Saturday, February 23, 2013

ምረጡኝ ብዬ አላልኹም፤ ምረጡኝ ብዬ አላውቅም



  • ፓትርያሪክ እንድሆን የመንግስት ባለሥልጣን አላግባባሁም 
  • ካህናትና ምእመናን ለቤተ ክርስቲያንና ለቤተ ክርስቲያን ብለው ብቻ ማሰብ፣ ይገባቸዋል›› - /ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል/


From Addis Admass :

አምስተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ የነበሩት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በሞተ ሥጋ ከተለዩ ስድስት ወራት ተቆጠሩ፡፡ ከፓትርያርኩ ኅልፈት በኋላ በሕገ ቤተ ክርስቲያን በተደነገገው መሠረት ስድስተኛው ፓትርያርክ እስኪመረጥ ድረስ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል በዐቃቤ መንበረ ፓትርያሪክነት ተሠይመው ቤተ ክርስቲያኒቱን በማገልገል ላይ ናቸው፡፡



የስድስተኛውን ፓትርያሪክ ምርጫ ለማስፈጸም ታኅሣሥ 10 ቀን 2005 . በቅዱስ ሲኖዶስ የተቋቋመው የፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴ ጥር 30 ቀን 2005 . ለብዙኀን መገናኛ ይፋ ባደረገው የምርጫ መርሐ ግብር መሠረት፤ ከየካቲት 9 - 14 ቀን 2005 . አምስት ዕጩ ፓትርያሪኮች ሲመርጥና ሲያጣራ ቆይቶ በዛሬው ዕለት ለቅዱስ ሲኖዶሱ እንደሚያርቀርብ ታውቋል፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤም ከዛሬ ጀምሮ በሚያካሂደው ውይይት የካቲት 21 ቀን 2005 . ለሚከናወነው ምርጫ በዕጩነት በሚቀርቡት አምስት ዕጩ ፓትርያሪኮች ላይ የመጨረሻ ውሳኔ አሳልፎ የዕጩዎቹን ዝርዝር ይፋ እንደሚያደርግ ይጠበቃል፡፡

የምርጫው ሂደት በይፋ ከተጀመረ አንሥቶና ከዚያም በፊት ቀጣዩ ፓትርያሪክ እንደሚኾኑ ብዙ ከተነገረላቸው ሊቃነ ጳጳሳት መካከል የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል አንዱ ናቸው፡፡ ብፁዕነታቸው በፓትርያሪክነት ምርጫው ከሚሳተፉ 800 በላይ መራጮች የምርጫ ድጋፍ ለማሰባሰብ በሥልጠና ስም በርካታ ገንዘብ ማውጣታቸውን፤ በሕንፃ ኪራይ፣ በሥራ ምደባ፣ በውጭ ተልእኮና በሹመት አሰጣጥ ለብዙዎች ቃል መግባታቸውን፤ ከዚህም አልፎ ቀጣዩ ፓትርያሪክ እርሳቸው እንደሚኾኑ ራሳቸውን ለመንግሥት አካላት ስለ ማስተዋወቀቸው በአንዳንድ ሚዲያዎች ተዘግቧል፡፡

በእኒህ ጉዳዮች ላይ የብፁዕ አቡነ ሳሙኤልን አስተያየት ከራሳቸው አንደበት ለመስማት የአዲስ አድማስ ሪፖርተር ሰላም ገረመው ከብፁዕነታቸው ጋር አጭር አጠር ያለ ቆይታ አድርጋለች፡፡

በያዝነው ዓመት በኮሚሽኑ ድጋፍ ለአህጉረ ስብከት ሓላፊዎች የተሰጡ ሥልጠናዎች፣ በአዲስ አበባ ከግብጽ ቤተ ክርስቲያን ጋር የተደረጉ የልምድ ልውውጦች ከፓትርያሪክ ምርጫው ጋር በተያያዘ ለብፁዕነትዎ ድጋፍን የመሸመት ዓላማ እንደነበራቸው ይነገራል፡፡ የተሰጠው ሥልጠና ምን ነበር? ዓላማውና የበጀት ምንጩስ?

ከግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከመጡ ልኡካን ጋር የተደረገው የልምድ ልውውጥና የተሰጠው ሥልጠና፣ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከግብጹ ፖፕ አቡነ ሺኖዳ ጋር ቀድሞ በደረሱበት ስምምነት መሠረት የተፈጸመ፣ ነገር ግን ዘግይቶ የተፈጸመ ስለኾነ እንጂ ከፓትርያሪኩ ኅልፈት በኋላ የታቀደና ለምርጫ ድጋፍ ቅሰቀሳ የታሰበ አይደለም፤ በቀጣይም ከሌሎች አኀት አብያተ ክርስቲያናት ለምሳሌ ከሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጋር በተመሳሳይ መድረኮች የመገናኘት ዕቅድ አለን፡፡

ለአህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጆችና ሌሎች ሓላፊዎች በጥቅምት ወር ከሀገር አቀፉ አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ጋር ተያይዞ የተሰጠው ሥልጠና አምናም በተመሳሳይ ወቅት የነበረ ነው፡፡ 2004 . ጥቅምት ወር ፓዝፋይንደር ኢትዮጵያ በሰጠው የገንዘብ ድጋፍ በሥነ ተዋልዶና የሴት ልጅ ግርዛት ላይ ያተኮረ ሥልጠና ለቅዱስ ሲኖዶስ አባላትና ለአህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች ተሰጥቷል፡፡

በዚህ ዓመት ‹‹ዳቦ ለዓለም›› በተባለ ገባሬ ሠናይ ድርጅት ድጋፍ በአቅምና የሰላም ግንባታ ጭብጥ ዙሪያ በታቀዱ በርካታ ርእሰ ጉዳዮች ላይ በመስኩ ባለሞያዎች ሥልጠና ተሰጥቷል፡፡ ዋና ዓላማው በቤተ ክርስቲያናችን መልካም አስተዳደር እንዲጠናከር፣ ፍትሕ እንዲሰፍንና የልማት አቅም እንዲፈጠር ነው፡፡ ስለዚህ ምርጫው ስላለ ወይም ከምርጫው ጋር ተያይዞ የታቀደ ነገር አይደለም ማለት ነው፡፡
ለሥልጠናው ተሳታፊዎች በአበል መልክ እንደተጨማሪ ክፍያ ወጥቷል የተባለው 500,000 ብርና የበጀት ምንጩስ?

የዚህ ዓመት ሥልጠና የበጀት ምንጩ እንደተናርኹት እኛው ቀርጸን ‹‹ዳቦ ለዓለም›› (Bread For the World) ገባሬ ሠናይ ድርጅት ባቀረብነው ፕሮፖዛል መሠረት የተገኘ ገንዘብ ነው ለሥልጠናው ማስፈጸሚያና ለአበል የተከፈለው፡፡ ይህም በየዓመቱ በተለያዩ ርእሰ ጉዳዮች ላይ ፕሮፖዛል እየቀረጽን፣ ድጋፍ ሰጪ ድርጅቶችን እየጠየቅን ስንሠራው የቆየና ለወደፊቱም የሚቀጥል ነው፡፡ ለሥልጠናው ወጭ የተደረገው ገንዘብ ለአፋርና ለሶማሌ ክልሎች ለሚሠሩ የልማት ፕሮጀክቶች የተገኘ ገንዘብ ነበር ለተባለው በክልሎቹ ለምንሠራው ሥራ ድጋፍ ያገኘነው ከተመድ የስደተኞች ማእከል (UNCR) ነው፤ ገንዘቡንም የሚቆጣጠረው ራሱ ማእከሉ ነው፡፡ ስለዚህ ከሥልጠናው ወጪ ጋር አይገናኝም፡፡

ከምርጫው ጋር በተያያዘ÷ ሹመት እንደሚሰጣቸው፣ በሥራ እንደሚመደቡ፣ በሕንጻ ኪራይ፣ በውጭ ዕድል ቃል የተገባላቸው መራጮች አሉ ተብሏል
ለመሾምም፣ ሕንጻ ለማከራየትም፣ በሥራ ለመመደብም፣ ወደ ውጭ ለመላክም ሥርዐት አለው፡፡ ከተጠቀሱት የትኛውም ነገር ከሥርዐት ውጭ እንዳይፈጸም ተከፍቶ የነበረው መንገድ ተዘግቷል፡፡
በሌላ በኩል የፓትርያሪክ ምርጫ መንፈሳዊ ጉዳይ ነው፡፡ በዚህ መንገድ ፕትርክናውን ለማግኘት ማሰብና መሞከር ሕግም አይፈቅድም፡፡ ይህ የሥልጣን ስግብግብነት ነው፡፡ መራጮቹስ እነማን እንደኾኑ በስም ይታወቃሉ ወይ? ይህን አሉባልታ ያመነጩትና የሚያስተጋቡት የምርጫውን ሂደት ለማወናበድ፣ ሕጋዊውን አሠራር ወደ ቤተሰባዊነት፣ ዘረኝነትና አድሏዊነት ለመውሰድ ማመኻኛ የሚሹ ሕገ ወጥ ቡድኖች ናቸው፡፡

ስድስተኛው ፓትርያሪክ ኾነው እንዲመረጡ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትን፣ የቤተ ክህነት አመራሮችንና ታዋቂ ግለሰቦችን አግባብተዋል? ስለጉዳዩ ላይ ሊቃነ ጳጳሳቱ ትችት እንደሰጡ ተዘግቧል።
ምረጡኝ ብዬ አላልኹም፤ ምረጡኝ ብዬ አላውቅም፡፡ ይህን አድርገኻል የሚሉኝ ወገኖች እውነተኛ ከኾኑ መረጃውን ለምን አያቀርቡም? የቤቱን [የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን] ዕድገት፣ ልማትና መሻሻል ርምጃዎች ሲያኮላሹ የነበሩ ሰዎች ስሜት ነው፡፡
 
የመንግሥት ባለሥልጣናትን ማግባባትዎና ‹‹መንግሥት ፓትርያሪክ ኾኜ እንድመረጥ ይፈልጋል›› እያሉ ማስወራትዎ. . .
ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮኻል፤ በየትኛውም አቅጣጫ የተለያዩ አካላት ብዙ ሊናገሩ ይችላሉ፤ ይህንንም የሚሉት የቤታችንን የዕድገትና ልማት ርምጃ ሲያኮላሹ የነበሩ ግለሰቦችና አሁን ደግሞ በምርጫው ዙሪያ የተደራጁ ቡድኖች ናቸው፡፡
ፓትርያርክነት የአባትነት፣ የቡራኬ ሥልጣን ነው፤ ለእኔ አገልጋይነት ይሻለኛል፤ አገልጋይ መኾን ነው እንጂ፤ አገልጋይነት÷ ሃይማኖትን መጠበቅና ማስጠበቅ፣ ሕዝብንና እግዚአብሔርን በማእከል ኾኖ ማገናኘት እንጂ አዛዥ፣ ገዥ፣ አሳሪ፣ አሳሳሪ መኾን አይደለም፡፡

ለመኾኑ እንዴት ነው የፓትርያሪክነት ሥልጣን ይሰጠኝ ብዬ የምጠይቀው? ሹመቱ የመንፈስ ቅዱስ ምርጫ ነው፤ ሥርዐቱ የሚፈጸመው በፍትሕ መንፈሳዊ፣ በሕገ ቤተ ክርስቲያን፣ በፓትርያርክ ምርጫ ሕገ ደንቡ መሠረት ነው፤ ሕጉን፣ ሥርዐቱን የሚፈጽመውና የሚያስፈጽመው ቅዱስ ሲኖዶሱና ሕዝቡ እንጂ መንግሥት አይደለም፤ በሕገ መንግሥቱ የመንግሥትና ሃይማኖት ግንኙነት ምን መኾን እንደሚገባው በግልጽ ተደንግጓል፡፡ ያግባባኹትም የጠየቅኹትም የመንግሥት አካል ይኹን ባለሥልጣን የለም፡፡

በምርጫው የሚሳተፉ ካህናትና ምእመናን ለሚኖራቸው ድርሻ እርስዎ ምን ይላሉ? በምርጫው ዙሪያ ይካሄዳል ስለሚባለው የቡድኖች እንቅስቃሴስ
?
በየብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳቱ ቤት፣ በእኔም ቤት ሳይቀር እየዞሩ እገሌን ካልመረጣችኹ፣ ካላስመረጣችኹ የሚሉ አካላት እንዳሉ ግልጽ ነው፡፡ ሥልጣን ባለው አካል መንፈሳዊ ሥልጣንን ለመያዝ የሚደረገው ሽር ጉድ ሁሉ በፍትሕ መንፈሳዊ፣ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን የተወገዘ ነው፤ ይህን የሚያደርጉ አካላት በሰውና በእግዚአብሔር ዘንድ ይጠየቃሉ፡፡ እንዲህ ኾኖ የሚሾመው አባትም ቢኾን ሢመቱ ሥጋዊ ሹመት ይኾንና በነፍስም በሥጋም ያጎድለዋል፤ ያለጊዜውም ሊያሥቀስፍ ይችላል፡፡

ስለኾነም በምርጫው የሚሳተፉ ካህናትና ምእመናን ለቤተ ክርስቲያንና ለቤተ ክርስቲያን ብለው ብቻ ማሰብ፣ መወሰንና መቆም ይገባቸዋል፡፡

1 comment:

  1. Thank you Andadrgen ! you gave us approprait information at approprait time.

    ReplyDelete