Tuesday, November 5, 2013

ኑፋቄ የተገኝበት መጽሐፍ ታገደ


በዳዊት ደስታ
  • መጽሐፉ በዋልድባ ገዳም የሚኖሩ መነኩሴ የጻፉት ነው፡፡

(አንድ አድርገን ጥቅምት 26 2006 ዓ.ም)፡- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ  ባደረገው ስብሰባ ‹‹ምስጢረ ሥላሴ በአበው ሊቃውንት›› በመል ርዕስ በዋልድባ ገዳም በሚኖሩት በመ/ር አባ ገ/እግዚአብሔር አብርሃ የተዘጋጀውን ቅጽ አንድና ሁለት መጽሀፍ በሊቃውንት ጉባኤ አስመርምሮ የኑፋቄ ትምህርት ያለበት መሆኑን ስለተረጋገጠ እንዳይራጭና እንዳይሸጥ አገደ፡፡

መጽሐፉ በማንኛውም የቤተክርስቲያኒቱ ዐውደ ምህረትም ሆነ የመጻሕፍት ማከፋፈያ ቦታዎች እንዳይሸጥና እንዳይሰራጭ ቋሚ ሲኖዶሱ ያገደው የዋልድባ አብረንታት ገዳም መጽሐፍ ኑፋቄ ያለበት መሆኑን ለጠቅላይ ቤተክህነት በተደጋጋሚ ጥያቄ በማቅረቡ ምክንያት ነው ተብሏል፡፡
                                                     
በመምህር አባ ገ/እግዚአብሔር የተዘጋጀው ቅጽ አንድና ሁለት መጽሐፍ ከቤተክርስቲያን ትምርተ ሃይማኖት አስተምህሮ አንጻር በሊቃውንት ጉባኤ ተመርምሮ የውሳኔ ሃሳብ እንዲቀርብለት ቋሚ ሲኖዶስ ባዘዘው መሰረት የሊቃውንት ጉባኤ ሰኔ 27 2005 ዓ.ም በጻፈው ደብዳቤ አባሪ አድርጎ የላከው  ባለ ዘጠኝ ገጽ ጽሁፍ መጽሐፉ ኑፋቄ እንዳለበትና ዶግማ ያፋለሰ እና የጣሰ መሆኑን ገልጿል፡፡

የሊቃውንት ጉባኤ አባሪ አድርጎ የላከው ጽሑፍ ስለ ምስጢረ ሥላሴና  ምስጢረ ሥጋዌ የቀረበው ማብራሪያ የቤተክርስቲያኒቱ አስምህሮ በተለየ ‹‹ሦስት መለኮት›› የሚል በመሆኑ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ዶግማ ያፋለሰ እና የጣሰ መሆኑን ይገልጣል፡፡

ስለ ምስጥረ ሥላሴ እና ምስጥረ ሥጋዌ  የቀረበው የተሳሳተ ትምህርት በዋልድባ አብረንታት ገዳም መናንያን ዘንድ ከፍተኛ ሁከት ፈጥሮ እንደነበር መረጃው ያመለክታል ፡፡ ይህንንም አስመልክቶ በቁጥር ዋል/042 በቀን 16/09/2005 ዓ.ም የተጻፈው ደብዳቤ በመጀመሪያ ለብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማቲያስ ቀርቦ በሊቃውንት ጉባኤ እንዲጣራ መመሪያ መስጠታቸውን ከሪፖርቱ መረዳት ተችሏል፡፡

ጉዳዩን በተመለከተ የሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና ዋና ጸሀፊ ብጹዕ አቡነ ሉቃስ ‹‹መጽሐፉን በሊቃውንት ጉባኤ ታይቶ ኑፋቄ እንዳለበት  ተረጋግጧል ፡፡ ስለሆነም መጽሐፉ ቀድሞ ታትሞ በመበተኑ በመጀመሪያ መጽሐፉን ማውገዝና መሰብሰብ አስፈልጓል፡፡ ምክንያቱም ምዕመናን መጽሐፉን አንብበው እንዳይሳሳቱ ለመጠበቅ ነው፡፡ ቀጥሎም ጸሐፊው ተጠርተው ይጠየቁና ስሕተታቸውን እንዲያውቁ ይደረጋል ፤ ስሕተታቸውን አውቀው ከተመለሱ መልካም ነው፡፡ ካልተመለሱ ግን እንዲወገዙ ይደረጋል፡፡›› ብለዋል፡፡

ኑፋቄ ያለባው መጻፍት ሲወገዙ ለሁሉም ሀገረ ስብከት ታሳውቃላችሁ? ብለን ላቀረብንላቸው ጥያቄ አሁን ቅሬታ የቀረበው በገዳሙ ሲሆን በቀጣይ ጸሐፊውን  አናግረን ስህተታቸውን የማይቀበሉ ከሆነ ለሁሉም ሀገረ ስብከት እናሳውቃለን ሲሉ ገልጠዋል፡፡

የሊቃውንት ጉባኤ ሰብሳቢ ሊቀ አእላፍ ያዝዓለም ገሠሠ በበኩላቸው  ‹‹መጽሐፉ የትምህርተ ሃይማት ችግር እንዳለው ገዳማውያኑ ለቋሚ ሲኖዶስ በማሳወቃቸው የሊቃውት ጉባኤ ደግሞ መርምሮ ለቋሚ ሲኖዶስ አቅርቧል፡፡ በቀጣይ ፀሀፊው ተጠርተው ይኼን የተሳሳተ ትምህርት እንዳያስተምሩ እና ከስህተታቸው እንዲመለሱ ለመወያየት ቀነ ቀጠሮ ይዘናል፡፡ በምክሩ እና በተግሳጹ ከስህተታቸው የማይመለሱ  ከሆነ ጉዳዩ ዳግም ለቅዱስ ሲኖዶስ ቀርቦ ቀኖናዊ ውሳኔ እንዲተላለፍባቸው ይደረጋል›› ብለዋል፡፡ ለመጽፉ መልስ የሚሆንና የሚያቀርበውን ትንታኔ ውድቅ የሚያደርግ መጽሐፍ በሊቃውንት ጉባኤ እደሚዘጋጅ ለማወቅ ትችሏል፡፡
ስምዐ ጽድቅ ጥቅምት 2006 ዓ.ም

የ‹‹አንድ አድገን›› ሃሳብ
ቋሚ ሲኖዶሱ እና ሊቃውንተ ቤተክርስቲያናት በአንድ በመሆን የሰሩት ስራ የሚያስመሰግን ነው፤ በየጊዜው የተለያዩ ቤተክርስያኒቱን የማይወክሉ ጸሀፍት በርካታ ነገሮች እየተጻፉ ለምዕመኑ እንዲበተኑ ሲደረግ ቆይቷል ፤ ሁሉም በየሀገረ ስብከቱ ይህን የመሰለውን  ኢ-ኦርቶዶክሳዊ የሆነ የኑፋቄ አካሄድ ተመልክቶ ዝም ማለት መቻል የለበትም ፡፡ የስልጣን ተዋረዱን ጠብቆ ለሚመለከተው አካል በማሳወቅ ለሚጻፉት ጽሁፎች በሊቃውንተ ቤተክርስቲያን አባቶች ተመርምሮ መልስ እንዲሰጥበት ማድረግ ሃይማኖታዊ ግዴታ አለበት፡፡ ‹‹ዲ/ን›› አሸናፊ የሚባል ጸሀፊ  በርካታ መጽሀፎች የቤተክርስያኒቱን ስም በመጠቀም እንደጻፈ ይታወቃል ፤ አሁን ግብሩ ታውቆ ሳለ ከመጻፍ አልተቆጠበል ፤  መጻሕፍት ቸርቻሪዎች እና ለተሃድሶያውያን የምንፍቅና አካሄዳቸው ተባባሪ የታወቁ የካሴት ማከፋፈያ ሱቆች ውስጥ አሁንም እየተሸጠ ይገኛል፡፡ ስለዚህ ይህን የመሰሉ ሰዎች መጻህፍትም ከገበያ እንዲወጡ ምዕመኑም እንዳያነባቸው እና እንዳይመለከታቸው ማድረግ ይገባል፡፡


 

2 comments:

  1. ስንቱ በህርመትና በገድል በረድእነት ያገለገሉ መናንያን መነኮሳት የሚወዷትን ገዳማቸውን ጥለው የተሰደዱበት የኑፋቄ መጽሃፍ ቢዘገይም ተወግዞ ማየቱና መስማቱ የቅዱሳን አምላክ ይመስገን።ለርቱዓነ ሃይማኖት ሊቃውንትም ጸጋውን ያብዛላቸው አሜን።

    ReplyDelete