Sunday, March 25, 2012

ጠቅላይ ቤተክህነት የዋልድባ ገዳም እንደማይነካ ማረጋገጫ አግኝቻለሁ አለ

ሪፖርተር ጋዜጣ
  • በ11 ቀበሌ ገበሬ ማኅበራት ውስጥ የሚገኙ ቤተ ክርስቲያናት ሊፈርሱ ይችላሉ
  • የአሰቦት ገዳም ሆን ተብሎ በተለኮሰ እሳት እንደተቃጠለ ጥርጣሬ አለው
  • በገዳሙ የሚማር አንድ ሕፃን በኢሳ ታጣቂዎች ተገድሏል
ሰሞኑን መነጋገርያ ሆኖ የሰነበተው ጥንታዊው የዋልድባ ገዳም በስኳር ልማት ምክንያት እንደማይነካ ከመንግሥት ማረጋገጫ ማግኘቱን ጠቅላይ ቤተ ክህንነት አስታወቀ፡፡

በጥንታዊው የዋልድባ ገዳም ላይ መንግሥት ምንም ዓይነት የስኳር ልማት እንደማያካሂድ ቃል ስለገባ በሕዝበ ክርስቲያኑ ላይ የተፈጠረው ግርታ አግባብ አይደለም ቢልም፣ ከገዳሙ ውጭ ባሉ 11 ቀበሌ ገበሬ ማኅበራት ውስጥ የሚገኙና ቁጥራቸው ለጊዜው ግልጽ ያልሆኑ አብያተ ክርስቲያናት ሊፈርሱ እንደሚችሉ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ፍንጭ ሰጥቷል፡፡

በወልቃይት ቆላማ አካባቢ የሚኖሩት ሰዎች ከመኖርያ አካባቢያቸው ሲነሱ አብረዋቸው ማኅበራዊ ተቋሞቻቸውም እንደሚነሱ፣ የስኳር ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ዳይሬክተር አቶ ዓባይ ፀሐዬ ከጥቂት ቀናት በፊት መግለጻቸው ይታወሳል፡፡

ባለፈው ሐሙስ በጠቅላይ ቤተክህነት ጽሕፈት ቤት ከተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ መረዳት እንደተቻለው፣ በአካባቢው የሚኖሩ ሰዎች በሚነሱበት ጊዜ አብያተ ክርስቲያናት ብቻቸውን ስለሚቀሩ መፍረሳቸው ባይቀርም፣ ያም ቢሆን ግን ተፈጻሚ የሚሆነው ቤተ ክርስቲያኒቱ ስትስማማ እንደሆነ ነው፡፡

የጠቅላይ ቤተ ክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ ተስፋዬ ውብሸት ለጋዜጠኞች እንዳስታወቁት፣ ሊፈርሱ የሚችሉት ቤተ ክርስቲያናት ቁጥር ገና በግልጽ አልታወቀም፡፡ ከዋልድባ ገዳም አካባቢ የተሰሙ ወሬዎች ግን ከ18 ያላነሱ ቤተ ክርስቲያናት ሊፈርሱ እንደሚችሉ ይጠቁማሉ፡፡

መንግሥት የዋልድባ ገዳምን የከበቡትን ወንዞች በመጠቀም 76 ኪሎ ሜትር ስፋት ያለው ግድብ የሚሠራ ከመሆኑም በላይ፣ የሸንኮራ አገዳ የሚተክልበትን 50 ሺሕ ሔክታር መሬት እያዘጋጀ ይገኛል፡፡ 

ግድቡ ሲጠናቀቅ ለገዳሙ ከለላ በመሆን በሰዎችና በእንስሳት የሚደርስበትን ጫና እንደሚያስቀር የገለጸው ጠቅላይ ቤተክህነት፣ ከዚህ በተጨማሪ ገዳማውያኑ የዓሣና የመስኖ ልማት ተጠቃሚ እንደሚሆኑም አስታውቋል፡፡ የጥንታዊውን የዋልድባ ገዳም በተመለከተ ከመንግሥትም ሆነ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት የተሰጡ መግለጫዎችን በጥርጣሬ የሚያዩ አሁንም ስጋታቸውን እየገለጹ ነው፡፡ በአገሪቱ በርካታ ልማት ላይ የሚውሉ ቦታዎች እያሉ ዋልድባ ገዳም አካባቢ የስኳር ልማቱን ማካሄድ ለምን አስፈለገ ይላሉ፡፡

በሌላ በኩል በምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት የሚገኘው የአሰቦት ደብረ ወገግ ሥላሴና አቡነ ሳሙኤል ገዳም ላይ ሆን ተብሎ በተለኮሰ እሳት ቃጠሎ ሊነሳ እንደቻለ ያለውን ጥርጣሬ ያስታወቀው ጠቅላይ ቤተክህነት፣ ይህ ምናልባት የፖለቲካ ጥቅም ለማግኘት ሲባል ሊደረግ እንደሚችል በቦታው ተገኝተው ጉዳዩን ካጣሩት የቤተክህነት ኃላፊዎች መረዳት መቻሉን ገልጿል፡፡

ከዚህ ውጭ ደግሞ ገዳሙ ለኦሮሚያ፣ ለአፋርና ለሶማሌ ክልሎች አዋሳኝ በመሆኑ፣ አርብቶ አደሮች ዝናብ በሚጥልበት ወቅት አዲስ ሳር በቶሎ እንዲበቅልላቸው በማሰብ ደረቁን ሳር እሳት ስለሚለቁበት፣ እንዲሁም ከሰል አክሳዮች የለኮሱትን እሳት ሳያጠፉ እየሄዱ በሚቀጣጠል እሳት የአሰቦት ገዳም ላይ እሳት ሊነሳ እንደሚችል ጠቅላይ ቤተክህነት ግምቱን ተናግሯል፡፡ በሶማሌ ክልል ከሚገኙት የኢሳ ጎሳ ታጣቂዎች በተደጋጋሚ አደጋ ሲጣልበት የቆየው የአሰቦት ገዳም፣ የእሳቱም መነሻ ከዚያው ከኢሳዎች አካባቢ ሊሆን ስለሚችል መንግሥት ለገዳሙና ለገዳማውያኑ ህልውና ሲባል ጥበቃ እንዲያደርግ አሳስቧል፡፡

በአሰቦት ገዳም ከተነሳው እሳት ባሻገር ባለፈው ረቡዕ ዕለት በጠራራ ፀሐይ አንድ የአብነት ትምህርት ሲከታተል የነበረ የሰባት ዓመት ሕፃን በኢሳ ታጣቂዎች መገደሉን አስታውቆ፣ የገዳሙን ከብቶች የሚጠብቁ ታጣቂዎች ከኢሳ ታጣቂዎች ጋር የተኩስ ልውውጥ አካሂደው እንደነበር የገለጸው ቤተክህነት፣ የፌዴራል ፈጥኖ ደራሽ ፖሊስ መነኮሳቱን ባያስጥል ኖሮ የከፋ አደጋ ሊፈጠር ይችል እንደነበር አስረድቷል፡፡ ሦስቱም ክልሎች የራሳቸውን ጥበቃ እንዲያደርጉ በፓትርያርኩ በኩል በደብዳቤና በስልክ ከሚመለከታቸው ኃላፊዎች ጋር ግንኙነት መደረጉን የቤተክህነት ኃላፊዎች ገልጸዋል፡፡ 

የቤተክህነት ልዑካን በአሰቦት ገዳም ተገኝተው የእሳቱን መንስዔ እንዳጣሩና በገዳሙ ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት እንዳልደረሰ፣ ነገር ግን በርካታ አገር በቀል ዕፅዋቶችና የደን ይዞታዎች በከፍተኛ ሁኔታ ውድመት እንደደረሰባቸው መረጋገጡንና ምናልባትም ከሰው ዕይታ ተሰውረው የሚኖሩ መናኒያን የእሳቱ ሰለባ ሊሆኑ እንደሚችሉም አስረድቷል፡፡

እስካሁን በአሰቦት ገዳምም ሆነ በዝቋላ አቦ ደረሰው የእሳት ቃጠሎ ጉዳት መጠን በትክክል ያልታወቀ ሲሆን፣ በተለይ በአሰቦት ገዳም እስከ 13 ሔክታር የሚሸፍን ደን በቃጠሎ እንደወደመ መነኮሳት እንደሚገልጹ የተናገሩት የቤተክህነት ኃላፊዎች፣ የጉዳቱ መጠን በባለሙያዎች ተጠንቶ ይፋ እስከሚደረግ በመጠባበቅ ላይ እንደሚገኙ አስረድተዋል፡፡

4 comments:

  1. May God be with us!!!

    ReplyDelete
  2. This is totally insane to destruct CHURCHES!!! These are churches - which we all hope and take part. yekiristosin akal lemafres lemin tenesasu. INDET GIN LIHON YICHILAL. YIHEN SEMTO ZIM YEMIL JORO YEKIRISTIAN JORO MEHON AYCHILIM. BETEKIRISTIAN FERSO KIRISTINA WEYIM HIYWET WEYIM MENGIST YELEM. PLEASE PETITION!!!

    ReplyDelete
  3. 18 bete kerestiyanoch????????????????? betam bezu nachew degemo betekeresetiyan sinefeleg yeminafersew sinefeleg degmo bemanegnawem bota yemenegenebaw ayidelem geta lebetekeresetiyan belo yekedesate, yakeberat botalayi eneseralen enji.......... becha yebetekeresetiyan amlak betekerestiyanochin tebik kemeferesim tadegachew amen

    ReplyDelete
  4. lets strongly pray GODwill hear us

    ReplyDelete