Friday, February 22, 2013

ሦስት ጋዜጠኞች በኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን በቀረበባቸው ክስ ለፖሊስ ቃላቸውን ሰጡ




(ሰንደቅ የካቲት 13 2005 ዓ.ም)፡-በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት በቀረበ ክስ መሰረት ሦስት ጋዜጠኞች በቀድሞ የማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ  ቢሮ ቀርበው ቃላቸውን ሰጡ፡፡

በቤተክርስያኗ ላይ የሐሰት መረጃ አሰራጭተዋል የተባሉት የእኛ ፕሬስ ፤ ሎሚ መጽሄት ፤ ሊያ መጽሄት ፤ እና አርሂቡ መጽሔት ሲሆኑ ማዕከላዊ ቀርበው ቀርበው ቃል እንዲሰጡ ተደርጓል፡፡ ጋዜጠኞቹ ቃላቸውን ሰጥተው አሻራና ፎቶ ግራፍ ከተነሱ በኋላ ሊብሬና የቤት ካርታ በማስያዝ ተለቀዋል፡፡ 


የሊያ መጽሄት ማኔጂንግ ዳይሬክተር ጋዜጠኛ መላኩ አማረ ለሰንደቅ ጋዜጣ እንደገለጸው መጽሔቱ በቁጥር 19 ዕትሙ ላይ “የኢትጵያ ኦርቶዶክስ ተዋዶ ቤተክርስቲያን ቀጣይ እጣ ፈንታ ምንድነው?”  በሚል ባቀረበው ጽሁፍ ጋር በተያያዘ በአቃቢ መንበር አቡነ ናትናኤል በግል ክስ እንደቀረበበት ገልጿል፡፡  ክሱ አግባብ አለመሆኑ የገለጸው ጋዜጠኛ መላኩ “የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመገንባት የተነሳች ቤተክርስቲያን ተራ ዜጎችን መክሰሷ ያሳዝናል” ሲል በክሱ ላይ ያለውን ቅሬታ ገልጿል፡፡

የሎሚ መጽሔት ዋና አዘጋጅ ግዛው ታዬ በበኩሉ የተመሰረተበት ክስ መንግሥት በሐይማኖት ፤ ሐይማኖትም በመንግስት ጣልቃ አይገባም የሚለውን ሕገ-መንግስታዊ ድንጋጌ በመጻረር ፤ ሕዝብ በመንግስትና በቤተክርስቲያን አመኔታ እንዳይኖረው የሚያስችል ጽሑፍ አትሞ በማሰራጨት ፤ ሕዝብን ለአመጽና ለሁከት የሚያነሳሳ ጽሁፍ አትሞ አሰራጭቷል የሚሉ ናቸው፡፡

እንደ ጋዜጠኛ ግዛው ክሱ ሕገ-መንግስታዊ ድንጋጌ የሆነውን ሀሳብን የመግለጽ መብት የሚነካና ከቤተክርስቲያን የማይጠበቅ ነው ሲል ክሱን ተቃውሟል፡፡ በተመሳሳይ ክስ የቀረበበት እኛ ፕሬስ ጋዜጣ ቃል እንዲሰጥ ከማዕከላዊ የወንጀል ምርመራ ቢሮ ጥሪ እንደተደረገለት የጋዜጣው  ዋና ስራ አስኪያጅ ኤርሚያስ ስዩም ለሰንደቅ ጋዜጣ አረጋግጧል፡፡

No comments:

Post a Comment