Saturday, October 17, 2015

“ይድረስ ለቸልተኛው ሲኖዶስ”!


  • የሐዋርያት ጉባኤ ስለሆነች ስለአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሰላም እንማልዳለን! (መጽሐፈ ሚስጢር)
  • ‹‹በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ!›› የሐዋርያት ሥራ 2028
  • ተሀድሶያውያን ጳጳሳቱን ፊት አስቀምጠው በዘመናዊ የሙዚቃ መሳሪያ(ኦረጋን) መዝሙር ሲያቀርቡ የሚያሳይ  ሙሉ videoውን YouTube ላይ ለማየት ይህንን አያያዥ ይጫኑ https://youtu.be/Mo2p3lpcTtI 
                                                                             ቢኒ ዘልደታ

(
አንድ አድርገን ጥቅምት 06 2008 ዓ.ም)፡-  ተሃድሶን ከዚህ በላይ መታገሱ ከተሃድሶነት የተሻለ ስም አያሰጥም! ዛሬ ያለ አሽሙር፣አንድም ያለ ስላቅ በቀጥታ ቅዱስ ሲኖዶስ በዚህ ሰዓት ምን እንደሚያስብ ምን እንደሚሠራ መጠየቅ እፈልጋለሁ!
ይህ ጥያቄዬ የመጀመሪያዬ አይደለም የመጨረሻዬም አይሆንም! ይህ ተሃድሶ የተባለ ክፉ ነቀርሳ ከደጀ ሰላማችን እስካልተነቀለ ድረስ እቀጥላለሁ! ይህ የበላበትን ወጭት ሰባሪ ቡድን ከቤታችን ተጠራርጎ እስካልወጣ ድረስ እቀጥላለሁ! ይህ የጠባውን ጡት ነካሽ ክፉ ባንዳ የአባቶቼን ርስት፤ የናቡቴ እርሻ ለቆ እስካልተሰደደ ድረስ እቀጥላለሁ! ለዚህ ሁሉ የተሃድሶ ቡድን መደራጀትና የልብ ልብ ማግኘት ብቸኛ ተጠያቂው ደግሞ ቅዱስ ሲኖዶስ ነው!

አሁን እየሆነ ያለውን ሰፊ የተሃድሶ ዘመቻ ቅዱስ ሲኖዶሳችን አላየውም አልሰማውም አልልም! ዓይቶና ሰምቶ ዝምታው መርዘሙ ነው ግራ የገባኝ!
ተሃድሶ ከትላንት ይልቅ ዛሬ ግልጽ የሆነ አቋሙን በማንጸባረቅ ላይ መሆኑን እያየንም እየሰማንም ነው። ቀድሞ ለአመል ፣ለማታለያ እና መመሳሰያ ያህል ይነካካ የነበረውን የኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ዛሬ በግልጽ ስለ ድንግል ማርያም አንሰብክም፣አንዘምርም ነገር ቅዱሳን ለመዳን ትርጉም የለውም፣ብቸኛው መንገድ የሉተር አስተምህሮ ኢየሱስ...ኢየሱስ ብቻ ነው እያለ ሲያጋሳብን እኔም እናንተም ሲኖዶሳችንም እኩል ሰምተነዋል።

ቀድሞ ውስጥ ለውስጥ አንታይም አንሰማም እያሉ ኑፋቄን አሹልከው ሲያስገቡ የነበሩት ተሃድሷውያን ዛሬ በቫይበር፣በዋትሳፕ፣በፌስ ቡክ እና መሰል ሚዲያዎችን በመጠቀም በቀጥታ ‹‹ድንግል ማርያም አታማልድም፣የውርስ ኃጢአት አለባት፣የክርስቶስ ሥጋና ደም ለመታሰቢያ እንጂ ለመዳን ትርጉም የለውም፣ቅዱሳን በአጸደ ሥጋም ሆነ በአጸደ ነፍሥ አያማልዱም፣መዝሙር በሙዚቃ መሣሪያ እናወጣለን……›› የሚሉና የመሳሰሉ የሉተራውያንን ትምህርት ለየዋሃን ሲያድሉ እኛም ሲኖዶሱም እኩል ዓይተናል ሰምተንማል

ከምንም በላይ ዘወትር እሑድ በኢቢኤስ ቴሌቪዥን የሚሰራጨው ግልጽ የተሃድሶ የምንፍቅና ትምህርት ሲኖዶሱ በምን ዓይነት ሁኔታ እንደሚመለከተው እና መቼ እልባት እንደሚሰጠው ይናፍቀኛል። አባቶቻችን ይህን ጣቢያ እየተማሩበት ነው ወይስ እየመረመሩት???
በቤተክርስቲያናችን ስም የሚነግዱ እንደነ አሰግድ፣በጋሻውና መሰሎች እንፈውሳለን እያሉ የሴት እህቶቻችንን ሲያሻሹ እያዩ ምን እንደሚጠብቁ አይገባኝም??? እንደነ ቅዱስ ኤፍሬምና ቅዱስ ያሬድ የመሳሰሉ ሊቃውንት ምሳሌ ያጡላት የእናታችን የድንግል ምርያምን ስዕለ አድኅኖ ከእግራቸው ትቢያ ሥር በድፍረት ሲያኖሩት እኛም ሲኖዶሱም እኩል አይተናል ሰምተንማል!
ይህን ሁሉ ስናይ እና ስንሰማ ከሥርዓት አንጻር እኛ የዚህን አካል እኩይ ተግባር ከማጋለጥ የዘለለ ዐቅም የለንም ነገሩን መርምሮ ይህን አጥፊ አካል ከተቻለ መክሮና ዘክሮ የመመለስ ሲቀጥልም ከቤተ ክርስቲያኒቱ የማግለል ኃላፊነትም ግዴታም ያለበት ቅዱስ ሲኖዶስ ሲሆን ምን እየጠበቀ እንደሆነ ሊገባኝ አልቻለም!

ይህን አካል ለማውገዝና ከቤተ ክርስቲያኒቱ ለማስወገድ ቅዱስ ሲኖዶስ ከፍተኛ መለሳለስ ታይቶበታል። ይህም ቀላል ለማይባሉ ዓመታት የተስተዋለ ችግር ሲሆን ብዙዎች ‹‹ሲኖዶስ የለንም!›› እስከማለት ድረስ ተስፋ ቆርጠውበታል እኔን ጨምሮ።

ይህ ሁሉ የሆነው ደግሞ እዛው ጠቅላይ ቤተ ክሕነት ውስጥ በተሰገሰጉ ዕልፍ አማሳኞች ነው። ይህን ሃሳብ የሚያጠናክርና ተሃድሶ አዚሙን ጠቅላይ ቤተ ክሕነት ድረስ መርጨቱን የሚያሳዩ ብዙ ምልክቶችን አሉ። ከነዚህም ውስጥ፡

1) ምንፍቅናቸው የተረጋገጡ ሰዎች በተለያዩ ደብራት አስተዳዳሪ ተደርገው በሲኖዶሱ ጳጳሳት መሾማቸው፣

2) እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት የደብር አስተዳዳሪዎችና ግለሰቦች በማስረጃ ምንፍቅናቸው በተጋለጠ ጊዜ ከፓትርያርኩ ጀምሮ (የቀድሞውም ይሁኑ ያሁኑ) ከለላ በመስጠት በሕግ እንዳይጠየቁ በማድረግና ነገሩን መሸፋፈን። ለምሳሌ ሽጉጥ ታጣቂውና የራሱን አዳራሽ በመሥራት ቤተ ዕምነት ከፍቼ የማጥመቅ ሥራን እየሰራሁ ነው በማለት ግልጽ ፓስተርነቱን ለሚዲያ ጭምር የተነፈሰው አቶ ጌታቸው ዶኒ አንዴ በቃሊቲ ደብረ ቁስቋም ኋላም በሐዋሳ ቅዱስ ገብርኤል በደብር አስተዳዳሪነት የተሾመው በፓትርያርኩ ነው።
 
ይህ ግለሰብ ለሙሉ ወንጌል አባል ለመሆን የጻፈው ደብዳቤ እና የመሳሪያ ታጣቂነት ፍቃድ ጭምር በወቅቱ ለፓትርያርኩ በእጅ የተሰጠ ቢሆንም ሲኖዶሱ አይቶም ሰምቶም እርምጃ አለመውሰዱ ያሳፍራል።

ከዚህ ባለፈም አባ ሰረቀ ተብዬው የቀድሞውን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የአሁኑን ማኅበረ ቅዱሳን የበላይ ጠባቂ እንዲሆን ሲመደብ መናፍቅና አማሳኝ መሆኑን ፓትርያርኩ በግልጽ ያውቁ ነበር ለምን ዝም አሉ??? 

የሚያሳዝነው ደግሞ በቤተ ክርስቲያኒቱም ሆነ በመንግሥት ስሙ በህግ ተመዝግቦ የሚገኘውን የማኅበረ ቅዱሳንን ስም በማጥፋታቸው ማኅበሩ ክስ መሥርቶ አባ ሰረቀን ለሕግ ባቀረበበት ወቅት አባ ጳውሎስ በአንዲት ደብዳቤ ክሱ እንዲሣሳ እና አባ ሰረቀ ነጻ እንዲወጡ ለፍርድ ቤት በመጻፋቸው ይህ ግለሰብ ከሕግ ጥላ ሥር ወጥቶ ዛሬም ሲኖዶሱን እያወከ እነዲኖር እና ማኅበረ ቅዱሳንን እንዲያብጠለጥል ድጋፍ ተሰጥቶታል ይህን ማድረግ ለምን አስፈለገ???

3) በቅዱስ ሲኖዶስ እና ጠቅላይ ቤተ ክሕነት ስም በሃሰት የተዘጋጁ ብዙ ደብዳቤዎች በተሃድሶ መናፍቃን እጅ እንደሚገኙ እና ከዛው ከቅዱስ ሲኖዶስ በሙስናና በድብቅ ተጽፈው ለነዚህ ግለሰቦች መሰጠቱን እያወቀና እየሰማ ምንም ዓይነት እርምጃ አለመውሰዱ ዐውቆ የተኛን……ዓይነት ያስተርታል። በተለይ እነዚህ በተሃድሶ መናፍቃን እጅ የሚገኙት የሃሰት ደብዳቤዎች ‹‹ለመስበክ ተፈቅዶልናል….ይቅርታ ተደርጎልናል…..ከሲኖዶስ ተጽፎልናል…….›› የሚሉ በመሆናቸው ብዙሃኑን ምእመን ለማታለል ረድቶአቸዋል። ይህንንም እውነት እኛም ሲኖዶሱም አይተነዋል ሰምተነዋል ግን ዝምታው ለምን ???

4) በአዲስ አበባ ቅዱስ ዮሴፍ፣በገጠሪቱ አንዳንድ አቢያተ ክርስቲያናት እና በተለያዩ የአውሮፓና ሰሜን አሜሪካ ግዛቶች በተለይም በዱባይ መሽጎ በገዛ ዐውደ ምሕረታችን ላይ ተሃድሶ ያለከልካይ ምንፍቅናውን ሲዘራ ቅዱሳኑን ሲሰድብብን፣ድንግል እናታችንን ሲያጣጥልብን፣ከዘፈን የተቃኘ ረገዳውን ሸክፎ አዝማሪ ቤት ሲያስመስልብን እኛም ሲኖዶሱም አይተናል ሰምተንማል ግን ለምን ዝም ተባለ ???

5) ቤተ ክርስቲያን በዘመኗ አድርጋ በማታውቀው መልኩ የአዳራሽ የመናፈሻ እና የሆቴል ጉባዔያት ተጥለቅልቃ ሳለ እያየም እየሰማም ከዝምታ ያልዘዘለለ እርምጃ አለመውሰዱ ሲኖዶሱ ቀደምት ዘመናትን በተሞክሮ ወስዶ እንደ ሠለስቱ ምዕት ጉባዔ ሠርቶ ሃሰተኞችን ከማውገዝ ይልቅ ለዚህ አጥፊ አካል ይበልጥ መንሰራራት ጉልበት ሲሰጥ ተስተውሏል ለምን ??? ደግሞስ ይህ ሁሉ ምንፍቅና በገሃድ እየታየ ሲኖዶሳችን የትኛው ፕላኔት ላይ ያሉ መንጎችን ነው እየጠበቀ ያለው ???
እንግዲህ ለዚህ ሁሉ የተሃድሶ መንሰራራት ብቸኛው ተጠያቂ ሲኖዶሱ እንጂ ማንም ሊሆን አይችልም! የእኛ ኃላፊነት እራሳችንን ከዚህ አጥፊ አካል መጠበቅ ሲሆን ቤተ ክርስቲያኒቱን ከነምእመኗ መታደግ ደግሞ ድርሻው የሲኖዶስ ነው። አሁንም ቅዱስ ሲኖዶስ በዋናነት ትኩረቱን ያደረገው በሙሰኞች ላይ ብቻ ሲሆን የበለጠ አንገብጋቢውን የተሃድሶ እንቅስቃሴ ይዋል ይደር ሳይል ፈጥኖ ውሳኔ ማስተላለፍና በጎቹን መታደግ አለበት

ዛሬ ታዖሎጎስና እና ቃለ ዓዋዲ በተሰኙት የተሃድሶ መናፍቃን እስትንፋሶች ላይ በቤተ ክርስቲያናችን ስም እየተነገደ የሚገኝ ሲሆን አሳሳቢው ጉዳይ ደግሞ በእነዚህ ጣቢያዎች ላይ ዘወትር አዳዲስ ፊቶች ብቅ ብቅ ማለታቸው በየጊቢው፣በየክልሉና በየአዳራሹ በከፍተኛ ስልታዊ ዕቅድ የተሃድሶ ስልጠና የወሰዱ ሰዎች መሆናቸው አያጠራጥርም! ታዲያ ጠላት እንዲህ ጉልበቱን አግዝፎ መንጋውን ለመውረር ዘምቶ ሲያበቃ የሲኖዶሱ ዝምታ ምን እንስክንሆን እና ምን እስኪፈጠር እንደሆነ አልገባኝም

በቅርቡ ቤተ ክርስቲያኒቱን ሲመዘብሩ ቆይተው ሸንጎ የቀረቡትን ሰዎች እና ዛሬ አውደ ምህረቱን የሙሉ ወንጌል አዳራሽ አስመስለው የሚፈነጩበትን ተሃድሷውያን የማርያም መንገድ የሰጣቸው ማነው?? ምእመኑ ነው ወይስ ሰበካ ኩባዔው??? ሰንበት ተማሪው ነው ወይስ ማን ??? ብቸኛው ተጠያቂ ነገሮችን በርቀትና በትዝብት እየተመለከተ ያለው ቅዱስ ሲኖዶስ ነው!!! እነዚህ ተሃድሷውያን ‹‹ሎይድ›› በተሰኘው መጽሔታቸው ላይ በሲኖዶሱ መዘናጋት እና በእነርሱም ላይ ውግዘትን ባለማስተላለፉ ደስታቸውን ሲገልጹ፡- ‹‹ለመንጎቹ የሚጨነቀው ሲኖዶስ›› በማለት አሞካሽተውታል። ይህ ደግሞ በሲኖዶሱ ዝምታ እነዚህ አጥፊዎች ምንኛ ከለላ እንደተደረገላቸው ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ ሃቅ ነውና ሲኖዶሳችን ይንቃ!!! 

አሁንም እንላለን በዚህ ተጋግሎ በቀጠለው የተሃድሶ መናፍቃን ዘመቻ ላይ ቅዱስ ሲኖዶስ ያለውን አቋም ለምእመናን የማሳወቅ ኃላፊነትም ሆነ ግዴታ አለበት!!!

ተሀድሶያውያን ጳጳሳቱን ፊት አስቀምጠው በዘመናዊ የሙዚቃ መሳሪያ(ኦረጋን) መዝሙር ሲያቀርቡ የሚያሳይ  ሙሉ videoውን YouTube ላይ ለማየት ይህንን አያያዥ ይጫኑ https://youtu.be/Mo2p3lpcTtI 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን-ይቆየን።

ሻሎም!!!

7 comments:

  1. አቦ ወንጌል ስበክ አሁንም መንገዱ ኢየሱስ ነው ሌላ የለም ይቅርታ የኔ ሳይሆን የሐዋርያት ት/ርት ነው ሐዋ 4 ;12

    ReplyDelete
    Replies

    1. 1ኛ ወደ ተሰሎንቄ ሰዎች
      5፥14
      ወንድሞች ሆይ፥ እንመክራችኋለን፤ ያለ ሥርዓት የሚሄዱትን ገሥጹአቸው፤ ድፍረት የሌላቸውን አጽኑአቸው፤ ለደካሞች ትጉላቸው ።የሚለውን የወንጌል ቃል አታውቀውም እንዴ? ነው ወይስ የሐዋርያውን ቃል አትቀበለውም? ለነገሩ መናፍቃን ከወንጌሉ ቃል ያልተመቻችሁ ካለ አትቀበሉም፡፡

      Delete
  2. ጊዜ የሰጠው ቅል ድንጋይ ይሰብራል ይባላል። ለማለቱ ለማንቂያ ያህል መፃፍህ በርታ የሚያሰኝ ነው። ወንድሜ ጌታን አሳልፎ ማን ሰጠው? ይህ ይሆን ዘንድ ደግሞ ግድ ነው " ለመንጋው የማይራራ" ነው እኮ ጌታ ያለን። የሚያስፈልገን አሁን መፆም መፀለይ ነው እመ አምላክን ይዘን መጠየቅ የእናት ልመና አንገት አያስደፋ፣ ፊት አያስመልስ አይደል። ሰዓታቸው ስለሆነ እኮ ነው እራሳቸውን ያጋለጡት፣ ነገ ደግሞ ስም ዝርዝር ይነግሩናል የአባላቶቻቸውን፣ እናም እከሌም ልንል ሳይሆን አዎ ይሁዳም እኮ አብሮት ከጌታ ጋር ነበር እንላለን። "አብ ያልተከለው ሁሉ ይነቀላል" ዛሬ የሚያስፈልገው እኔ እኔ እኔ ቤቴን እጠብቃለሁ፣ ለቤቴ ከኔ የሚጠበቀውን እኔ ላድርግ እነ ዮዲት እነ ግራኝ ያላጠፏትን ማንም ንክች አያደርጋትም ጠባቂዋ አያንቀላፋም። እንግዲህ ፅዳቱን እንደሆነ ከቤቴ እጀምራለሁ ያለው አምላካችን ቤቱን ጥርት አድርጎ ያፀዳዋል። አምላከ ቅዱሳን እነዚህ አፅራረ ሐይማኖቶች( ሀራጥቃ) ከስራቸው ነቅሎ ይጥልልን ዘንድ ፈቃዱ ይሁንልን። አሜን።

    ReplyDelete
  3. የአባቶች ዝምታ እጅግ በጣም ገርሞኛል ለምድራዊው ንጉስ ነው እንዴ የተቀመጡት ባይሆንማ ምርጫው በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ቢጠናቀቅ ይሄ ሁሉ ሀራጥቃ በቤተክርስቲያናችን ላይ ባልፈነጨ ነበር እይወታቸውን የሰውላትን አባቶች ለነሱ ሲል እግዚአብሔር እምላክ እጽራረ የቤተክርስቲያንን ጠራርጎ ያስወግድልን አሜን!!!

    ReplyDelete
  4. bert lega enzhen ynat tut nkaswechen lebanachewn eskmales zam atble abatochacenm agaz yfelegalew ymtkmi achwen kganach naz ymlachaw leg ylabachawen tsenow tawkew yall bchacwen benagarew sam ylam ymenmenan dems klalabtna egezabher kalredachew bcha bert egezabher ytabkh ewntawen new ycafkew kdengl Maryam yasrat lege andaw!!

    ReplyDelete
  5. ጐበዝ አባቶች ተሀድሶ ከሆኑስ

    ReplyDelete
    Replies
    1. አይዞህ ስጋት አይግባህ ሁሉም ሊሆኑ አይችሉም

      Delete