንድም መጽሐፍ ቅዱስ፣ አንድም ቤተክርስቲያን፣ አንድም ስመ እስራኤል) የረከሰው (ሐሳዊ መሢሕ ፕሮቴስታንት) ተርጓሚ ሆኖ ቀርቧል። እነዚህም ሐሳዊያነ መሢሕ (ፕሮቴስታንት) እስራኤል ማለት ቀያፋ እንጂ ክርስቶስ አይደለም ይላሉ። የአስቆሮቱ ይሁዳ እንጂ ቅዱስ ጴጥሮስ አይደለም ይሉናል። አይናችን በጥፋት እርኩሰት ላይ እንዲሆን እና ከክርስቶስ እንድንለይ እስራኤልን ተመልከቱ በሳይንስ ተራቋል፣ አቶሚክ ቦምብም አለው መሪው ናታንያሁ ይባላል እሱን የነካ የዶጋ አመድ ይሆናል ይሉናል። ለነዚህ አለይሁድ ነን ባዮች ሲሉም አገራችን (ኃይማኖታችን) እንዳልነበረ አድርገዋታል። እኛ ግን እስራኤል ተዋህዶን ተመልከቱ መሪዋ ክርስቶስ ይባላል እሷን የነካ ሃያሉ አምላክ ይገስፀዋል እንላለን። ደግሞም ይመልከቱ ኢትዮጵያን (ኃይማኖቷን ተዋህዶን) የነካውን ሁሉ እግዚአብሔር አምላክ እንዴት ሲገስጸው እንደኖረ። በቅርቡ እንኳን እነ ሲሪያን፣ እነ ኢራቅን፣ እነ ግብጽን ይመልከቱ። የናንተና የኛ የድንግል ማርያም ወገኖች ልዩነት ይህ ነው። አምላክ እግዚአብሔር እድሜ ከሰጥዎትም እስራኤል ናታንያሁ ወይንስ ክርስቶስ - ማን እንደሆነ ለይተው ያውቃሉ።

      ታላቁን የእግዚአብሔር ሊቅ አለቃ አያሌውን የሚሳደቡትን ኃሣዊ መሲሕ አባ እገሌዎንማ ሌላ ምን እላለሁ እግዚአብሔር ይገስጽ። አባ እገሌዎ ዲያቆን ዳንኤልን እና ወንድሞቹን ይሄ ሻኛውን አሳብጦ አባቶችን (እነ “የውጭ ሲኖዶስ” አባ መልከጸዴቅን ማለታቸው ነበር) የሚተች እያሉ አፋቸውን ሲከፍቱበት አልነበረምን? ማህበረ ቅዱሳንንስ “ማህበረ አጋንንት” እያሉ አሜሪካን አገር በየሲቲው እየዞሩ አፋቸውን ሲከፍቱበት እርስዎ አላዩም? ምንው የዲያቆን ዳንኤል ወዳጅ ለመምሰል ቃጣዎት? ነው ወይስ እየመረጡ ነው የሚያስተጋቡት? ይልቁንስ አባ እገሌዎ እርስዎ እራስዎ ካልሆኑ ባስኳይ ከሳቸው እንግዳና ከኃይማኖት የሚያስወጣ ትምህርት ይራቁና አባቶቻችን የተውልንን የቀደመችውን መንገድ የተዋሕዶን ትምህርት ይመልከቱ። አባቶቻችን ትርጓሜ መጻህፍትን ሲተውልን ፓሪሞድ የለበሰች ሎጋ እና አዳልት ሙቪ አያዩ አልነበረም። በጾም በጸሎትና በለቅሶ እግዚአብሔርን ለምነው ያገኙት ነው። ለነፍስዎ የአባቶቻችን ይጠቅምዎታል። አይ ለኔ የሚሻሉኝ ዘማዊና ዘማናዊ ፕሮቴስታንቶች የሚተረጉሙት ነው ካሉ ደግሞ ምርጫው የርስዎ ነው።

      እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን።
      ኃይለሚካኤል

      Delete
    16. ጌታዬ ነገሬ እያበሰለዎት የመጣ መሰለኝ ፡፡ የቃላትዎ ቃና ተቀይሯል ፡፡ አይጥ ፣ ድንቢጥ ማለት ከጀመሩ ከነትርጉምዎ በሰላም ይክረሙልኝ ፡፡ ከመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ቢያስተምሩኝ በማለት ጥያቄ ባቀርብልዎት ፣ ሰዎችን እያመልክንና ለጥብቅና የቆምን ያለ ይመስል ዙሪያ ገባውን ከፖለቲከኛ እስከ ሃይማኖተኛ ደረደሩ ፡፡ አላውቀውም ቀላል መልስ ነበር ፡፡ ዲያቆኑ ካስረዳው አንዲት ሴትዮ ያሉትን የመረጡበት ምክንያት በራሱ ግልጽ አልነበረም ፤ ከግል ጥላቻ ፣ የማኀበረ ቅዱሳን አባል ስለሚባል ፣ አልገባኝም ፡፡ አባ እገሌ እያሉ ስም ለመጥራት እንኳን ያልደፈሯቸውን ደግሞ ከአለቃ አያሌው ጋር እያሉ ደጋገሙብኝ ፤ ማስታረቅ የሚቻል ቢሆን በሠራሁ ደስ ባለኝ ፣ እግዚአብሔር ስለሚወደው ፤ ነገር ግን ያ እንደማይቻል ያውቁት ይመስለኛል ፡፡ ለብቀላ ፈልገዋቸው ከሆነ ግን የእግዚአብሔር መንገድ አይደለም እልዎታለሁ ፡፡

      እንግዲህ መጽሐፍ ቅዱስ ራሱ በራሱ አብራርቶና ተርጉሞ የሚያስረዳውን አልቀበል ብለው ነው ቆላና ደጋ የሚሉብኝ (ስሙን ቀይሮ መዝገበ ቃላት ስለተባለ እንጅ መግለጫው የመጽሐፍ ቅዱስ ቃልን ነው ያስቀመጠው) ፡፡ የደነቀኝ ነገር ደግሞ ከሌሎች ጋር ስወያይ አንተ ማኀበረ ቅዱሳን ነህ ፣ ፍቅረ ማርያም ነህ የሚሉኝን ፣ ርስዎ ደግሞ ኘሮቴስታንትና ተሐድሶ የሚለውን ጨምረውልኛል ፡፡ ስለዚህ እኔ ሁሉንም ነኝ ማለት ይሆናል ከእስማኤላዊነት በስተቀር ፡፡

      ከውይይታችን እንደተረዳሁት መጽሐፍን በትክክል እየጠቀሱ ሊያስተምሩና ሊያሳምኑኝ አልቻሉም ብዬ ደምድሜአለሁ ፡፡ በመሃል ማስረጃ ያሏቸውና ያቀረቧቸው በሙሉ ፣ ሃይማኖትን በአመክንዮ ለመተርጐም የሚታገሉ ሁነው ነው ያገኘሁዋቸው ፡፡ እግዚአብሔር አይወግንምና የግድ እኛም እሥራኤል መባል እንችላለን ፣ ይገባናልም ፣ ደግሞም ነን ፡፡ ይሄን የመጽሐፍ ትርጉምና ማስረጃ ሳይሆን አመክንዮ ነው የምለው ፡፡

      በተረፈ የሚያጠኑት የአንደምታ ትርጓሜ ራሱ ማቴዎስ 24፡5 (ገጽ 169) ላይ ስለ ሐሳዊ መሲህ ምሳሌ አድርጎ የጠቀሰው ፣ “በአማራ መንግሥት ጊዜ አንዱ ዘክርስቶስ ይሉኛል ብሎ ተነስቶ ፣ ሰባት መቶ የሚያህል ሰዎች ተከትለውት ነበር ፡፡ ኋላ ግን ህዝቡ ርሱንም ሰቀለው ፤ እነርሱንም ደግሞ ገደላቸው ፣ በዚህም ሰማዕታት ዘክርስቶስ ተብለዋል በማለት ከነምሳሌው ኢየሱስ ነኝ የሚል ግለሰብ ነው በማለት አስቀምጦልዎት እያለ ፣ አይ ሐሳዊ መሲህያን ማለት ወደ ግማሽ ቢሊየን የሚጠጋው ፣ ክርስቶስን በማመን ብቻ እድናለሁ ብሎ የራሱን መንገድ የያዘው ህዝብ ነው እያሉኝ ነው እዚህ ደረጃ የደረሱት ፡፡ ከቃሉ ውጭ እንዲህ መባላቸውንም አላምንበትም ፡፡

      ሁሉንም የወንጌል ትንቢት ደግሞ የሚያያይዙት ከአገራችን ሁኔታ ጋር ነው ፤ ሌላው ዓለምን ለማን አደራ ሰጥተውት እንደሆነ አልተገለጸም ፡፡ ቀደም በአውሮፖ መሲህ ነኝ ብሎ የተነሳ አይሁዳዊ እንደነበረና ብዙ ተከታይም እንደነበረው ፣ ነገር ግን በሂደት በራሱ ጊዜ እንደተነፈሰ ታሪክ አለ ፡፡ እንዲያ ዓይነቱን ስንኳ ፈልገው አፈላልገው ከኘሮቴስታንቱ መሃል ኢየሱስ ነኝ የሚለውን ሰው ፣ ቦታውንና ተአምራቱን ይጥቀሱ ብልም መልስ የለዎትም ፡፡ አሁን በመጨረሻው ደግሞ የዓለምን የፖለቲካ ሁኔታ እያቆላለፉና እየተረተሩት ስመለከት ፣ የነቢይነት (ሌላ ቃል ነበረ የሚባለው) ነገርም እየሞከሩ መስሎኛል ፤ እኔ ለራሴ ግን እንደርስዎ አልረዳውም ፡፡ አገራችንን እግዚአብሔር እንደሚጠብቃት ጥርጥር የለኝም ፡፡ እርስዎ እንደሚሉት ግን ህጻናትና እናቶችን ለቦምብና ለጥይት ሰለባ እያደረገ አይደለም የሚታደጋት ፡፡

      ለማጠቃለል በእኔ ምክንያት አንስተው የጣሏቸውን አባቶች ፣ በጉዳያችን ያልተሳተፉ ነገር ግን በበጎም ሆነ በክፉ የተነሱ ሰላማዊ ወገኖችን ፣ ቤተ ክርስቲያን ሳትሆን በግልዎ ስም የሰጧቸውን (ተሐድሶ ያሏቸውን) ሁሉ በጨዋ ቃል ቢሰናበቷቸው እጠይቅዎታለሁ ፡፡ እኔም በመግለጫዬ የተቀየመና ያዘነብኝ ካለ ይቅርታ አድርጉልኝ እላለሁ ፡፡

      ሰላም ሁኑልኝ

      Delete
    17. ሰላም ጤና ይስጥልኝ ፥ እንደምን ዋላችሁ?

      በአውሮፓ መሲሕ ነኝ ብሎ የተነሳ ሰው ከነበረ፣ ወደፊት ደግሞ የሚመጣ ሌላ መሲሕ ነኝ ባይ ካለና በእርስዎ አስተሳሰብ ደግሞ ኃሳዊ መሢሕ አንድ ግለሰብ ከሆነ በዚህ አሁን ባቀረቡት ምሳሌ ኃሳዊ መሢሕ ከአንድ በላይ ሆነ እኮ። የእርስዎን አመክንዮ አወዳደቅ እስካሁን አላዩትም? ያዳገትዎት መሰለኝ - እስኪ እንደገና ላቅርብልዎት።

      ከዚህ ቀደም “እኔ ኢየሱስ ነኝ” ብሎ የመጣ ሰው ከነበረ እና ወደፊት ደግሞ ሌላ “እኔ ኢየሱስ ነኝ” ብሎ የሚመጣ ሲኖር ከአንድ በላይ ሆነ ማለት ነው። አንድ ሲደመር አንድ ሁለት አይሆንም? ሁለትም ሰዎች፣ ሦስትም ሰዎች፣ አንድ ሚሊዮንም ሰዎች ሁሉም ከአንድ ግለሰብ ይለያሉ። ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ ኃሳዊ መሢህ ሲል አንድ ግለሰብ ማለቱ አይደለም። ሌላው የግድ ኃሳዊው “ኢያሱስ እኔ ነኝ” የሚል ቃል ይጠቀማል ማለት አይደለም። ጣኦቱን ኃሳውያን እግዚአብሔር ነው ወይም እንደ እግዚአብሔር ነው ብለው ከፍ ከፍ ያደርጉታል ማለት ነው።

      እስራኤል ዘሥጋ እና እስራኤል ዘነፍስ ብለው ለጠየቁት ጥያቄ አጭር መልስ - እስራኤል ዘስጋ አይሁድ ነበሩ፣ እስራኤል ዘነፍስ ደግሞ ክርስቲያኖች ነን። እስራኤል ዘስጋና እስራኤል ዘነፍስ ባንድ ዘመን አብረው አይኖሩም ምክንያቱም በአንድ ጊዜ ሁለት ቃል ኪዳን የለምና። እግዚአብሔር ከአብርሃም ልጆች ጋር ያደረገውን ቃልኪዳን በአዲሱ ቃልኪዳን በአዲስ ኪዳን አድሶታል። እግዚአብሔር አዲስ ቃል ኪዳን ሰርቶ ወደኋላ አይመለስም። ክርስቲያን አይሁድ፣ ክርስቲያን አህዛብ ይባላል እንዴ? በአዲሱ ቃል ኪዳን አይሁድ የለም፣ ጌታ የለም፣ ባሪያ የለም። ክርስቲያን ብቻ ነው ያለው። አዲሱ እስራኤል እነሆ ክርስትና ነው። እስራኤል ዘሥጋ የሥጋ እንስሳ ይሰዉ ነበረ። በዛ ግን መዳን አልነበረም። የእስራኤል ዘነፍስ መስዋእት ክርስቶስ ነው። በዚህ መዳን አለ። በአንድ በኩል የእንስሳ መስዋእት እያቀረቡ በሌላ በኩል ክርስቶስ አለን እንደማይሉ ሁሉ እስራኤል ዘሥጋ እና እስራኤል ዘነፍስ ባንድ ላይ አሉ አይባልም። በእስራኤል ዘነፍስ ዘመን እስራኤል ዘስጋ የሚባል ነገር የለም። የታሪክ ምሳሌ ለመጥቀስ ካልሆነ በቀር።

      የወንጌል ትንቢትን ከሃገራችን ጋር ያያዘው መድኃኔ ዓለም እንጂ እኔ አይደለሁም። ኢሳይያስ ፲፰ን፣ መዝሙር ፸፬፥ ፲፬ን፣ ራእይ ፲፪፥፲፫ን ያንብቡ።

      ምስጋና ለመድኃኔ ዓለም።
      ኃይለሚካኤል።

      Delete
    18. ሀ/ ወገኖች ሲጫወቱ "ይቺን ለኛ ጥሬን ለጌኛ" ይላሉ ፡፡ ምነው አመክንዮ ብለው ቁጥር ባያስተምሩኝ ምናለበት ፡፡ ወንጌሉን መጀመሪያ መች በቅጡ አነበቡልኝና የድምር ሂሳብ ያስተምሩኛል ፡፡

      "ብዙዎች። እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉና፤ ብዙዎችንም ያስታሉ።" ማቴ 24፡5 ፤ ማር 13፡6 ፤ ሉቃ 21፡8 ይልልዎታል ፡፡ ለማንበብ መነጽር የሚያስፈልግዎ ከሆነ ይጠቀሙ እንጅ ቃሉ በሦስቱም ወንጌሎች የሚጀምረው “ብዙዎች” በሚል ቃል እንጅ በአንድ ሐሳዊ ሰው ብቻ አይልዎትም ፡፡ አንድ ትናንት ከመጣ ፣ ነገ ሌላ ሐሳዊ ክርስቶስ ፣ ከዛ ደግሞ አሁንም ጊዜ ጠብቆ ሌላው እኔ ክርስቶስ ነኝ ብሎ ሲነሳ ፤ እውን ብለው የሚያምኑ ፣ የሚከተሉና የሚሳሳቱ ይኖራሉ ነው የሚለው እንጅ አንድ ከመጣ የመጨረሻ ነው አይለውም ፡፡

      እንዲያ ቢሆንልዎትማ የሊቃውንቱ የአንደምታ መጽሐፍም ዘክርስቶስ መጥቶ ነበር ባላለዎትና አንድ ግለሰብ መሆኑንና ሌላውን እንድንጠብቅ በማለት ባላብራራ ነበር ፡፡ ሐሳዊ መሲሕ አንድ ብቻ ቢሆን ደግሞ ፣ ርሱም በዘክርስቶስ መገለጥ ተዘግቷል ባለን ነበር ፡፡ ስለዚህ እኔ ኢየሱስ ነኝ እያሉ የሚመጡትን ለይተን እንድንጠነቀቅ ጌታ አስተምሮናልና ላለመሳሳት እንጠነቃቀለን ፡፡ የርሶ ትርጉም ትክክል ተብሎ ሊቀበሉት ይገባ የነበረው ፤ ማርቲን ሉተር እኔ ኢየሱስ ነኝ ብሎ ቢያስተምር ነበር ፡፡ ርሱ ግን ተሳስቶ እንኳን አላለም ፡፡ ተከታዮቹም ስሙን እንኳ ሲጠሩ አይሰሙም ፡፡

      ስለዚህም እልዎታለሁ ፡- “የተሳሳቱ ወገኖች ፣ ስህተታቸውን እንዲያርሙና እንዲመለሱ ፣ የሚያስፈልገውን መሠረታዊ ሃይማኖት በትክክል ማስረዳትና ማስተማር እንጅ ፣ በጭፍን ትርጉም መኰነኑና ማግለሉ ምንም ጥቅምና ትርፍ አያስገኝልዎትም ፡፡ ምክንያቱም ትርጉምዎ ውሸትና ከቁጭት የመነጨ መሆኑን ሌሎች ወንጌላውያን ነን የሚሉት ሳይሆኑ ፣ እኔ እንኳን በደከመች ዕውቀት እያየሁልዎት ስለሆነ ፡፡

      ለ/ ከመጽሐፍ ቃል ደግሞ እስራኤል ሆይ፥ ስማ፤
      - ለአምላክህ ለእግዚአብሔር አንተ ቅዱስ ሕዝብ ነህና በምድር ፊት ከሚኖሩ አሕዛብ ሁሉ ይልቅ ለእርሱ ለራሱ ሕዝብ ትሆንለት ዘንድ አምላክህ እግዚአብሔር መረጠህ። ዘዳ 7፡6
      - ብቻ እግዚአብሔር ስለ አባቶችህ ደስ ብሎታል፥ እነርሱንም ወድዶአል ከእነርሱም በኋላ እናንተን ዘራቸውን እንደ ዛሬው ሁሉ ከአሕዛብ ሁሉ መካከል መረጠ። ዘዳ 1ዐ፡15
      - እግዚአብሔር አምላኩ የሚሆንለት ሕዝብ ምስጉን ነው፥ እርሱ ለርስቱ የመረጠው ሕዝብ። መዝ 33፡12

      እንግዲህ እግዚአብሔር የመረጣቸውንና የባረካቸውን ህዝቦች ነው ፣ ያለ አንዳች አለማፈር ለማውገዝ ሲታገሉ የሰነበቱት ፡፡ እኔ ግን በሮሜ 8፡33 የሠፈረውን ቃል እንዲያነቡና ልቦና እንዲገዙ አዛለሁ ፡፡ አንዳች ሳይፈሩ ከእግዚአብሔርም በላይ አልፈው ከዘመናት በኋላ የሚሆነውን የተረዱ መስለው ነው የሚጽፉልኝ ፡፡ እኔ ደግሞ እንኳንስ የሌሎችን የራስዎን እምነትና ሃይማኖት ከአመት በኋላ ፣ ከአምስት በኋላ ምን ሊሆን እንደሚችል አያውቁም እላለሁ ፡፡ እግዚአብሔር ግን ገና ከማህጸን ሳይወጡ የት እንደሚደርሱ አንብቦዎታልና ያውቃል ፡፡ አይሁድም በሏቸው እሥራኤል ወደፊት በምን መንገድ ምን እንደሚሆኑ መናገር ከሰዎች የመጠበብ ችሎታ ውጭ ነውና ለጊዜው ትንሽ በረድ ይበሉ ፡፡ የዓመጽ ስሜትዎንም ቢችሉ ይቆጣጠሩት ፤ እንደ ክርስቲያንነትዎ መጠንም የወደቀ ወገን እንኳን ቢያገኙ ለማንሳትና ተስፋ ለመስጠት ይጣሩ ፡፡

      ቢለቅዎት ይህችንም ረጋ ብለው ያንብቡ ፤ የመዳናችን ምክንያት አይሁዶች ናቸው እልዎታለሁ፡፡ ምክንያቶቼም
      1. ድንግል ማርያም በቅድስናና በንጽሕና ከነርሱ ወገን ባትገኝ ኖሮ ጌታችን የሚዋሐደው ሥጋ ስለማይኖር ቀድሞውኑ ሰው አይሆንም ነበር ፡፡
      2. ቀጥለውም ኢየሱስን ያለፍርድ ባይገድሉት ኖሮ ፣ ካሳችን አይከፈልም ነበርና ድኀነታችን ዘበት ነበረች

      ታድያ ይኸውልዎ ክርስትናችን እንዲህ ባለውለታዎ ለሆኑ ወገኖች ብቻ ሳይሆን ፣ ለጠላት እንኳን ቢሆን ሲበድሉ ይቅር በላቸው እያልን መጸለይ እንደሚገባ ነው የምታስተምረን ፡፡ ጌታችንም ሲያስተምረን ፤ እየቸነከሩትና እየወጉት ሳለ ምህረትን ጠይቆላቸዋልና ፡፡ ድቤ ተመታ ብለውም ነጋሪት ለማስጐሰም አይዳዳዎ ፡፡ በፍቅር ሁሉንም እናሸንፋለን ፡፡

      ሐ/ እስራኤል የሚለው ቃል በመጽሐፍ የተለያየ አገባብ አለው ፡፡ ክርስቲያን ማለት እንዳልሆነ የሚያመለክቱትን ጥቂት ኃይለ ቃሎች
      - ከእስራኤልም ልጆች ብዙዎችን ወደ ጌታ ወደ አምላካቸው ይመልሳል። ሉቃ 1፡16
      - ሕፃኑም አደገ በመንፈስም ጠነከረ፥ ለእስራኤልም እስከ ታየበት ቀን ድረስ በምድረ በዳ ኖረ። ሉቃ 1፡8ዐ
      - ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው፦ አንተ የእስራኤል መምህር ስትሆን ይህን አታውቅምን? ዮሐ 3፡1ዐ
      - የእስራኤል ሰዎች ሆይ፥ ይህን ቃል ስሙ፤ ራሳችሁ እንደምታውቁ፥ የናዝሬቱ ኢየሱስ እግዚአብሔር በመካከላችሁ በእርሱ በኩል ባደረገው ተአምራትና በድንቆች በምልክቶችም ሥራ 2፡22
      - እናንተ በሰቀላችሁት እግዚአብሔርም ከሙታን ባስነሣው በናዝሬቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ይህ ደኅና ሆኖ በፊታችሁ እንደ ቆመ፥ ለእናንተ ለሁላችሁ ለእስራኤልም ሕዝብ ሁሉ የታወቀ ይሁን። ሥራ 4፡1ዐ

      Delete
    19. “ይቺን ለኛ ጥሬን ለጌኛ” ሲሉኝ ወደማውቃት ሠፈር መጣህልኝ ማለትዎ ነው? ከሆነ መልካም። ችግሩ አውቃታለሁ ያሏትንም ሠፈር የማያውቋት መሆኑ ነው። ቅን ልብ ቢኖርዎት ኖሮ እንዴት ደስ ባለኝ። ቅን ልብ ማጣት እንዲህ እያደር ጥሬ ያደርጋል። ቅን ልብ ያሳጣዎት ምክንያቱ ምን እንደሆነ ይገባኛል። አንድ በጀርመን አገር ይኖር የነበረ ማርቲን ሉተር የሚባል ሰው ካባቱ ጋር ባለው ጥላቻ ምክንያት እራሱን ሊገድል ሲል በጀርመን ይኖሩ የነበሩ የካቶሊክ መነኮሳት ያገኙትና ወደ ገዳማቸው ወስደው፣ አስተምረው መነኩሴ አደረጉት። መነኩሴ ሆኖ ሲኖር የሥጋዊ ፍላጎቱ እየበረታበት መጣና ምንኩስናውን ሊያፈርስ ፈለገ። ነገር ግን በካቶሊክ ቀኖና ምንኩስናን ማፍረስ ጥፋት እንደሆነ ስላየ ከንስሃ ይልቅ እራሱን ጥፋተኛ የማያደርግበትን መንገድ ሻተ። ለራሱ ችግር ደብቆ መጠለያ የሚያገኝበት ሁለንተናዊ ፍልስፍና ቀመረና ጥፋተኛ የካቶሊክ ቀኖና ነው ብሎ ወደ ዘጠና አምስት የሚሆኑ የክስ መግለጫዎችን በካቶሊክ ቀኖና ላይ አውጆ እንዲያውም በገዳም ውስጥ የሚኖሩ ብዙዎችን በማሳሳት ከገዳም አስወጥቶ ለኃጢአት ዳረጋቸው። እርስዎም ማርቲን ሉተር የገባበት የአእምሮ ማጥ ውስጥ እንደገቡ ከአንሳስዎና ከአኪያሄድዎ ማየት ይቻላል። ምናልባት በኑዮርክ ወይም በአትላንታ ወይም በሎሳንጀለስ ወዘተ የተሰደድን ሲኖዶስ የተዋህዶ ካህን ነን ከሚሉት ውስጥ ሊሆኑ ይችላሉ። ዜግነትዎን በመሃላ ቀይረው ከሆነ ይህ የሚሰጡት አስተያየት ሁሉ ከዛች ሥራዎ - ከመሠረተ እንጭጯ “የራስ ሲቆረስ” (ፈረንጆች ኮንፍሊክት ኦፍ ኢንተርስት ከሚሏት) ማጥ የመነጨች እንደሆነች መገመት አያዳግትም። ማርቲን ሉተር የካቶሊክ መነኮሳትን ከገዳማዊ ኑሮ ውጡ፤ ወደ ከተማ ግቡ እንዳለ ሁሉ እርስዎ ደግሞ በራስዎ ቋንቋ ከጽዮን ውጡ ወደ ባቢሎን ግቡ እያሉን ነው። አባ እገሌዎም ያሉት ይሀንኑ ነበር። “ውላጤ ዘእንበለ ውላጤ” ወይም ኦርቶዶክስ ተዋህዶ መባላችን ሳይለወጥ ማንነታችን ተለውጦ እንደፕሮቴስታንቶች እንሁን እያሉ በየስቴቱ እየዞሩ ሲያስተምሩ ነበር። አሁን ማጣፊያው ሲያጥርባቸው ከዚህ አይን ካወጣው የሃሰት ትምህርታቸው ሽሽት የጀመሩ ይመስላል።

      ለማንኛውም በዝርዝር ካርቀረቡት ውስጥ የእርስዎን አስተያየት የሚያግዝ አንድም ነጥብ የለም። የብሉይ ኪዳን ጥቅሶች የርስዎን አስተሳሰብ ለመደገፍ ሊጠቀሙባቸው አይችሉም ምክንያቱም በብሉይ ኪዳን አይሁድ እስራእል ዘሥጋ ነበሩ። ይህን አምጥተው ለማሳመኛነት ማስረጃ ብለው ለማቅረብ መሞከርዎ አስተያየትዎ እንደተሳሳተ መረዳትዎን ነገር ግን ተሳሳትኩ ብለው ለመቀበል አለመፈለግዎን ያሳያል። የጨነቀው እርጉዝ ያገባል እንደሚባለው።

      ያ ሳያንስ ከአዲስ ኪዳን ጥቅስ ጠቅሰው የሃሰት ምስክር አድርገው ሊጠቀሙበት ሞከሩ። ሉቃስ ፲፮ ን በመጥቀስ “ከእስራኤልም ልጆች ብዙዎችን ወደ ጌታ ወደ አምላካቸው ይመልሳል” የሚለውን በመያዝ በሃሰት ይሁዳን እንጂ ክርስትናን እስራኤል አላለም ብለው ሊያምታቱን ሞከሩ። እንዲህ አይነቱ ምግባር ከስርቆት የማያንስ በእግዚአብሔርም ዘንድ ሆነ በሰው ጸያፍ የሆነ ምግባር ነው። ይህን ቃል የእግዚአብሔር መልአክ ለካህኑ ለዘካርያስ የነገረው ገና ክርስቶስ ሳይወለድ ስለዮኃንስ መጥምቁ መወለድ ለማብሰር ነበር። እግዚአብሔር በዚህ ጊዜ ገና አዲስ ቃል ኪዳን አላደረገም ነበር። ኢየሱስ ክርስቶስ ገና አልተሰቀለም ፣ ገና ሞትን ድል አድርጎም አላረገም ነበር። እርስዎ ግን በቃሉ ክርስትናን የማቃለል ወንጀል ፈጸሙበት። መልካም አይደለም። ሉቃስ ፩፥፰ ፣ ዮኃንስ ፫፥፲ንም የጠቀሱት በተመሳሳይ ሁኔታ ነው። የሃዋርያት ሥራ ፪፥፳፪ በበዓለ ኀምሳ ለተሰበሰቡ ሁሉም የክርስቶስን ተዓምር እንዲያስተውሉ በሱም መንገድ እንዲሄዱ ቅዱስ ጴጥሮስ የተናገረው ነው። ይቀጥላል።

      Delete
    20. አንድም የርስዎን አስተያየት የሚደግፍ ከቅዱሳን መጻህፍት አላገኙም፣ አያገኙምም። በተለይ ደግሞ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ የአዲስ ኪዳን ትርጓሜ አይሁድ በፍርድ ቀን እንደሚጠፉ እስራኤል (ክርስቲያኖች) ግን እንደሚድኑ ይናገራል። ክርስቲያንን ህዝበ እስራኤል አይሁድን ደግሞ አይሁድ ብሎ አቅርቧል። ከጥንት ክክርስቶስ ስቅለት ወዲህ ባለው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ታሪክ ውስጥ አይሁዲነት እርጉምነት እንጂ ሌላ ሆኖ አያገኙትም። እስራኤልነት ማለት ክርስቲያንነት ብቻ ነው። ቅዱስ መጽሐፍም እንድሚከተለው ይህን ጉዳይ ከመሠረቱ ያስተምረናል።

      እስራኤልነት በክርስትና የተሻረ ሳይሆን እንዲያውም ክርስቲያንነት እስራኤልነት የሚቀጥልበት ብቸኛው መንገድ እንደሆነ ቅዱስ ጴጥሮስ ለሮማውያን ሲያበስር እንዲህ አለ፥ ሮሜ ም ፱ ቁ ፮ ፥ ከእስራኤል የሚወለዱ ሁሉ እስራኤል አይደሉምና፤ የአብርሃምም ዘር ስለሆኑ ሁላቸው ልጆች አይደሉም።

      ቅዱስ ጳውሎስም ለገላትያ ሰዎች እስራኤል ዘሥጋ (ኦሪት) ወደ እስራኤል ዘነፍስ (ክርስትና) የሚያደርስ ሞግዚት እንጂ በክርስትና ላይ አጎልብቶ የሚቀጥል አለመሆኑን እንደሚከተለው ያበስራል።

      ወደ ገላትያ ሰዎች ም፫፣ ከ፳፩ እስከ መጨረሻ፥ እምነትም ሳይመጣ ሊገለጥ ላለው እምነት ተዘግተን ከሕግ በታች እንጠበቅ ነበር። እንደዚህ በእምነት እንጸድቅ ዘንድ ሕግ ወደ ክርስቶስ የሚያመጣ ሞግዚታችን ሆኖአል፤ እምነት ግን መጥቶአልና ከእንግዲህ ወዲህ ከሞግዚት በታች አይደለንም። በእምነት በኩል ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጆች ናችሁና፤ ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና። አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፥ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፥ ወንድም ሴትም የለም፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና። እናንተም የክርስቶስ ከሆናችሁ እንኪያስ የአብርሃም ዘር እንደ ተስፋውም ቃል ወራሾች ናችሁ።

      ከፕሮተስታንቶች ተውሰው አይሁድ ወደፊት ክርስቲያን ይሆናሉ፣ ያን በመጠበቅ የእስራኤልነትን ማእረግ ይዘው ይቆያሉ በሚለው ዝንባሌዎ በጣም ሊታዘንልዎት ይገባል። የክርስቶስ ነገር ምንም እኮ አልገባዎትም። ክርስቶስ እኮ እምነትን እንጂ ሥጋን አይሻም። ስንት ሚሊዮን አይሁድ እየተሰበከላቸው ክርስቶስን ሳያምኑ እንዳለፉ አያውቁምን? ክርስቶስ ያለፉትን አይሁድ ካላለፉት አይሁድ የሚለይበት ምን የሥጋ ልዩነት ቢኖራቸው ነው? የወደፊቱን የሚጠብቅ ከሆነ ያለፉትን ለምን ጣላቸው? ወደፊት ክርስቲያን የሚሆኑትስ አይሁድ-ክርስቲያን ሊባሉ ነው? ይህን ደግሞ መጽሐፍ በቀጥታ ከለከልዎት፥ እንዲህም አለ፥ ክርስትያን ሆኖ አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም አልዎት። አዩ የትውስት ነገር እንዲህ አእምሮን ለኪሳራ አጋልጦ ይሰጣል።

      “የመዳናችን ምክንያት አይሁዶች ናቸው” እና እስራኤል እንበላቸው የሚሉት ምንም አስተውሎ የሌለው የቸለልተኝነት ወግ ነው። ክርስቶስ የተወለደው እኮ ከአይሁድ ነው። ኢትዮጵያውያንም እኮ አይሁዶች ነበርን። ነገር ግን ጌታችን መድኃኔታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም ሆነ ብጽእት ቅድስት ድንግል ማርያምንም ሆነ እኛን የአሥራት ልጆቿን ከአሁኑ ጊዜ አይሁድ ነን ባዮች የሚለየን ክርስቶስ በሥጋ እንደመጣ፣ በሱም እንደምንድን ማመናችን ነው። አሁን አይሁድ ነን የሚሉት ክርስቶስ በሥጋ እንደመጣ አያምኑም፣ መዳን በክርስቶስ እንደሆነ አያምኑም፣ ብጽእት ቅድስት ድንግል ማርያም እመ እግዚአብሔር እንደሆነች አያምኑም። ስለዚህ እነሱ እስራኤል አይደሉም። እኛ በተዋህዶ የምናምን ክርስቲያኖች ግን እስራኤል ነን። እርስዎም በተዋህዶ ካላመኑና የፕሮቴስታንት እምነት አራማጅ ከሆኑ የእስራኤል ጠላት እንጂ እስራኤልም፣ የእስራኤልም ወገን አይደሉም። እርግጥ ነው ጥሩ ጠቁመዋል ጌታችን መድኃኔታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሆኖ የሚያደርጉትን አያውቁትምና ይቅር በላቸው እንዳለ እኛም የሚያደርጉትን አያውቁትምና ይቅር በላቸው ብለን ልንጸልይላቸው ይገባናል። እንዳሉኝ አደርጋለሁ እግዚአብሔር ይርዳኝ። እውነቱን ያዩ ዘንድ እርስዎን እና እርስዎን የመሰሉትን ዘወትር ከማሳሰብ ደግሞ ፈቀቅ አልልም።

      መድኃኔ ዓለም ይመስገን።
      ኃይለሚካኤል።

      Delete
    21. አንድም የርስዎን አስተያየት የሚደግፍ ከቅዱሳን መጻህፍት አላገኙም፣ አያገኙምም። በተለይ ደግሞ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ የአዲስ ኪዳን ትርጓሜ አይሁድ በፍርድ ቀን እንደሚጠፉ እስራኤል (ክርስቲያኖች) ግን እንደሚድኑ ይናገራል። ክርስቲያንን ህዝበ እስራኤል አይሁድን ደግሞ አይሁድ ብሎ አቅርቧል። ከጥንት ክክርስቶስ ስቅለት ወዲህ ባለው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ታሪክ ውስጥ አይሁዲነት እርጉምነት እንጂ ሌላ ሆኖ አያገኙትም። እስራኤልነት ማለት ክርስቲያንነት ብቻ ነው። ቅዱስ መጽሐፍም እንድሚከተለው ይህን ጉዳይ ከመሠረቱ ያስተምረናል።

      እስራኤልነት በክርስትና የተሻረ ሳይሆን እንዲያውም ክርስቲያንነት እስራኤልነት የሚቀጥልበት ብቸኛው መንገድ እንደሆነ ቅዱስ ጴጥሮስ ለሮማውያን ሲያበስር እንዲህ አለ፥ ሮሜ ም ፱ ቁ ፮ ፥ ከእስራኤል የሚወለዱ ሁሉ እስራኤል አይደሉምና፤ የአብርሃምም ዘር ስለሆኑ ሁላቸው ልጆች አይደሉም።

      ቅዱስ ጳውሎስም ለገላትያ ሰዎች እስራኤል ዘሥጋ (ኦሪት) ወደ እስራኤል ዘነፍስ (ክርስትና) የሚያደርስ ሞግዚት እንጂ በክርስትና ላይ አጎልብቶ የሚቀጥል አለመሆኑን እንደሚከተለው ያበስራል።

      ወደ ገላትያ ሰዎች ም፫፣ ከ፳፩ እስከ መጨረሻ፥ እምነትም ሳይመጣ ሊገለጥ ላለው እምነት ተዘግተን ከሕግ በታች እንጠበቅ ነበር። እንደዚህ በእምነት እንጸድቅ ዘንድ ሕግ ወደ ክርስቶስ የሚያመጣ ሞግዚታችን ሆኖአል፤ እምነት ግን መጥቶአልና ከእንግዲህ ወዲህ ከሞግዚት በታች አይደለንም። በእምነት በኩል ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጆች ናችሁና፤ ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና። አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፥ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፥ ወንድም ሴትም የለም፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና። እናንተም የክርስቶስ ከሆናችሁ እንኪያስ የአብርሃም ዘር እንደ ተስፋውም ቃል ወራሾች ናችሁ።

      ከፕሮተስታንቶች ተውሰው አይሁድ ወደፊት ክርስቲያን ይሆናሉ፣ ያን በመጠበቅ የእስራኤልነትን ማእረግ ይዘው ይቆያሉ በሚለው ዝንባሌዎ በጣም ሊታዘንልዎት ይገባል። የክርስቶስ ነገር ምንም እኮ አልገባዎትም። ክርስቶስ እኮ እምነትን እንጂ ሥጋን አይሻም። ስንት ሚሊዮን አይሁድ እየተሰበከላቸው ክርስቶስን ሳያምኑ እንዳለፉ አያውቁምን? ክርስቶስ ያለፉትን አይሁድ ካላለፉት አይሁድ የሚለይበት ምን የሥጋ ልዩነት ቢኖራቸው ነው? የወደፊቱን የሚጠብቅ ከሆነ ያለፉትን ለምን ጣላቸው? ወደፊት ክርስቲያን የሚሆኑትስ አይሁድ-ክርስቲያን ሊባሉ ነው? ይህን ደግሞ መጽሐፍ በቀጥታ ከለከልዎት፥ እንዲህም አለ፥ ክርስትያን ሆኖ አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም አልዎት። አዩ የትውስት ነገር እንዲህ አእምሮን ለኪሳራ አጋልጦ ይሰጣል።

      “የመዳናችን ምክንያት አይሁዶች ናቸው” እና እስራኤል እንበላቸው የሚሉት ምንም አስተውሎ የሌለው የቸለልተኝነት ወግ ነው። ክርስቶስ የተወለደው እኮ ከአይሁድ ነው። ኢትዮጵያውያንም እኮ አይሁዶች ነበርን። ነገር ግን ጌታችን መድኃኔታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም ሆነ ብጽእት ቅድስት ድንግል ማርያምንም ሆነ እኛን የአሥራት ልጆቿን ከአሁኑ ጊዜ አይሁድ ነን ባዮች የሚለየን ክርስቶስ በሥጋ እንደመጣ፣ በሱም እንደምንድን ማመናችን ነው። አሁን አይሁድ ነን የሚሉት ክርስቶስ በሥጋ እንደመጣ አያምኑም፣ መዳን በክርስቶስ እንደሆነ አያምኑም፣ ብጽእት ቅድስት ድንግል ማርያም እመ እግዚአብሔር እንደሆነች አያምኑም። ስለዚህ እነሱ እስራኤል አይደሉም። እኛ በተዋህዶ የምናምን ክርስቲያኖች ግን እስራኤል ነን። እርስዎም በተዋህዶ ካላመኑና የፕሮቴስታንት እምነት አራማጅ ከሆኑ የእስራኤል ጠላት እንጂ እስራኤልም፣ የእስራኤልም ወገን አይደሉም። እርግጥ ነው ጥሩ ጠቁመዋል ጌታችን መድኃኔታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሆኖ የሚያደርጉትን አያውቁትምና ይቅር በላቸው እንዳለ እኛም የሚያደርጉትን አያውቁትምና ይቅር በላቸው ብለን ልንጸልይላቸው ይገባናል። እንዳሉኝ አደርጋለሁ እግዚአብሔር ይርዳኝ። እውነቱን ያዩ ዘንድ እርስዎን እና እርስዎን የመሰሉትን ዘወትር ከማሳሰብ ደግሞ ፈቀቅ አልልም።

      መድኃኔ ዓለም ይመስገን።
      ኃይለሚካኤል።

      Delete
    22. “አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፥ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፥ ወንድም ሴትም የለም፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና።” ገላ 3፡28

      የሚለው ቃል እርሶ እንደሚሉት ዘራችሁን ቀይራችሁ እሥራኤላዊ ወይም አይሁዳዊ ትባላላችሁ ወይም ትሆናላች አይልም ፡፡ ባለፈው መግለጫ የጠቀስኩልዎትን ይዘው አይሁዳውያን በእግዚአብሔር የተመረጥን ህዝብ ነን ብለው ስለሚመኩ “እስከ አሁንም አብዛኞቹ በዛው መንገድ ስለሆኑ” ፣ ሌሎች ወገኖች ደግሞ አሕዛብ እየተባሉ እየተሚሸማቀቁ ይኖሩ ስለነበሩ ፣ ያንን ሃፍረት ለመግፈፍ ያስተማረው ነው (ጳውሎስ ለአሕዛብ የተላከ ሐዋርያ መሆኑ ተጠቅሷልና) ፡፡ አሁንም ቃሉን በትነው በጥንድ ቢመለከቱት ፣ አይሁዳዊና ግሪካዊ ፣ ባሪያና ጨዋ ፣ ወንድና ሴት (ወንድን የሴት ራስ ስለሚል) በማለት ከፍ ያለንና ዝቅ ያለን ወገን ጠቅሶ ፣ ቀደም የእግዚአብሔር ሰው የሆነና ያልሆነም ቢሆን በክርስቶስ እምነት እስካለው ድረስ ልዩነት የለበትም በማለት የብሉይን ትምክህት ማራቁ ነው ፡፡

      ይኸው መልዕክት በወንጌል በተለያየ ቃልና ሥፍራ ተጠቅሶ እናገኘዋለን ፡፡ አጠቃላይ መልዕክቱ ግን በእምነት ከተገኘን ፣ ሁላችን በክርስቶስ አንድና እኩል ነን ለማለት ነው እንጅ ግሪካዊው እሥራኤላዊ ፣ ኢትዮጵያዊውም አይሁዳዊ ወይም እሥራኤላዊ ይሆናል ማለት አይደለም ፡፡ ሁሎችም አማኞች በአንድነት ክርስቲያን ይባላሉና ፡፡

      - በዮሐንስ ወንጌል ከሠፈረው ከጌታ ትምህርት ፡-
      * 1ዐ፡16 ፤ “ከዚህም በረት ያልሆኑ ሌሎች በጎች አሉኝ፤ እነርሱን ደግሞ ላመጣ ይገባኛል ድምፄንም ይሰማሉ፥ አንድም መንጋ ይሆናሉ እረኛውም አንድ።”
      * 11፡52 ፤ “ስለ ሕዝቡም ሁሉ አይደለም፥ ነገር ግን የተበተኑትን የእግዚአብሔርን ልጆች ደግሞ በአንድነት እንዲሰበስባቸው ነው እንጂ።”
      * 17፡2ዐ-21 ፤ “ሁሉም አንድ ይሆኑ ዘንድ፥ ከቃላቸው የተነሣ በእኔ ስለሚያምኑ ደግሞ እንጂ ስለ እነዚህ ብቻ አልለምንም፤ አንተ እንደ ላክኸኝ ዓለም ያምን ዘንድ፥ አንተ፥ አባት ሆይ፥ በእኔ እንዳለህ እኔም በአንተ፥ እነርሱ ደግሞ በእኛ አንድ ይሆኑ ዘንድ እለምናለሁ።”

      - ሐዋርያው ጳውሎስ ወደ ሮሜ ሰዎች ከጻፋቸው መልዕክቶችም ፡-
      * 1፡16 ፤ “በወንጌል አላፍርምና፤ አስቀድሞ ለአይሁዳዊ ደግሞም ለግሪክ ሰው፥ ለሚያምኑ ሁሉ የእግዚአብሔር ኃይል ለማዳን ነውና።” ፣
      * 2፡9-1ዐ ፤ ክፉውን በሚያደርግ ሰው ነፍስ ሁሉ መከራና ጭንቀት ይሆንበታል፥ አስቀድሞ በአይሁዳዊ ደግሞም በግሪክ ሰው፤ ነገር ግን በጎ ሥራ ለሚያደርጉ ሁሉ ምስጋናና ክብር ሰላምም ይሆንላቸዋል፥ አስቀድሞ ለአይሁዳዊ ደግሞም ለግሪክ ሰው። ፣
      * 3፡29-3ዐ ፤ “ወይስ እግዚአብሔር የአይሁድ ብቻ አምላክ ነውን? የአሕዛብስ ደግሞ አምላክ አይደለምን? አዎን፥ የተገረዘን ስለ እምነት ያልተገረዘንም በእምነት የሚያጸድቅ አምላክ አንድ ስለ ሆነ የአሕዛብ ደግሞ አምላክ ነው።”
      * 4፡11-12 ፤ “ሳይገረዝም በነበረው እምነት ያገኘው የጽድቅ ማኅተም የሆነ የመገረዝን ምልክት ተቀበለ፤ ይህም እነርሱ ደግሞ ጻድቃን ሆነው ይቆጠሩ ዘንድ ሳይገረዙ ለሚያምኑ ሁሉ አባት እንዲሆን ነው፥ ለተገረዙትም አባት እንዲሆን ነው፤ ይኸውም ለተገረዙት ብቻ አይደለም ነገር ግን አባታችን አብርሃም ሳይገረዝ የነበረውን የእምነቱን ፍለጋ ደግሞ ለሚከተሉ ነው።”
      9፡24 ፤ “የምሕረቱ ዕቃዎችም ከአይሁድ ብቻ አይደሉም፥ ነገር ግን ከአሕዛብ ደግሞ የጠራን እኛ ነን።”
      * 1ዐ፡12-15 ፤ “በአይሁዳዊና በግሪክ ሰው መካከል ልዩነት የለምና፤ አንዱ ጌታ የሁሉ ጌታ ነውና፥ ለሚጠሩትም ሁሉ ባለ ጠጋ ነው፤ የጌታን ስም የሚጠራ ሁሉ ይድናልና። እንግዲህ ያላመኑበትን እንዴት አድርገው ይጠሩታል? ባልሰሙትስ እንዴት ያምናሉ? ያለ ሰባኪስ እንዴት ይሰማሉ? መልካሙን የምሥራች የሚያወሩ እግሮቻቸው እንዴት ያማሩ ናቸው ተብሎ እንደ ተጻፈ ካልተላኩ እንዴት ይሰብካሉ?”

      በመጀመሪያው የቆሮንቶስ መልዕክትም 7፡14 ፣ 7፡19 ፣ 12፡12-13ን መመልከት ይቻላል
      ወደ ገላትያ ሰዎችም 5፡6 እንደ አይሁድ መገረዝ ወይም አለመገረዝ ቢሆን በማለት ልዩነትን ይሽራል
      ወደ ኤፌሶን ስዎች ደግሞ 2፡13-22 ፣ 3፡5-1ዐ ፣ 4፡4፡ 15-16ም በክርስቶስ አንድ አካል መሆናችንን ያስረዳል

      ስለ ማርቲን ሉተርም ታሪክ ካነበብኩት ባክል ደስ ባለኝ ነበር ፤ ነገር ግን ማወቁ አይረባንም ፤ በተረፈ የኔን ሹመት ከጽሁፌ ገምተው የሚለግሱኝን እቀበልዎታለሁ ፡፡ መግባባት ያቃተን እርስዎ በክርስቶስ ክርስቲያን ነን ከማለት ይልቅ በክርስቶስ እሥራኤላውያን ነን ስለሚሉኝ ነው ፡፡ ይኸስ የስም መሸሽ በኋላ ምን ሊባል እንደሚችል ስለማላውቅ ፣ ቤተ ክርስቲያናችን በምትጠራበት የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ክርስቲያን ነኝ በሚለው መለያ እቀጥላለሁ ፡፡ እርስዎም እንግዲህ በወደዱት በእሥራኤልነትዎ ፡፡
      ሰላም ይሁኑልኝ

      Delete
    23. ሰላም እንደምን ዋላችሁ።
      መድኃኔዓለም የተመሰገነ ይሁን።

      እርስዎ ሰውየ ምነው የሚይዙት የሚጨብጡትን አጡ? ዝም ብለው ቅጀት ጀመሩ እኮ። እስኪ በስመ አብ ይበሉ።
      እኔን የተቃወሙ እየመሰልዎት እኔ የምልዎትን የሚደግፉ እርስዎ የሚሉትን የሚነቅፉ ጥቅሶችን እኮ ነው የሚጠቅሱልኝ። በጥቅሶቹ ካመኑ እኮ ለኔ መልስ መስጠት አያስፈልጎትም። እኔ የምለው የእስራኤልነት መደምደሚያው ክርስትና ነው። ነው። የብሉይ እስራኤል ዘስጋ የክርስትና (እስራኤል ዘነፍስ) ጥላ ነው። አይሁድና ግሪክ አለ እንጂ እስራኤልና ግሪክ አላለም። አልቆቦታል አርፈው ይቀመጡ። ይህን የማይረባ የፕሮተስታንት አመለካከት ይዘው በአቢይ ጾም የክርክር መናቆሪያ አያድርጉት። የፕሮቴስታንቱን የረከሰና የጠነባ አስተሳሰብ ወደ ጉድጓድ ጥለው ወንጌልን ይጨብጡና በክርስቶስ መንገድ በተዋሕዶ ቢሄዱ ይበጅዎታል።

      እስራኤል ከመሠረቱ የእግዚአብሔር ስም ነው። ክርስቶስ ደግሞ የእግዚአብሔር ስም ነው። እኛ የተዋህዶ ልጆች ክርስቲያን ነን ስንል ስማችን ያገኜነው ከክርስቶስ ነው ማለታችን ነው። ስለዚህ ክርስቲያን ነን ማለት እስራኤል ነን ማለት ነው። በፈረንጆች አቆጣጠር ፲፱፻፵፰ ዓ.ም. ማለትም የዛሬ ፷፭ አመት አካባቢ ኃሳዊያነ መሢሕ ፕሮቴስታንቶች አይሁዶችን ሰብስበው በቴላቪቭ በማስፈር እስራኤል የሚል ስም ሰጧቸው። በዓለም ላይ እየዞሩም እሥራኤል እነሱ ናቸው እያሉ ማስተጋባት ጀመሩ። ብዙዎችንም አሳሳቱ። የእርስዎና የብዙዎች የተሳሳተ አስተሳሰብ ምንጩ ያ ነው። ከ፲፱፻፵፰ ዓ.ም በፊት እስራኤል ማን ነበረ ብለው እስኪ ትንሽ ይመርምሩ። አሁን አይሁድ ነን የሚሉት ከአውሮፓ መጥተው ቴልአቪቭ የሰፈሩት ሰዎች አውሮፓ በነበሩበት ቀደም ባሉት ጊዜያቶች እስራኤል ብሎ ጠርቷቸው የሚያውቅ ፍጥረት አልነበረም። እንግሊዞች ሰዎችን ሰብስበው በቴልአቪቭ ስላሰፈሩ የእግዚአብሔር መልእክት ቋንቋው ይለወጣል ወይ?

      መሠረታዊው ነገር ፕሮተስታንቶች (ኃሳውያነ መሢሕ) አይሁዶችን ሰብስበው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተሰቀለብት ቦታ በማስፈር ከእግዚአብሔር ጋር ቃል ኪዳን ያላቸው እሥራኤል ማለት እነዚህ ናቸው። በመጽሐፍ የተጻፈው “እሥራኤልን የነካና የከፋፈለ ይጠፋል” የተባለላቸው የተመረጡ የተቀደሱ ሕዝብ እነሱ ናቸው።” እያሉ ሌላው ቀርቶ ለነሱ ሲሉ አገራችን ኢትዮጵያን ቆረሱ፣ ምስቅልቅሏን አወጡ፣ አንድ ሃይማኖት ያለንን አንድ ህዝብ ነጣጠሉን። (አይሁድ ነን ባዮቹ ኢትዮጵያን እንዴት እንደተጫወቱባት ለማወቅ ቢፈልጉ የኸርማን ኮኸንን መጽሐፍ ያንብቡ)። እስራኤል ማለት ክርስትያን ሆኖ ሳለ “እስራኤል ማለት አይሁድ ነው” ብለው ፕሮቴስታንት ምእራባውያን ብዙ ግፍ በክርስትያኖች ላይ ፈጸሙ። አዩ ይህ ጅሎች የሚሳለቁበት ሳይሆን መሠረታዊ የሆነ አስተውሎን የሚሻ ነጥብ ነው። እግዚአብሔር እስራኤልን አትንኩ ሲል ቤቱን ቤተክርስቲያንን (ተዋህዶን) አትንኩ ማለቱ እንጂ ከሚጠሉትና ከማያምኑት ከአይሁድ ጋር ምን ጉዳይ አለው? ከአይሁድ ጋር የሚደረግ፣ የሚጠበቅ ሌላ ውል አለ ወይ? በአይሁድ ዘንድ አሁን አምላክ ይመሰገናል ወይ? መልሱ የለም ነው። አይሁድ ጋ አሁን ቅድስና አለ ወይ? የተከበሩ ሆይ፥ አጉል ነገር እኮ ነው የሚያወሩት። ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ እንደሚባለው ማለት ነው። ቅድስናን ፍለጋ ወደ ርኩሰት ስብስብ ይኬዳል ወይ›? ከእርሱ ጋር ውል ያላቸው አይሁዶች እነ ቅዱስ ጳውሎስ፣ እነ ቅዱስ ጴጥሮስ፣ እነ ቅዱስ ዮኃንስ፣ ኢትዮጵያውያንም ጭምር እሱን መድኃኔዓለምን ተከተሉና አመኑ ተጠመቁ ክርስቲያን ሆኑ። አዲስ ምዕራፍ ተጀመረ። እነሆ እስራኤል እነሱ ናቸው። እግዚአብሔር እነሱን የሚተናኮልን ነው ወዮለት ያለው። ለዚህም ነው የተዋህዶ እምብርት የሆነችውን ኢትዮጵያን የነካ ሁሉ ሲወድቅ የምናየው።

      እርስዎ የሚያወሩት ምንም ስሜት የማይሰጥ መሠረት የለሽ ክርክር ነው። እባክዎትን ውይይቱን በአቢይ ጾም ስሜት ወደማይሰጥ ወደ ድርቅና ክርክር መንገድ አይውሰዱት።

      እግዚአብሔር አምላክ ይክበር፣ ይመስገን።
      ኃይለሚካኤል

      Delete
    24. ሰላም ጤና ይስጥልኝ።

      ለማጠቃለል አንዲት ነገር ልጨምር።

      ከአዲስ ኪዳን ትርጓሜ እርስዎም የጠቀሱትን እንደገና እንጥቀስ።

      “ሕዝበ ሮም (እርስዎም እንደተስማሙበት ምእራባውያን) በሕዝበ እሥራኤል ላይ በጸላትነት ይነሡባቸዋል ፡፡”

      ሕዝበ እሥራኤል የሚለውን ቃል አሁን በቴልአቪቭ የሰፈሩት አይሁድ ነን የሚሉት ናቸው ብለን ብንረዳው የትርጓሜው ትንቢት ስሜት የሚሰጥ ሆኖ አናገኜውም ምክንያቱም እርስዎም መረጃውን እንደደረሱበትና እንዳስቀመጡት አይሁድና ምእራባውያን አንዱ ለሌላው ሊሞት ቃል የተገባቡ ሰምና ወርቅ ሆነው ነው የምናያቸው እንጂ ምንም ጠላትነት አናይባቸውም።

      ነገር ግን ሕዝበ እሥራኤል በሚለው ቦታ “ኢትዮጵያ” የሚለውን ቢያስገቡበት ከመቅጽበት ስሜት የሚሰጥ ነገር ሆኖ ያገኙታል። ወንጌል አይሳሳትም። እነሆ ህዝበ እስራኤል ማለት ሕዝበ ክርስቲያን (ተዋህዶ) ማለት መሆኑን በትርጓሜው መጽሐፍ ይረዱ።

      መድኃኔዓለም ይመስገን።
      ኃይለሚካኤል።

      Delete
    25. በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሓዱ አምላክ አሜን ፡፡
      1. ልቋጨው በማለት የስንብት መልዕክት ሳቀርብልዎት ርስዎ ነዎት ውይይቱን እንዲቀጥል ያደረጉት ፤ የቀጠልኩትም የመከራከር ፍላጐቱ ኖሮኝ ሳይሆን ውሸት ሲነገርብን ወይም ሲጻፍብን ዝመ ብዬ ማየት ስላልመድኩ ነው ፡፡ በተለይም በእምነታችን ላይ ሲሆን ይመረኛል ፡፡ አሁንም እንኳን ይባስ ብለው ለፍጡሩ ፣ እግዚአብሔር የሰጠውን ስም ፣ የራሱ መጠሪያ አድርገው ሲያሳክሩን "እስራኤል ከመሠረቱ የእግዚአብሔር ስም ነው።" ይሉናል ፡፡ ከላይ እስራኤልን በተመለከተ ሁሉንም ከመጽሐፍ ቃል የሚስማማ ዝርዝርዝ ትርጉም ሰባስቤ አስቀምጨልዎት ነበር ፡፡ "ኤል" የሚለው ቃል ብቻ ነው እግዚአብሔርን ወይም ፈጣሪን የሚያመለክት ፤ ሚካኤል ፣ ገብርኤል ፣ ሩፋኤል ፣ ራጉኤል ... እንዲል ፤ በዘረዘርኩት ትርጉም ውስጥ ያላካተትኩት ስለከበደኝ ነው ፡፡ ባጠቃላዩ ፈጣሪአችን እስራኤል ተብሎም ሆነ ተጠርቶበት አያውቅም ፡፡ እርሱ እስራኤል ከተባለ ፣ በምን ሂሳብ ቢሆን እኛም እስራኤል እንባላለን ብለው ይሞግታሉ ? እስከ አሁን እኛም እግዚአብሔር ነን እያሉን ነው የመጡት ማለት ነው ፡፡ እኔን ለማረጋጋት ብለው አሁንም ሌላ ተጨማሪ ስህተት ጻፉልን ፡፡

      2. "ለዚህም ነው የተዋህዶ እምብርት የሆነችውን ኢትዮጵያን የነካ ሁሉ ሲወድቅ የምናየው።" ያሉትም ስለማያውቁት ነው ከማለት ይልቅ የክርስትናችንን ታሪክ ችላ ስላሉ ብቻ ነው ብዬ እገምታለሁ ፡፡ ታሪካቸው የተመዘገበላቸውን (በቤተ ክርስቲያናችን ትምህርተ ሃይማኖት ሳይቀር) በአደባባይ ለተዋሕዶ እምነት የተከራከሩ የግብጽ አባቶችን የት ትተው ነው እኛን እምብርት ያሉት ? ወይንስ እነርሱን የተዋሕዶ ልብ ለማድረግ ፈልገው አለያም ኢትዮጵያዊ አድርገዋቸው ይሆን ?

      በተረፈ የአገር ፍቅር መኖሩ ፣ የኢትዮጵያዊነት ስሜትን አጉልቶ ማውጣትዎን ወድጄልዎታለሁ ፡፡ ነገር ግን በእውነት ላይ የተመሠረተ ቢሆን ሁላችንም የምንመኘው ፤ መልሰን የምናስተጋባው ይሆን ነበር ፡፡ ለማንኛውም ጊዜ ወስደው በትዕግሥት ሃሳብዎትን ስላጋሩኝ ፣ ስለሁሉም አመሰግናለሁ ፡፡ መልካም የጾም ጊዜ ይሁንልን ፡፡ አሜን ፡፡

      Delete
    26. ሰላም፡ ጤና ይስጥልኝ እንደምን ዋላችሁ።
      መድኃኒዓለም የተመሰገነ ይሁን።

      እስራኤል የእግዚአብሔር ስም ነው ስል የእግዚአብሔር የሆነ (something that belongs to Him) ንብረቱ፣ የሱ (of Him, that which is specifically His; unlike Kebede, Delelegn etc) ለማለት ነበር የተጠቀምኩበት። ልክ የእግዚአብሔር ሰው እንደሚባለው። የቃላት አጠቃቀሜ እንዴት የተለየ ስሜት ሊሰጥ እንደሚችል ብገነዘብም እኛ እግዚአብሔር ነን ለማለት እንንዳልሆነ እርስዎም ያውቁታል። የሆነ ሆኖ ግን ለክስ የሚሆን ወንጀል ፍለጋ ላይ የተሰማሩ ሰው በመሆንዎ የተገኘውን ሁሉ የርቀት አጋጣሚ ለውንጀላ ይጠቀሙበታል። ይህን የሚያደርጉ እርስዎ ሳይሆኑ በውስጥዎ ያለው ክፉ መንፈስ መሆኑን አውቃለሁ። ሊጸለይልዎት ይገባል።

      እስካሁን ድረስ የሚዋሹት እርስዎ ኖት። ጥቅሶችን ያለአግባብ ለሃሰት ምስክርነት የሚጠቀሙትም እርስዎ ኖት። የሌባ አይነደረቅ እንደሚባለው “ውሸት ሲነገርብን” እያሉ ይመጻደቃሉ። ያቀረብኩትን ሁሉ ከነማስረጃው ነው ያቀረብኩት። ሰነፍ የጥበብን ነገር አይወድም ተብሎ እንደተጻፈ ጠበብን አልወደዷትም። ኤሳውም ጸጋውን አላወቀም፥ አቀለላት። ጅል ውድቀቱ ሁለት ጊዜ ነው። አንደኛም በስንፍናው ምክንያት ቤቱን ስለማይመረምር እግዚአብሔር ጸጋ እንደሰጠው አያውቅም። በሱ ጸጋ ላይ ሌሎች ሲሳለቁ አብሮ ይሳለቃል። ሁለተኛም ሰነፍ ስለሆነ ሌሎች “ጸጋ ያለን እኛ ነን አንተ ጸጋ የለህምና እንምራህ ተከተለን” ሲሉት ሳይመረምር የራሱን ጥሎ የሌለ የሌላ ጸጋ እሱም እርግማን ሲከተል ይውላል። ሰነፍ በሰፈሩ ከሚያየው እውነት ይልቅ ከሩቅ የሚሰማውን ሐሰት ያምናል። ምን ይደረግ የእግዚአብሔር መላእክት በአረም እስኪመለሱ ድረስ ሰይጣን በመካከላችን እንክርዳድ ዘርቶብን አሁን ብዙ ሰነፎች በሰፈራችን ተሰግስገዋል። “እኛ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ አማኞች ነን” ይላሉ ቅኝታቸውም “እንቋችን እንጣል፣ እንቋችን እንጣል” ነው። የመዝሙራቸው አርዕስትም “የሌሎችን ድሪቶ እንሰብስብ” ነው። ምን አደከመዎት - ቁርጥ እርስዎን።

      ኃሳዊያነ መሢሕ በኢትዮጵያ ያላቸው ዋነኛ ተልእኮ ኢትዮጵያን ከመንፈሳዊነት ውጭ ማድረግ ነው። ይህንንም በእያንዳንዱ የኃሳዊያነ መሢሕ አረፍተ ነገር ውስጥ ማየት ይቻላል። በዚህም ረገድ ባለፉት አርባ አመታት ብዙ ተሳክቶላቸዋል (የዚህ ብሎግ የአስተያየት መስጫ ሰሌዳ ለጥናታዊ ሥራ ጽሁፍ ተስማሚ ስላልሆነ ይህን በተመለከተ እግዚአብሔር በፈቀደ ሌላ መንገድ ፈልጌ ለኢትዮጵያውያን አቀርባለሁ።) እርስዎም በተለያየ ተቃውሞዎት ይህንኑ ዝንባሌዎትን አሳይተዋል። ኢትዮጵያ የተዋህዶ እምብርት ናት ማለቴ አሳመምዎት። የታመመው አሁንም በድጋሜ በውስጥዎ ያለው ክፉ መንፈስ ነው። ጳጳስ ከግብጽ ይመጣ ስለነበር ለምን ግብጽ አላልክም ብለው ነው። ከዳዊት በፊት እኮ እግዚአብሔር የቀባው ሳኦልን ነበር። ምነው ሮምንስ ረሱ? የቅዱስ ጴጥሮስ መንበር እኮ ሮም ነበረ። እርስዎ አይኖትን ስለጨፈኑ ቀኑ ለኛ ጨልሟል ማት አይደለም። በዓለም ላይ ካሉ ከየትኞቹም አገሮች በበለጠ ኢትዮጵያ ብዙ የእግዚአብሔር ተዓምራት እና ጥበብ የተገለጠባት አገር ናት። ሌላው ቀርቶ “ሞዓ አንበሳ ዘእምነገደ ይሁዳ” በሚል ስያሜ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ክርስቶስ ነው ተብሎ ከአንድ ሺህ ስድስት መቶ ሃምሳ አመታት በላይ ዙፋን ለክርስቶስ መባ የተሰጠባት አገር ናት። ታካችን ተነስና የእግዚአብሔርን ተዓምራት ተመልከት ቢሉት አንበሳ በሜዳው አለ ቢበላኝስ ይላል። ብዘረዝርልዎ ደስ ባለኝ። ቦታውም አይመች፣ ዕንቁ በእሪያ ፊት እንዳይሆን ተብሎ እንደተጻፈም ቦታና ጊዜን እጠብቃለሁ። በነገራችን ላይ “ሞዓ አንበሳ ዘእምነገደ ይሁዳ” የሚለው ቃል የይሁዳ መደምደሚያው ክርስቶስ መሆኑን ያሳያል። ማለትም የብሉይ ኪዳን እስራኤል መዳረሻው የአዲስ ኪዳን ክርስቲያን ነው።

      “የኢትዮጵያዊነት ስሜትን አጉልቶ ማውጣትዎን ወድጄልዎታለሁ” የሚለው ከንቱ የክፋት አነጋገርዎን ወደ መሰልዎችዎ ይውሰዱ። የሚሰማኝ ስሜት ይቅርና የምጽፈው ቀላልና ግልጽ አረፍተ ነገርም እንኳን አልገባዎት እያለ ይሄው በንትርክ እያንገላቱኝ አይደለምን? እንደርስዎ አይነት ሰው የሚወደው ባህርይ ካለኝ አሁኑኑ አስወግደዋለሁ። ንብ ቢወደው አበባ፤ ዝምብ ቢወደው አዛባ እንዲሉ። ለማንኛውም እንዲያውቁት ለኢትዮጵያ ያለኝ ፍቅር መሠረቱ ክርስቶስ ነው።

      ምስጋና ይድረስ ለመድኃኔዓለም።
      ኃይለሚካኤል።

      Delete
    27. በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሓዱ አምላክ አሜን ፡፡
      አሁን ደግሞ ቃልዎ እየገነተረብኝ ነው የመጣው ፤ የጻፉትን ቃል ገልብጨ ይኸማ እንዴት ይሆናል ባልኩ ፣ ክፉ መንፈሴ ተገለጠልዎትና እስከ ምኔ እንደሆነ ነገሩኝ ፡፡ እውነትን የሚፈልግ ሰው ብዙውን ችሎ ነውና ስለ አባባልዎ አንዳች አልተከፋሁም ፡፡ አልታወቀዎት ይሆናል እንጅ ይኸው የተሳሳተ ቃልዎን በመጠቆሜ ማብራራትና ማቃናት ቻሉና ተጠቀሙ ፡፡

      በተረፈ እኔ ያነሳሁትን መከራከሪያ እኮ ፣ ራስዎ ከላይ በደንብ አብራርተው ገልጸውታል ፡፡ የተግባባን ስለመሰለኝ አለፍኩት እንጅ ፣ እሥራኤል የሚለው ቃል ቢያንስ በሁለት እንደሚከፈል ተስማምተናል ፤ እሥራኤል ዘስጋ እና ፣ እሥራኤል ዘነፍስ ፤ እኔ ቀደም አይሁድ ኦርቶዶክስና አይሁድ ክርስቲያን ያልኩዎትን ያመለክታል፡፡ ታድያ በደፈናው እንዴት እሥራኤል እንባላለን የምልዎትን ደግሞ ቢያንስ በዚህ የአገባብ ልዩነት የተረዱትን እንዳብራሩት ሁሉ ፣ በመጽሐፍ ቅዱስም የተለያየ አገባብ እንዳለው ፣ ከግለሰብ ስም እስከ ሕዝብ መጠሪያ ሆኖ ማገልገሉን ለመገንዘብ ቀናነት ቢኖርዎ መረዳቱ አይከብድዎትም ነበር ፡፡

      ስለ እሥራኤል ሲባል ኢትዮጵያ ከሁለት ወገን ተከፈለች ብለው ደጋገሙት እንጅ ፣ በመከፈላችን ያስገኘላቸውን ጥቅም አላብራሩትም ፤ ይኸም ለኔ እንቆቅልሽ ነው ፡፡ ነባራዊ ታሪኩን ለውጠው ፣ አዲስ ነገር ሊያስተምሩን ካልሆነ በስተቀር የመገንጠላችን ምክንያት ከእሥራኤላውያን ጋር የተያያዘ አይደለም ፡፡

      ስለ ግብጾችም የጠቀስኩት በኬልቄዶን ጉባኤ (451 ዓ.ም. እኤአ) “ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ነን” በማለት ከካቶሊክ በመገንጠላቸውና ራሳቸውን በመለየት በተዋሕዶ እምነት ምሥረታ ባደረጉት አስተዋጽዖ እንጅ ቋንቋችንን የማይናገር ጳጳስ በወርቅ ፣ በብርና በዝሆን ጥርስ ለውጥ ስለላኩልን አይደለም ፡፡ እዚያ ጉባኤ ላይ ተገኝቶ የውሳኔው ተካፋይ የነበረ አንድ እንኳን ኢትዮጵያዊ አባት ከነበረ ቢገልጹልኝ ለመማርና ቃሌን ለማረም ዝግጁ ነኝ ፡፡

      ሳጠቃልለው እንደምኞትዎ ወደፊት በዚህና በሌሎችም ጉዳይ ላይ ሰፋ ያለ መግለጫ የያዘ ምናልባትም መጽሐፍ ከጻፉልን አንብቤ ለመማር እችል ይሆናል እንጅ እስከ አሁን ያስተማሩኝ አንዱም አልገባኝም ፡፡ እስከዚያውም ያቀዱትን ያስፈጽምዎ ዘንድ በየዕለቱ እግዚአብሔር ይረዳዎትና ሰላሙን ይሰጥዎት ዘንድ እመኛለሁ ፤ ለርስዎም ከተገለጸው ክፉ መንፈስ እገላገል ዘንድ በጸሎትዎ እንዳይርሱኝ እለምንዎታለሁ ፡፡

      አመሰግናለሁ ፤ ሰላም ይሁኑልኝ ፡፡

      Delete
    28. ትንሽ የሚታከል መግለጫ
      በእኔ ከሚበሳጩ የጻፉትን ደግመው ያንብቡት ፤ እኔ የፈጠርኩት አስመስለው ወረዱብኝ ፡፡ በጽሁፍ የሰፈረው ቃልዎት ሳይጨመርለትና ሳይቀነስለት እንዲህ ይላል ፤ “እስራኤል ከመሠረቱ የእግዚአብሔር ስም ነው። ክርስቶስ ደግሞ የእግዚአብሔር ስም ነው። እኛ የተዋህዶ ልጆች ክርስቲያን ነን ስንል ስማችን ያገኜነው ከክርስቶስ ነው ማለታችን ነው። ስለዚህ ክርስቲያን ነን ማለት እስራኤል ነን ማለት ነው።” ፡፡ አሁን እንግዲህ ልብ ይበሉት እስራኤልንና ክርስቶስ የሚለውን ስም እያነጻጸሩ መጻፍዎን ፡፡

      በእርሶ አባባል ትርጉሙ እንዲህ ሊሆን ነው ፡፡
      1. እሥራኤል የእግዚአብሔር ስም ነው ፡፡
      2. ክርስቶስም የእግዚአብሔር ስም ነው ፡፡
      3. ክርስቶስን ያመነ ሁሉ ክርስቲያን ይባላል ፡፡
      4. ክርስቲያን ማለትም ደግሞ እሥራኤል ነው ፡፡ በተጠናበረ አመክንዮ መሆን አለበት

      እኔ ደግሞ በተራ የሂሳብ ስሌት ብልሃት ስመረምርልዎት
      1. እሥራኤል == የእግዚብሔር ስም
      2. ክርስቶስ == የእግዚአብሔር ስም
      3. ስለዚህ እሥራኤል == ክርስቶስ
      4. እናም ትንሽ እንኳን ክብሩን ላለመዳፈር ሲባል ዘእሥራኤል ቢሉት ባማረልዎት ነበር ፡፡

      ይኸን በዚሁ ይተውትና እንዲያው ለመሆኑ ፣ ዘመን ቆጥረው አይሁዳውያንን እሥራኤል ብለው አሠፈሩበት ያሉትና ፣ እኛ ክርስቲያኖች እሥራኤል ነን የሚሉኝ ፣ ባለቤቶቹን ከምድራቸው አስወጥተው ኢየሩሳሌምን ለመውረስ አስበው ይሆን ? ከቻሉና ፈቃደኛ ከሆኑ ይኸ ሁሉ ትግል ምን ለማትረፍ እንደሆነ በትንሽ ቃል ጨምረው ይግለጹልኝ ፡፡ አይሁዳውያንስ ከዚህ ዓለም በየትኛው ስፍራስ ይኖሩ ነበር ወይንስ ከጠፈር የወደቁ መጤዎች ይሆኑ ?

      Delete
    29. ሰላም ጤና ይስጥልኝ እንደምን ዋላችሁ።
      መዳህኔዓለም የተመሰገነ ይሁን።

      በአዲስ ኪዳን እሥራኤል ማለት ክርስቲያን ነው። አራት ነጥብ። በአዲስ ኪዳን አይሁድ ብሎ እሥራኤል የለም። አራት ነጥብ። እሳካሁን ድረስ እኔ ብቻ ሳልሆን እርስዎም የጠቀሷቸው የወንጌል ጥቅሶች በሙሉ የመሰከሩት ይህንኑ ነው። አሁን ደግሞ እንደገና ተመለሰው ሌላ ጭቃ ውስጥ ተዘፈቁ። እሥራኤል ዘሥጋ እና እሥራኤል ዘነፍስ “አይሁድ ኦርቶዶክስና አይሁድ ክርስቲያን” ነው ይሉኛል። እስካሁን ድረስ የሚጻፈውን አያነቡም ማለት ነው ወይስ የአእምሮ መታወክ ነው ልበል እንዲህ የሚያደርግዎት? ተግባባን የሚል አረፍተ ነገር ካጻፉ በኋላ ተመልሰው ጭቃ ውስጥ እንዴት ይገባሉ? ሃዋርያው በቀጥታ በክርስትና አይሁድና ግሪክ ብሎ ነገር የለም እያልዎት እኔ ብቻ ሳይሆን እራስዎ ጠቅሰውት እንደገና አሁን ለብሽሽቅ ነው ይሄን የሚሉት?

      የፕሮተስታንት እምነት ተከታይ ሆነው ይሆናል ስለ ቤተክርስቲያን ትምህርት የማያውቁት። በኦርቶዶክስ ተዋህዶ ትምህርት እሥራኤል ዘነፍስ ማለት የተዋህዶ አማኝ ክርስቲያን ማለት ነው። እርስዎ መቸም አይማሩም ለአንባቢ እንዲረዳ የዛሬ ፲፰ ዓመት የተጻፈ ጽሁፍ ላስነብዎት። እስራኤል ዘነፍስ እኛ የተዋህዶ ክርስቲያኖች ነን ይላል ጽሁፉ።

      http://www.mahiberekidusan.org/Default.aspx?tabid=36&ctl=Details&mid=371&ItemID=15

      እንደገና ሌላም የተዋህዶ ጽሑፍ ላስነብቦት። ይህም ጽሁፍ እንዲሁ እሥራኤል ዘነፍስ እኛ ክርስትያኖች ነን ይላል።

      http://freatewhedo.blogspot.com/2012/04/blog-post_15.html


      ከቅዱስ ሚካኤል ድርሳን ደግሞ ጥቂት ልጥቀስልዎት።

      “እሥራኤል ዘሥጋን በመንገዳቸው ሁሉ የጠበቃቸው፥ መና ከሰማይ ያወረደላቸው፥ ተአምራትን ያደረገላቸው፥ ማርና ወተት ወደምታፈስሰው ርስታቸው የመራቸው፥ በደመና መጋረጃ የጋረዳቸው፥ በክንፎቹም የሸፈናቸው መጋቤ ብሉይ የተባለ ቅዱስ ሚካኤል ነው። እኛንም ከዲያቢሎስና ከሠራዊቱ ይጠብቀናል፥ ከአሽክላው ይሰውረናል፥ ወደ ምድረ ርስት ገነት መንግሥተ ሰማያት ይመራናል፥ ብለን እናምናለን። ኅዳር አሥራ ሁለት ቀን በየዓመቱ በማኅሌት እና በቅዳሴ የምናከብረው ይኽንን ለእሥራኤል ዘሥጋ የተደረገውን በማሰብ ነው። የበለጠው ደግሞ እሥራኤል ዘነፍስ ለምንባል ክርስቲያኖች ይደረግልናል። የእግዚአብሔር ቸርነት፥ የድንግል ማርያም አማላጅነት፥ የቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነት አይለየን አሜን።”

      አሁንስ ያምናሉ ወይስ አያምኑም?

      እኔን ተሳሳትክ ለማለት ትንሽ እኩዮሽ (ኢክዌሽን) ቢጤ ጀምረውልኛል። እኔ እኮ በየቀኑ የምሳሳት ሃጢአተኛ ሰው ነኝ። አላማዎት ከኔ ስህተት ማግኜት ከሆነ ስህተት ሞልቷል። ነገር ህን የኔ መሳሳት የርስዎን የተዛባ መንገድ አያቃናውም። ለምሳሌ እኔ ልሳሳት ልበል። አረፍተ ነገሩን ስጽፍ “እኛ እግዚአብሔር ነን” ማለቴ አይደለም አልክዎት። እንደዚህ ማለቴ አይደለም ማለቴ እኮ በቂ ነበረ። ለእርስዎ ቁምነገሩ የውውይቱ ፍሬ ነገር አልነበረም። ሃሳቡን ትተው ወይ ኩላሊቴን ወይ እግሬን ተኩሰው ለመምታት ጥርስዎን ነክሰው በየቀኑ ኃጢአት የሚሠራውን ሰውነቴን ይሳድዱት ጀመር። ለማኛውም እግዚአብሔር ይትረቅዎ።

      ለመድኃኔዓለም ምስጋና ይሁን።
      ኃይለሚካኤል።

      Delete
    30. ሰላም ጤና ይስጥልኝ እንደምን ዋላችሁ።
      መዳህኔዓለም የተመሰገነ ይሁን።

      ትንሽ ላክል

      “ስለ እሥራኤል ሲባል ኢትዮጵያ ከሁለት ወገን ተከፈለች ብለው ደጋገሙት እንጅ ፣ በመከፈላችን ያስገኘላቸውን ጥቅም አላብራሩትም ፤ ይኸም ለኔ እንቆቅልሽ ነው ፡፡” ላሉት እኔ ስለ እሥራኤል ሲባል ኢትዮጵያ ለሁለት ተከፈለች አላልኩም። እኔ ያልኩት ስለ አይሁድ ሲባል ኢትዮጵያ ተከፈለች ነው ያልኩት። የካምፕ ዴቪድ ስምምነት የተባለውን አሜሪካኖች የገቡበት በአይሁዶች ጎስጓሽነት ለአይሁዶች ጥቅም ሲሉ ነው። ውሉ አይሁድና ግብጽ በወዳጅነት እንዲተያዩ ለማድረግ ነበር። እነ ኢራን በአይሁዶች ላይ እንዳይነሱ ለማገድ ግብጽ ለአይሁድ ትሠራለች አይሁድ ደግሞ ኢትዮጵያ እንዳትበለጽግና ውኃ እንዳትገድብ አይሁዶች ይሻጥራሉ። አሜሪካኖች ግብጾችን የተወሳሰበ መሣሪያ ያስታጥቃሉ፣ በውትድርና ያሰለጥናሉ (ግብጾች የውትድርናውን ስልጠና የሚደረግላቸው በኢትዮጵያ ላይ ወታደራዊ የበላይነትን በቀላሉ ለማግኜት እንዲችሉ ነው። ውሉ በማየት ግብጾች መሣሪያውን በአይሁድ ላይ እንደማያዞሩት አሜሪካኖችና አይሁዶች ይተማመናሉ።) ባህረ ነጋሽ ከኢትዮጵያ እንድትገነጠል የተደረገውም ኢትዮጵያን ከንግድ ለመለየት ና ለማቀጨጭ ግብጾች ስለፈለጉት እና አይሁዶችም በስምምነታቸው መሠረት ይህን የግብጽ መሻት (interest) ከግብ ማድረስ ስለነበረባቸው አሜሪካን በመጠቀም አስገነጠሉ። ቤተክርስቲያንም በዚሁ መንገድ ተከፈለች። ኢትዮጵያ መከፈሏ አንሶ ቤተክርስቲያን ተከፈለች ማለት በጣም ከባድ የሆነ ነገር ነው። አትራፊዎቹ አይሁድና ግብጾች ናቸው። አይሁድ ይህን ስላከናወኑ ግብጾችም አይሁዶችን ከብዙ የአረብ ጥቃት ጠብቀዋቸዋል። ለበለጠ መረጃ ጣልቃ ገብነታችን በአፍሪቃ የሚለውን የኸርማን ኮኸንን መጽሃፍ እና የግብጽ ጣጣ መዘዝ በሚል ርዕስ በግሬጎሪ ኮፕሌይ የቀረበውን የስለላ መረጃ ዘገባ ያንብቡ።

      ምስጋና ለመድኃኔዓለም።
      ኃይለሚካኤል።

      Delete
    31. ቃል አባይ እንደምጸየፍ ቢያውቁ እንዲህ በቀለም ብቅ ባሉ ቁጥር የማይነካካኝን እንዲህ ነህ ፤ እንጀራህ (ሥራህ) በዚህ ፣ መኖሪያህም በዚያ ቢሆን ፤ የሌለብኝንም እንዲህ አለብህ ፤ አይ እንግዲያው እንዲያ ብትሆን ነው ባላሉኝም ነበር ፡፡ እኔ ግን እንደዚህ ዓይነቱን ሰው በትዕግሥት ከማሳለፍ በስተቀር ብዙ አልተጋፋሁም ፡፡

      ብቻ አንዳንዴ እንደርስዎ የመጨረሻው ቀን ምልክቶች ይሆኑ እላለሁ ፤ “ሰዎች ትምክህተኞተ ፣ በትዕቢት የተነፉ ፣ ተሳዳቢዎች ፣ ቅድስና የሌላቸው ፣ ፍቅር የሌላቸው ፣ የአምልኮተ መልክ አላቸው ፣ ነገር ግን … ” 2 ጢሞ 3፡2-5 ስለሚል ፡፡

      በተረፈ ወደ ቁም ነገራችን ስመለስ በዚሁ ከተስማማን ይበቃኛል እልዎታለሁ ፡፡ ስለሰጡኝ ማብራሪያም በጣም አመሰግናለሁ ፡፡ ቢረዱልኝ የእኔም ትግል ይኸው ነበር ፤ እውነትን ፍለጋ ብቻ ፡፡ አሸነፍኩ ለማለት ሳይሆን ትክክለኛው ቃል አሁን ያመጡልን ነው ፡፡ እሥራኤል ዘነፍስ ነው እንጅ በደፈና ክርስቲያኖች እሥራኤል ነን ማለት አይቻልም ፡፡ ምክንያቱም የቃሉ አገባብ በመጽሐፍ ይለያያልና ነው ፡፡ ከላይ በጽሁፌ በሸቁ እንጅ ከአይሁድ መሃከል ክርስቲያን የሆኑትን የጠቀስኳቸው እሥራኤል ዘነፍስ ለማለት ፈልጌ ነው ፡፡ አይደሉም የሚሉኝ ከሆነ ስለነርሱ አልከራከርዎትም ፤ ከአሁን በኋላ ግን እኛ እሥራኤል ሳይሆን የምንባለው “እሥራኤል ዘነፍስ” ነን ብለው ያስተምሩን ፡፡ ያስነበቡኝም ጽሁፍ ይኸንኑ መስክሯልና ፡፡

      “እነርሱ የኤርትራን ባሕር ተሻገሩ፡፡ በባሕርም መካከል ተጠመቁ፡፡ እኛ ግን ምልዓት ኃጢአትን ተሻገርን፣ ልጅነትን በሚያሰጥ በውኃና በመንፈስ ቅዱስ ተጠመቅን፡፡ እነርሱ ከሞተ ነፍስ የማያድን መና በሉ፡፡ እኛ ግን ሞተ ነፍስን የሚያሸንፍ ሥጋውንና ደሙን በላን፡፡ እነርሱ እሥራኤል ዘሥጋ ተባሉ፡፡ እኛ ግን እሥራኤል ዘነፍስ ሆንን፡፡”

      በመጨረሻ ያሳረጉበት ቃል የኔም ድክመት ነው ፤ እግዚአብሔር ይቅር ባይለን ፍጹምነት ከማንኛችንም ዘንድ አይገኝም ፡፡ እኔ ስህተትዎትን በመፈለግ ሳይሆን ሌሎች እጅ ሳንወድቅ ርስ በርሳችን ብንማማርበት ለማለት ጠቀስኩት ፤ ርስዎ እንዴት ብለው ተቆጡኝ ፤ አይነ ደረቅ ስለሆንኩ ባይረዱኝ ይሆናል ብዬ አብጠርጥሬ ደገምኩልዎት ፡፡ አሁን ፍሬ አፍርቶ መጣ ፡፡ ወደፊትም በሃሳብ ልውውጥ መገናኘታችን የማይቀር ይመስለኛልና ሲያገኙኝ እንደ ጨዋ እንወያይ ፡፡ አያውቁኝ አላውቅዎት ፣ አያገኙኝ አላገኝዎት ፤ ሻይ እንጠጣ እንኳን የማንባባል ሰዎች እንዲያው በመስኰት ስንተያይ በጠላትነት ስንፈላለግ እንዳንኖር አደራ ፡፡ ሌላ ቦታ ስለ መለያ ስሜ ሲሉ ብቻ ምኑንም ምኑንም ሲጽፉ አጋጥሞኛል ፡፡ አቶን የጠላው የክርስትና ስምዎት ስለሚሆን ወደፊትም ስጽፍ ኃይለሚካኤል ብቻ በማለት ይሆናልና ቅር እንዳይልዎት ፡፡

      ሰላም ይሁኑልኝ ፡፡ ሳይሰላቹ ስላስተናገዱኝም እግዚአብሔር ይስጥልኝ ፡፡

      Delete
    32. ሰለም ጤና ይስጥልኝ እንደምን ዋላችሁ።
      መድኃኔዓለም የተመሰገነ ይሁን።

      ቃለ አባይ መጸየፍዎ መልካም ነው ነገር ግን መጽሐፍ በወንድምህ ዓይን ያለውን ጉድፍ ስለምን ታያለህ፥ በዓይንህ ግን ያለውን ምሰሶ ስለ ምን አትመለከትም? ያለውን አይርሱ።

      “ቤተ ክርስቲያን ከፖለቲካ ተጽእኖ ነጻ ሆና አታውቅም” በሚል ርዕስ ዲያቆን ዳንኤል ስለ ዜግነት በሰጠው አስተያየት የሰጠሁትን አስተያየት በመንቀፍ ልክ እርስዎ በኢትዮጵያ ቅዱሳንም ላይ ቢሆን የሃሳብ የበላይነት (intellectual authority) እንዳለዎት አድርገው በባቢሎን የተመካ ትእቢት ያለበት መልስ ስለሰጡኝ እኔ ደግሞ ቅዱሳን አባቶቻችን ትተውልን ባለፉት መንፈሳዊ ቅርስ ላይ “እንዲህ አይነት ጽንፍ ያላቸው ብዙዎች ናቸው፣ አዲስም አይደሉም” ብለው በትእቢት መነሳትዎትን በማየት ከኃይማኖቴ ቅንአት ተነስቼ ነው በእግዚአብሔር ኃይል አሁን ካለንበት ደረጃ ላይ የደረስነው። በግልጽ ለመናገር ድፍረቱ ባይኖርዎትም ብዙ ትምህርት እንዳገኙበት አልጠራጠርም።

      “ሰዎች ትምክህተኞች ፣ በትዕቢት የተነፉ ፣ ተሳዳቢዎች ፣ ቅድስና የሌላቸው ፣ ፍቅር የሌላቸው ፣ የአምልኮተ መልክ ያላቸው” ይሆናሉ ብሎ መጽሐፍ የተናገረው በተለይ ስለባቢሎን ሰዎች ስለኃሳውያነ መሢሕ ነው። እንደሚያዩት ጌታ፣ ጌታ ይላሉ። ጌታ ጌታ እያሉ በሱ ስም ሰዎችን ቅኝ ይገዛሉ። የእግዚአብሔር ስም ሃያ አራት ሰዓት በሚቀደስባት በኢትዮጵያ መጥተው በአንድ እጃቸው መጽሐፍ ቅዱስ ይዘው በሌላ እጃቸው የዝንጆሮ አጽም ቆፍረው በማውጣት እራሳቸውን ከእግዚአብሔር በማስተካከል ሰው የመጣው ከጦጣ ነው እያሉ በትልቅ ትእቢት ይታበያሉ፣ ቅድስት ድንግል ማርያምን የሚሰድቡ ፥ የሚያጣጥሉ፣ ቅዱሳንን የሚሳደቡ ወዘተ። እነሱን ነው መጽሐፍ ትምክህተኛ ያላቸው። ምክንያቱም በእግዚአብሔር ሳይሆን በእጃቸው ሥራ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ይመካሉና። ስለ ኃይማኖት ብለው በእግዚአብሔር እየተመኩ ኃይለቃል ቢናገሩ የኃይማኖት ቅንዓት ነው እንጂ ትእቢት ወይ ስድብ አይደለም። ይህን ይወቁ።

      አሁንም እንደገና በዘመነ አዲስ ኪዳን አይሁድ እሥራኤል አይደሉም። በዘመነ አዲስ ኪዳን አይሁድ እሥራኤል ዘሥጋም አይደሉም ምክንያቱም በአዲስ ኪዳን አይሁድ የሚሠሩት በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት ያለው አንድም ነገር የለምና። በዘመነ አዲስ ኪዳን ያሉ እሥራኤል ዘነፍስ ብቻ ናቸው እነሱም ክርስቲያኖች ብቻ ናቸው። እንደገና ለመድገም በአዲስ ኪዳን እሥራኤል የምንባል የተዋህዶ ክርስቲያኖች ብቻ ነን።

      ምስጋና ለመድኃኔዓለም።
      ኃይለሚካኤል።

      Delete
    33. ሰላም ጤና ይስጥልኝ ፡፡
      ስለ አይሁድ ጉዳይ አልከራከርዎትም ብዬ ነበር ፤ ነገር ግን አሁንም ርዕስ አደረጉብኝ ፡፡ እንዳነበብኩት የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች እስከ ሦስት መቶ ዓመተ ምሕረት ገደማ የሚባሉት በደፈናው ክርስቲያን ነበር ፡፡ ተዋሕዶ ምን የሚባል ክፍፍል አልነበረም ፡፡እንዲሁም ክርስቶስን የተቀበሉና የተከተሉ ደቀመዛሙርት ስማቸው በቅዱሱ መጽሐፍ በሐዋርያት ሥራ ሳይቀር ተጠቅሷል ፡፡ የሐዲስን መጽሐፍት ጸሐፊዎቻችን ከሉቃስ በስተቀር በሙሉ ቢቀበሏቸውም ባይቀበሏቸው አይሁዳውያን የክርስቶስ ተከታዮች ናቸው ፡፡ ክርስቲያን የሚለውንም ቃል በመጀመሪያ የተጠቀሙ እኛ ሳንሆን እነርሱው ናቸው ፡፡ ሥራ 11፡26 ፡፡

      ተዋሕዶ የሚለው ቃል ጋር ስንመጣ መለኮትና ሥጋ በተዋሕዶ አንድ ባሕርይ ሆኑ ፤ አምላካችን በተዋሕዶ ፍጹም ሰው ሆነ ለማለት ነው ፡፡ ኢየሱስን ሁለት ባሕርይ የሚሉ ወገኖች ይኸን የኛን ገለጻ በጊዜው ሄረሲ ወይም መጤ ትምህርት ፣ ምንፍቅና ሲሉ ፣ አንዳንዶች እስከ አሁንም ቢሆን የስህተት ትምህርት እንደሆነ አድርገው ነው የሚያስተምሩት ፡፡ እናም እኛ የተዋሕዶ ክርስቲያኖች እሥራኤል ዘነፍስ ስንባል ቢያንስ የመጀመሪያዎቹን የክርስቶስ ተከታይ ክርስቲያኖች ደምስሰን ሊሆን ይገባው አይመስለኝም ፡፡ የእነርሱን ማንነት መካድ እኛን ባለቤት አያደርገንም ፡፡ የእምነቱ ትምህርት በራሱ የመጣው ከነርሱ ስለሆነ ፡፡

      በተረፈ እኔም ይህንኑ ነገር በማሰብ ፣ ለርስዎ በጥያቄ መልክ ስለ እሥራኤል ዘሥጋና ዘነፍስ ምንነት አቀረብኩልዎት ፡፡ ተነተኑልኝ ፤ የተግባባን መስሎኝ ዝም አልኩ ፡፡ ሌላው ደግሞ ትላንት ያመጡና ያስነበቡኝም የማኀበረ ቅዱሳን መግለጫ አይሁዳውያንን እስራኤል ዘሥጋ ይባላሉ ብሎልዎታል ፡፡ ቃሉን አንብብና እመን ያሉኝ ርስዎ ሳይቀበሉ ሊሆን አይችልምና ፤ እሥራኤል መባላቸው አያከራክረንም ፡፡

      አሁንም የድፍረት ቃል ቢያገኙ ያለዕውቀት ነውና ይቅርታ ፡፡

      Delete
  4. Ananymous 8:46 PM

    Yihn bilgnahn Ethiopiawinet yadinal menfesawinet ayadinm laleh sew bitwosdilet ayshalm?

    ReplyDelete