Monday, July 15, 2013

በዋልድባ ገዳም የሚገኝው የሥኳር ፕሮጀክት ነዳጅ ማራገፊያ የመሬት መንሸራተት አጋጠመው



(አንድ አድርገን ሐምሌ 8 2005 ዓ.ም)፡- መንግሥት በአምስት አመቱ የእድገትና የትራንስፎርሜሽን ዘመኑ ውስጥ በ32 ቢሊየን የኢትዮጵያ ብር በላይ  አስር የሥኳር ፋብሪካዎች በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ውስጥ እገነባለሁ ብሎ በእቅድ መያዙ ይታወቃል ፤ መንግሥት ከፍተኛ አትኩሮት ከሰጣቸው ፕሮጀክቶች ውስጥ ከታላቁ የህዳሴ ግድብ በኋላ የሥኳር ፕሮጀክቶቹ በሁለተኝነት ይገኛሉ፡፡ ከእነዚህ የስኳር ፋብሪካዎች ውስጥ ብዙ ውዝግብ ያስነሳው ፤ ብዙ ዋጋ ያስከፈለው አሁንም እያስከፈለ ካለው የሥኳር ፋብሪካ ውስጥ በዋልድባ ገዳም የሚገነባው አንዱ ነው፡፡ እነዚህን ፕሮጀክቶች በበላይነት የሚመራው መቀመጫው መሀል ካሳንቺስ ያደረገው በአቶ አባይ ጸሀዬ የሚመራው የስኳር ኮርፖሬሽን መሆኑ ይታወቃል፡፡ ከፕሮጀክቶቹ አንዱ እና ዋንኛው የሆነውን የዋልድባን የስኳር ፋብሪካ ግንባታን በመቃወም ብዙ መነኮሳት ከበአታቸው በመሰደድ በያሉበት ሆነው ስራውን እየተቃወሙ ይገኛሉ ፤ ፕሮጀክቱን ለመስራት በየጊዜው የሀገር ውስጥና ከሀገር ውጭ የመጡ ኮንትራክተሮች ውል በመቋጠር እንደገና በመፍታት አሁን ላይ ሶስተኛው ስራ ተቋራጭ ስራው እያካሄደ እንደሚገኝ ይታወቃል፡፡ 


መንግሥት በትላልቅ ፕሮጀክቶች ስራቸው እንዳይተጓጎል ለማድረግ ከየትኛውም ፕሮጀክቶች በተለየ መልኩ ከብሔራዊ ነዳጅ ማከማቻ ጋር የተለየ ውል መያዙን የውስጥ ሰዎች ይገልጻሉ ፤ ለአንድም ቀን ይሁን እነዚህ ፕሮጀክቶች ላይ የሚሰሩ መኪናዎችና የተለያዩ በነዳጅ የሚሰሩ መሳሪያዎች ስራቸው እንዳይስተጓጎል በመጀመሪያ ደረጃ በተለየ ምልከታ የነዳጅ ፍላጎታቸው በየጊዜው እንደሚቀርብላቸው ምንጮች ያስረዳሉ፡፡


ይህ በእንዲህ እያለ ከሳምንታት በፊት በዋልድባ ገዳም እየተሰራ ለሚገኝው የሥኳር ልማት ፕሮጀክት አንድ ከነተሳቢው ነዳጅ የጫነ መኪና ከአዲስ አበባ ወደ ዋልድባ የጫነውን ነዳጅ ለማራገፍ ወደ ቦታው ያመራል ፤ ቦታው ላይም ነዳጅ የጫነው መኪና በጊዜው መድረስ ችሎ ነበር ፤  ነገር ግን ነዳጅ የጫነው መኪና በጊዜው ቢደርስም ነዳጁን ለማራገፍ በሚሞክርበት ጊዜ ከመሬት ስር የተቀበረው ነዳጅ ማራገፊያ በመሬት መንሸራተት ምክንያት ከዋናው ቦታ መሸሹን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በዚህ ምክንያትም ነዳጁን የያዘው መኪና በመሬት መንሸራተት ምክንያት ቦታውን ያጣውን ነዳጅ ማከማቻ ወደ ቦታው የመመለስ ስራ እስኪሰራ እና ለመገልበጥ ሁኔታዎች እስኪመቻቹ ድረስ ለ21 ቀናት በቦታው ላይ መቆሙን ለማወቅ ተችሏል፡፡


እግዚአብሔር በአንድም በሌላም መንገድ ይናገራል ፤ በዋልድባ ከፕሮጀክቶቹ ጋር ተያይዙ ብዙ ምልክቶች እየታዩ ይገኛሉ ፤ ላስተዋለ አንድም ምልክት በቂ ነበር ላላስተዋለ እንደ ፈርኦን አስራ አንድ ምልክት ቢከታተል ልቡ ደንድኗልና የመጨረሻውን ምልክት እስከሚያይ ድረስ ፤ ባሕረ ኤርትራ ተከፍቶ እስኪውጠው ድረስ ከጥፋት ስራው ሊመለስ አይችልም ፤ መጽሀፉ ‹‹ ማንም የቆመ ቢመስለው እንዳይወድቅ ይጠንቀቅ›› ይላል፡፡


እግዚአብሔር ዋልድባ ገዳምን ይታደግልን፡፡

1 comment: