Monday, June 4, 2012

የዋልድባን ገዳም እናድን የሚሉ ሰላማዊ ሰልፎች በዓለም ዙርያ ሲካሄዱ ውለዋል


በ Addisu Abebe | Washington From VOA news
ሙሉውን ዘገባ ለማዳመጥ እዚህ ይጫኑ፡

ዛሬ ማለዳ ከዩናይትድ ስቴትስ ምክር ቤት ተነስቶ ወደ ውጪ ጉዳይ መሥራ ቤት የተጓዘውን የዋሽንግተኑን ሰልፍ ተከታትለን ነበር






በተደጋጋሚ የዘገብንበት ርዕሰ-ጉዳይ ነው፣ ዋልግድባ ገዳም። በዚህ ገዳም ላይ ደረሱ ከተባሉት አንዳንዶቹን ለመጥቀስ ለስኳር ፋብሪካ ፕሮዤክትና ለሸንኮራ-አገዳ ልማት ቦታው እየታረሰ ነው፤ የአበው መካነ-መቃብር እየተቆፈረ አስከሬናቸው በመውጣት ላይ ይገኛል፣ አያሌ አብያተ-ክርስቲያናት ሊፈርሱ በዕቅድ ተይዘዋል፣ የገዳሙ ንብረት የሆነ በርካታ ገንዘብ ባልታወቁ ታጣቂዎች ተዘረፈ፣ ብዙ ኲንታል የእጣን ምርት ባልታወቁ ሰዎች ተቃጠለ፤ እናም ይህን አባቶች «በደል» ያሉትን በዝርዝር ለተለያዩ መገናኛ ብዙኃን የሚገልጹ መነኮሳት አደን፣ ወከባና እንግልት እየደረሰባቸው ነው የሚሉ ይገኙባቸዋል።

የተባለው ልማት በእርግጥም በዕቅድ ላይ መሆኑን መንግትም ሆነ ጠቅላይ ቤተ-ክህነቱ ያምናሉ። መንግሥት፣ «ልማቱ ከገዳሙ ብዙ እርቅት ላይ ስለሆነ አይነካውም» ሲል፣ ወደ ስፍራው የተላኩት የጠቅላይ ቤተ-ክህነቱ የዐይን ምስክሮችም ይህንኑ አረጋግጠው፣ «ቤተ-ክህነት የመንግስቱን የልማት ዕቅድ ትደግፋለች" ብለዋል።

የገዳሙ ይዞታ እንዳይነካ ጥያቄ የሚያቀርበው ሕዝብ በአካባቢው ብቻ አልተወሰነም። «ዋልድባን ለመታደግ የተቋቋመ ዓለማቀፍ ኰሚቴ» የተሰኘው ስብስብ የየአካባቢው ተጠሪዎች ለቪኦኤ እንደገለጹት፣ ዛሬ አንድ ዓለማቀፍ ሰላማዊ ሰልፍ በመካሄደ ላይ ነው። ሰሜን አሜሪካ ውስጥ ቶሮንቶ-ካናዳ፣ ሎስ-አንጀለስ-ላኪፎርኒያ፣ ኒው-ዮርክና ዋሽንግተን ዲሲ። አውሮፓ ደግሞ ጀርመን፣ ብሪታንያ፣ ብራስልስና አውስትሬሊያ መሆኑን አስተባባሪዎቹ ተናግረዋል።

ዛሬ ማለዳ ከዩናይትድ ስቴትስ ምክር ቤት ተነስቶ ወደ ውጪ ጉዳይ መሥራ ቤት የተጓዘውን የዋሽንግተኑን ሰልፍ ተከታትለን ነበር።
በዚህ ሰልፍ ላይ የክርስትና እምነት ተከታይ ብቻ አይደለም የተገኙት። ሌሎችም በኢትዮጵያውነታቸው ተገኝተዋል። ከዋሽንግተን ሌላም በሎስ-አንጀለስና በቶሮንቶ ካናዳም ተመሳሳይ ሰላማዊ ሰልፍ ተካሂዶ ነበርና ተወካዮቹን በስልክ አነጋግረናል።

ከዩናይትድ ስቴትስ ውጪ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የተወከሉት ባለሥጣን Ms Lora, ሙሉ ስማቸውን ማግኘት አልተቻለም፤ የሰልፈኛውን ደብዳቤ ተቀብለው ጉዳዩን እንደሚያጤኑትና ተገቢ ነው የሚሉትን ምላሽ በጽሑፍ እንደሚሰጡ ለሕዝቡ ገልጸዋል።

በተለይም ባለፈው ሐሙስ ሰቋር ውስጥ፣ በማግስቱ ዐርብ ደግሞ ገሪማ ላይ ስብሰባ ተካሂዷል። የሐሙሱ፣ እራሱ ሕዝቡ ተጠራርቶ የተሰባሰበበት ሲሆን የዐርቡ ደግሞ ባለሥልጣናት የገዳሙን አሥር ያህል መነኮሳት ጠርተው የሰበሰቡት እንደነበር ተገልጾልናል። በዚህኛውም ሆነ ዛሬ በተካሄደው ሰልፍ ላይ ከዚያው ከአካባቢው ባለስልጣናት መልስ ለማግኘት ያደረግነው ጥረት አልተሳካም። ይሁንና ግድቡም ሆነ ልማቱ ገዳሙን እንደማይነካ መንግሥት ገልጧል።

2 comments:

  1. Good effort by diaspora. May God be with us.

    ReplyDelete
  2. Is there any video of this?

    ReplyDelete