Sunday, March 3, 2013

የአዲሱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ፓትርያርክ በዓለ ሲመት እሑድ ተፈጸመ


(Reporter ):- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስድስተኛ ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም  ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት  በዓለ ሲመት እሑድ የካቲት 24 ቀን 2005 ዓ.ም. በአዲስ አበባ መንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል  ተፈጸመ፡፡
እኩለ ቀን ያህል በወሰደው ታላቅ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት  አቶ አባ ዱላ ገመዳ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ሚኒስትሮች፣  የሕንድ ኦርቶዶክስ ፓትርያርክን ጨምሮ የተለያዩ አገሮች አብያተ ክርስቲያናት ተወካዮች ተገኝተዋል፡፡

 የካቲት 21 ቀን በከፍተኛ ድምፅ  የተመረጡት የ71 ዓመቱ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ማትያስ ዳግማዊ የተኩት  ጥንታዊቷን ቤተ ክርስቲያን ለ20 ዓመታት የመሯትና ባለፈው ነሐሴ ያረፉትን አቡነ ጳውሎስ ቀዳማዊን ነው፡፡
ቅዱስነታቸው በመንበረ ሐዋርያትና በመንበረ ተክለ ሃይማኖት  ከመቀመጣቸው በፊት መሠረተ ሃይማኖትንና ቀኖና ቤተ ክርስቲንን ለመጠበቅና ለማስጠበቅ ቃለ መሐላውን  በዐቃቤ መንበረ ፓትርያርኩ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል አማካይነት የፈጸሙ ሲሆን የፓትርያርክነት ዘውዱንም አድርገውላቸዋል፡፡

በበዓለ ሲመቱ  ‹‹ለቤተ ክርስቲያኗ ህልውና ለእግዚአብሔር ክብርና ለሃይማኖት ሲባል ቅዱስ ሲኖዶሱ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ፣ እንደ አንድ ልብ መካሪ ሆኖ ተስማምቶና ተግባብቶ እስከሠራ ድረስ ችግር ይኖራል ተብሎ አይታመንም፤ ከራሳችን ጥቅም ይልቅ ቤተ ክርስቲያኒቱን በማስቀደምና ማዕከል በማድረግ ከሠራን ምንም ችግር ሊኖር አይችልም፤›› በማለት  በዐውደ ምሕረቱ ላይ ንግግር ያደረጉት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በማጠቃለያቸው ላይ ‹‹ለረዥም ጊዜ ሲያወዛግብ የከረመው የዕርቅና ሰላም ጉዳይ ለጊዜው ባይሳካም በቅዱስ ሲኖዶሱ ውሳኔ መሠረት ጥረቱ ይቀጥላል፤›› ብለዋል፡፡

No comments:

Post a Comment