Sunday, April 20, 2014

ቅዱስ ፓትርያርኩ ቤተ ክርስቲያን ግብረ ሰዶማዊነትን እስከ መጨረሻው አምርራ ትዋጋለች አሉ


  • ‹‹ፀረ ግብረ ሰዶማዊነት የመንግሥት አጀንዳ ሳይሆን የተወሰኑ ቡድኖች አጀንዳ ነው ስለዚህም በሕግ የተቀመጠው ቅጣት በቂ ነው››  አቶ ሬድዋን ሁሴን ለአሶሼትድ ፕሬስ

(ሪፖርተር ሚያዚያ 12 2006 ዓ.ም) የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ፣ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ፣ ኢትዮጵያውያን ግብረ ሰዶማዊነትን በጽናት እንዲመክቱ ጥሪ አቀረቡ፡፡ ቤተ ክርስቲያንም እስከመጨረሻው አምርራ ትዋጋለች አሉ፡፡

ቅዱስ ፓትርያርኩ 2006 .. የትንሣኤን በዓል ምክንያት በማድረግ ‹‹ሕይወትን አየናት፣ አወቅናትም›› በሚል መሪ ቃል ባስተላለፉት ሃይማኖታዊ ቡራኬ ላይ እንዳሳሰቡት፣ ሰዶምንና ገሞራን በእሳት ያጋየ ግብረ ኃጢአት በኢትዮጵያ ልማትና ዕድገት ሳይሆን መቅሰፍትና ውድቀት እንዳያስከትል ሁሉም ኢትዮጵያዊ ይህንን የሰዶም ግብረ ኃጢአት ሊከላከል ይገባል፡፡


 የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ይህንን ግብረ ኃጢአት እስከ መጨረሻው ድረስ አምርራ ትዋጋዋለች ያሉት ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ፣ እኛ ክርስቲያኖች ለእግዚአብሔር ያለንን ፍቅር ለመግለጽ በመዋዕለ ጾሙ በአምልኮ፣ በጾም፣ በጸሎት፣ በምጽዋትና በስግደት ስንገልጽ እንደቆየን ሁሉ፣ በፋሲካው በዓላችን እግዚአብሔር የሰጠንን በረከት ከተቸገሩ ወንድሞቻችንና እኅቶቻችን ጋር በመካፈል ለወገኖቻችን ያለንን ፍቅር ልንገልጽ ይገባናል ብለዋል፡፡

የትንሣኤ መሠረታዊ ትርጉም ከሞት በኋላ በሕይወት መኖርና መመላለስ ነው፤ ስለሆነም የትንሣኤን በዓል ስናከብር ባለፉት ዘመናት በድህነትና በኋላ ቀርነት ከሞት አፋፍ ደርሳ የነበረችውን አገራችን በልማትና በዕድገት ትንሣኤዋን ለማረጋገጥ ቃል በመግባት በዓሉን ማክበር አገራዊ ብቻ ሳይሆን ሃይማኖታዊ ግዴታ መሆኑን መገንዘብ አለብን፤በማለት በቃሉ ቡራኬአቸውን አሳስበዋል፡፡

‹‹ጠንክረን በመሥራት ምድራችንን እንድናለማና እንድንከባከብ ከሁሉ በፊት ያዘዘ እግዜአብሔር ነውና፤›› ያሉት ቅዱስ ፓትርያርኩ፣ በተለይም የልማታችን የጀርባ አጥንት ሆኖ እንደ ሚያገለግል ታላቅ ተስፋ የተጣለበት ታላቁ የሕዳሴ ግድብ፣ በተያዘው ፍጥነት ሥራው ተሠርቶና ተጠናቆ የዕድገታችን ተሸካሚ ምሰሶ ሆኖ ማየት እንድንችል ሁሉም ኢትዮጵያዊ ድጋፉን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል፡፡ 

 
የይቅርታ ሥነ ሥርዓት ረቂቅ አዋጅ በቅርቡ ለፓርላማ ቀርቦ የነበረ መሆኑ ይታወሳል፡፡ በዚሁ ረቂቅ አዋጅ ላይ ግብረ ሰዶም ይቅርታ የማያሰጥ ተደርጐ ከሌሎች ወንጀሎች ጋር ተዘርዝሮ ተቀምጦ ነበር፡፡ የይቅርታ ሥነ ሥርዓት ረቂቅ አዋጁ በአሁኑ ወቅት በሕግና ፍትሕ አስተዳደር ቋሚ ኮሚቴ እጅ የሚገኝ ሲሆን፣ የግብረ ሰዶም ወንጀል ይቅርታ የማያሰጥ ተደርጐ የተጠቀሰበት አንቀጽ መሰረዙን ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡

የመንግሥት ቃል አቀባይ የሆኑት አቶ ሬድዋን ሁሴን ለአሶሼትድ ፕሬስ ፀረ ግብረ ሰዶማዊነት የመንግሥት ሳይሆን የተወሰኑ ቡድኖች አጀንዳ መሆኑን፤ ስለዚህም በሕግ የተቀመጠው ቅጣት በቂ መሆኑን ባለፈው ሳምንት ለአሶሼትድ ፕሬስ ገልጸው ነበር፡፡  
 
ግብረ ሰዶማዊነት በኢትዮጵያ በሕግ የተከለከለ ሲሆን እስከ 15 ዓመት በእስር ያስቀጣል፡፡ በተመሳሳይ ፆታ ግንኙነት አንድን ግለሰብ ለኤችአይቪ ቫይረስ ማጋለጥ ደግሞ 25 ዓመት እስራት ያስቀጣል፡፡ 


በሌላ በኩል ረቡዕ ሚያዝያ 8 ቀን 2006 .. ሃይማኖታዊ ቡራኬ ፓትሪያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ፣ ኢትዮጵያውያን ግብረ ሰዶማዊነትን እንዲከላከሉ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ግብረ ሰዶማዊነትን እንደምትዋጋ አስታውቀዋል፡፡             


1 comment:

  1. ዋና መልእክታቸውን ለምን ተዘሉታላችኍ?

    ሊቃውንት እንደሚያስተምሩን ጌታ ሰው መኾኑ፥ መሞቱ፥ መነሣቱ አዳምና ሔዋን በዲያብሎስ ተንኮል ከትእዛዙ በመውጣታቸው ቢያገኙት ቁንጣን ቢያጡት ቀጠና የሚኾን "ሲሳየ ኀዘን" ወዳለበት "ምድረ ፋይድ" መውረዳቸው ቢያሳዝነውና ወደቀደመ ክብራቸው ወደዘለዓለማዊ ሕይወት ሊመልሳቸው ቢወድ ነበር። ልማታዊው አቡን ባስተላለፉት መልእክት ግን፦

    " የትንሣኤ መሠረታዊ ትርጉም... ሃይማኖታዊ ግዴታ... [ስለኾነ] ጠንክረን በመሥራት ምድራችንን እንድናለማና እንድንከባከብ... በተለይም የልማታችን የጀርባ አጥንት ሆኖ እንደ ሚያገለግል ታላቅ ተስፋ የተጣለበት ታላቁ የሕዳሴ ግድብ፣ በተያዘው ፍጥነት ሥራው ተሠርቶና ተጠናቆ የዕድገታችን ተሸካሚ ምሰሶ ሆኖ ማየት እንድንችል ሁሉም ኢትዮጵያዊ ድጋፉን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል፡፡

    እንዲኽ ያለውን ዋና መልእክታቸውን ችላ ብላችኍ፤ ለመጪው ስንት ወር ይኹን ስንት ዓመት እየተጨቃጨቅን የእነሱን ሃይማኖትም አገርም የማፍረስ እኩይ ተግባር እንዳናይ ለማድረግ ዐላውያኑ የፈጠሩትን አጀንዳ ለምን ታራግባላችኍ? ረ ንቁ ባካችኍ!

    ReplyDelete