Saturday, January 10, 2015

ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን የምትደግፋቸውና የምትቃወማቸው ሳይንሳዊ ጉዳዮች

  
ብጹዕ አቡነ ሳሙኤል በኢትዮጵያ ኦርዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሃይማኖታዊ እና ሌሎች ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ከ18 በላይ መጽሐፍትን በአማርኛና በእግሊዝኛ ጽፈዋል፡፡ ካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲም ‹‹ዲክሽነሪ ኦፍ ክርስቲያን ኢዲሽን›› የተሰኝውን መጽፍ አሳትሞላቸዋል፡፡ በቤተ ክርስቲያኗ የፀረ ውርጃ ፤ ጽንስ ማቋረጥ ፤ እና ግብረሰዶም እንቅስቃሴ ድምጻቸው ጎልቶ ከሚሰሙ አባቶች ግንባር ቀደሙ ናቸው፡፡ የሜዲካል መጽሔት ዘጋቢ አጥናፉ አለማየሁ በዚህ እና  ተዛማጅ ጉዳዮች ላይ አቡነ ሳሙኤል አወያይቷቸዋል፡፡


ሜዲካል፡-  ፅንስ ማቋረጥን በተመለከተ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ያላት አቋም ምንድነው?
አቡነ ሳሙኤል፡- ፅንስ ማቋረጥን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ትቃወመዋለች ፤ አስተምህሮዋና ቀኖናዋም ይቃወማል፡፡ ምክንያቱም ፅንስ የሰው ዘር በምድር ላይ እንዲበዛ እግዚአብሔር ስለፈቀደ ‹‹ብዙ ተባዙ አላቸው ባረካቸውም›› ዘፍ 1፤28 ባለው አምላካዊ ቃል መሰረት  የሚገኝ በረከት ነው፡፡ ስለሆነም ፅንስ ገና ያልታየና ያልተወለደ ቢሆንም  ከእግዚአብሔር ሕይወት የተሰጠው ፍጡር ነው፡፡ ‹‹ከእናቴ ማሕፀን ጀምሮ አንተ አምላኬ ነህ›› መዝ 21፤9  ‹‹ከማሕፀን ጀምሮ በአንተ ተደገፍኩ ፤ ከእናቴ ሆድ ጀምሮ መሸሸጊያዬ ነህ›› መዝ 70፤6 እንደተባለው ሁሉ ፅንስ የእግዚአብሔር ጥበቃና መግቦታ ያለው ነው፡፡

እግዚአብሔር በፈቀደ ጊዜ ለወደፊት ሥጋዊም ሆነ መንፈሳዊ ተልዕኮ ያለው እንደሚሆን በእግዚአብሔር ዘንድ ዕውቅና  የተሰጠውና የመኖር መብት ያለው ነው፡፡ ስለሆነም ከዚህ በላይ በተገለጸው አምላካዊ ቃል መሠረት ፤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ፅንስ ማቋረጥን አጥብቃ ትቃወማለች፡፡(ዘጸ 20፤13)

ሜዲካል፡-   የእናቲቱ ሕይወት አስጊ በሆነ ደረጃ የሚገኝ ፅንስ እንዲቋረጥ ቢደረግ ምን ችግር ወይም ኃጢያት አለው?
አቡነ ሳሙኤል፡- አንዱን ሕይወት ለማዳን የሌላውን ሕይወት ማጥፋት በቀኖና ቤተ ክርስቲያን የሚደገፍ አይደለም፡፡ ሁሉንም ለማዳን የሚቻለው ያህል ጥረት ማድረግ ሃይማኖታዊም ሰብአዊም ግዴታ ነው ፤ ከሰው ዕውቀትና አቅም በላይ የሚሆነውን ግን ሁሉን ማዳን ለሚቻለው አምላክ መተው ነው እንጂ ፤ አንዱን ለማዳን ሌላውን መግደል የሚለውን ሀሳብ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አትቀበለውም፡፡ ምክንያቱም ከላይ እንደተገለጸው

1ኛ . ፅንሱ ከእናቱ ማሕፀን ጀምሮ በእግዚአብሔር ዘንድ ዕውቅና የመኖር መብት ያለው ሕያው ፍጡር ስለሆነ
2ኛ. በሰው በኩል የሚቻለውን በሰው አማካይነት ፤ ከሰው እውቀትና አቅም በላይ የሆነውን በራሱ በአምላካዊ ስልጣን ማዳን የሚቻለው እግዚአብሔር ብቻ ስለሆነ ነው፡፡ (ዘዳ 42፤48) ስለዚህ በመጀመሪያ ሴቶች ለመጸነስ ሲፈልጉ ሕገ እግዚአብሔርን መጠበቅ ፤ ሕገ ተራክቦን ማክበር ፤ ከዚያም ጤነኛና በትክክል የእርግዝና ሒደት ውስጥ የሚገኝ ልጅ  እንዲሰጣቸው በጸሎት ፤ በጾም ፤ በሰጊድ ፤ በምጽዋትና  በንስሐ ፈጣሪን መጠየቅና ህሊናን ማዘጋጀት ፤ ከተለያዩ ሱሶች ራስን መጠበቅ ይገባል፡፡ ‹‹ የተባረከ እና ጤነኛ ፅንስ አድርግልኝ ፤ መልካም ልጅ ፈጣሪውን የሚፈራ ፤ እናት አባቱንና ሰውን ሁሉ የሚያከብር ልጅ ስጠኝ ›› ብሎ መለመን ይገባል፡፡ይህ ደግሞ በወንዱም ሆነ በሴቷ በኩል ሊደረግ የሚገባው ልመና ነው፡፡ በመሆኑም ሰዎች አስጊ ነው ያሉት ላይሆን ይችላል፡፡ ጤነኛ ነው ያሉት ደግሞ ችግር ሲፈጠር ይታያልና ፤ በሥጋት ብቻ ፅንስ እንዲቋረጥ ሕይወት እንዲጠፋ ማድረግ ተገቢ አይደለም፡፡

ሜዲካል፡-ቤተ ክርስቲያኒቱ በቤተሰቦችና ዘመዳሞች መካከል ጋብቻ እና ሩካቤ የተከለከለ መሆኑን ታምናለች፡፡ በአሁኑ ወቅት ግን በሀገራችን በቤተሰብና በዘመዶቻቸው ተደፍረው የጸነሱ እንዳሉ የፖሊስና የሌሎች መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ እናም አንዲት ሴት በአባቷ  ወይም በወንድሟ መደፈር ያጋጠማትን ፅንስ ብታስወርድ ኃጥያቷ ምን ላይ ነው?
 
አቡነ ሳሙኤል፡- በቅዱሳት መጻሕፍትና በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ከጋብቻ እና ከግብረ ሥጋ ግንኙነት የሚከለከሉ የሥጋ ዝምድና ፤ መንፈሳዊ ዝምድና (አበ ልጅነት) ፤ የጋብቻ ዝምድና እና የማደጎ ዝምድና ናቸው፡፡ እነዚህ የዝምድና ሕጎች እንዲጠበቁ ቤተ ክርስቲያን ታስተምራለች፡፡ እነዚህ የዝምድና ሕጎች ተሽረው ቢገኙ የዝምድና ሕጉን በሻሩ ወገኖች ላይ ቀኖናዊ ቅጣት ትወስናለች እንጂ ዝምድናውንና የዝምድናውን ሕግ መሻሩን ሳያውቅ ባጋጣሚ በተፈጠረው ፅንስ ላይ የሚሰጥ የሞት ፍርድን ኦርቶዶክሳዊት  ቤተ ክርስቲያን አጥብቃ ትቃወማለች፡፡ ምክንያቱም ከላይ እንደተገለጸው ዝምድና ከማፍረስ ከተፈጸመው ኃጥያት በላይ የበለጠ ነፍስ የመግደል ወንጀል መፈጸም ስለሚሆን ነው፡፡(ዘጸ 20፤13) ስለዚህ ከዘመድ ተጸነሰ በሚል ሰበብ ፅንስ ማስወረድ ወይም ማቋረጥ በኃጥያት ላይ ኃጥያት መጨመር ነው፡፡

ሜዲካል፡- በሀገራችን በእናቲቱ ዘላቂ ጤንነትና ሌሎች አስገዳጅ በሆኑ ሁኔታዎች የሚፈጠርን ፅንስ  ማቋረጥ እንደሚቻል በከፊል በሕጓ ተቀብላለች ፡፡ በዚህ ላይ የቤተ ክርስቲያኗ አቋም ምንድነው?
 
አቡነ ሳሙኤል፡- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በቅዱሳት መጻሕፍትና  በቀኖናዊ አስተምኅሮዋ አስቀድሞ በዝምድና መካከል የግብረ ስጋ ግንኙነት እንዳይፈጸም አስገድዶ መድፈርና ያለ እድሜ ጋብቻ  እንዳይኖር ታስተምራለች ፤ ትከለክላለች እንጂ በማንኛውም ምክንያት ፅንስ ከተፀነሰ በኋላ የማስወረድና የማቋረጥ ተግባር አትቀበልም፡፡ ስለዚህ የበደለ የበደለውን እንዲክስና እንዲቀጣ የተበደለም ሊካስ እንደሚገባ የሚያመለክተው ሕግ አጠንክሮ ተግባራዊ የሚያደርግ መመሪያ ማውጣት ሲገባ ፤ ምንም ያልበደለ ሕይወትን ማጥፋት ወንጀል አይደለም የሚል ሕግን ማውጣትና ማወጅን ፤ ቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አጥብቃ ትቃወማለች፡፡

እንዲሁም በዝምድና መካከል በተደረገ የግብረ ስጋ ግንኙነት በሚለው ሁኔታ የሚፈጠር ፅንስንም ማቋረጥ ወይም ማስወረድ ወንጀል እንደማይሆን መገለጡ በሕገ ተፈጥሮም ፤ በሕገ ሃይማኖትም የሚደገፍ አይደለም፡፡ ምክንያቱም የጥፋት ውሳኔ ሲሰጥ  እንጂ ምንም ሳያውቅ በተፈጠረ ፅንስ ላይ የሞት ፍርድ የሚፈቅድ ሕግ ማውጣት ትክክል ነው ብላ  ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ስለማታምን ነው፡፡

ሜዲካል፡-   ከዚሁ ጋር የተያያዘው ቤተሰብ መመጠን ነው፡፡ ቤተሰብን ለመመጠን የሕክምና ሳይንስ የደረሰበትና በመላው ዓለም ተቀባይነት ያገኝው የፅንስ መከላከያ ኪኒን ወይም መርፌና ኮንዶም መጠቀምን ነው፡፡ በዚህ ላይ ቤተ ክርስቲያኗ ምን ትላለች?

አቡነ ሳሙኤል፡- ይህንንም ቅድስት ቤተክርስቲያን አትቀበለውም ፤ ምክንያቱም ‹‹ብዙ ተባዙ›› (ዘፍ 1፤28) ያለውን የፈጣሪን ትዕዛዝ መቃወም ስለሚሆን ነው፡፡  በተጨማሪም ተግባሩን እየፈጸሙ ፅንስ እንዳይሆን  መከላከል የሚያስቀስፍ ተግባር ነው፡፡ የይሁዳ ልጅ አውናን የተቀጠፈው በዚህ ተግባር ነውና፡፡( ዘፍ 48፤11) ቤተ ክርስቲያን የወሊድ መከላከያን አትቀበለውም ፤ ምክንያቱም ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታዎች  እንደመሆናቸው (መዝ 127፤ 3-4) ፈቃደ እግዚአብሔርን መከላከል ነው፡፡ ይሁን እንጂ ቤተ ክርስቲያን በዓመት ውስጥ ሰባት አጽዋማት እንዲሁም ሰንበታት ጨምሮ ወርሃዊ በዓላት ስላሉ በእነዚህ ጊዜያት የግብረ ሥጋ ግንኙነት አይፈቀድም፡፡ እንዲሁም ቤተ ክርስቲያን እናቶች ልጆቻቸውን ቢያንስ ከሁለት እስከ ሦስት ዓመታት ሳያቋርጡ እንዲያጠቡ ስትመክር (1ኛ ሳሙ 1፤ 22-24) በእነዚህ ጊዜያት እናቶች ልጆቻቸውን አራርቀው ሊወልዱ ይችላሉ፡፡

ሜዲካል፡- ከሕክምና ጋር ተያይዞ በአሁኑ ወቅት ሰዎች ከሞት በኋላ የአይናቸውን ብሌን በንቅለ ተከላ እንዲሁም እንደ ኩላሊት የመሳሰሉትን የሰውነት ክፍሎቻቸውን ለሌሎች በመለገስ ላይ ይገኛሉ፡፡ ይህን ጉዳይ በተመለከተ የኦርዶክስ ቤተክርስቲያን አቋም ምንድነው?
አቡነ ሳሙኤል፡- የሰውነት አካላት ልገሳ እና የዓይን ንቅለ ተከላን በተመለከተ ይህን ዓይነት ገቢ ሰናይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አትቃወምም፡፡ ነገር ግን ኩላሊት የሚለግሰው ለጋሹ በሕይወት እያለ ስለሚሆን ለጋሹን በማይጎዳ መልኩ  በለጋሹ ሙሉ ፍቃደኝነት ላይ የተመሰረተ መሆን ይኖርበታል፡፡ በዚህ አይነት መልኩ የሚደረግ የአካል ክፍል ልገሳ ምግባረ ሰናይን ፤ አፍቅሮ ቢጽን የሚገልጽና  ሌላውን የማዳን መልካም ስራ ስለሆነ  ቅድስት ቤተክርስቲያን አትቃወምም፡፡ (ዮሐ 15፤13 ገላ 4፤15)

ሜዲካል፡- መውለድ የማይችሉ ሴቶች በሌሎች ሴቶች መሕፀን በኪራይ መልክ ልጅ ማግኝት የሚችሉበት ደረጃ ላይ ተደርሷል፡፡ ይህ እንደ ቤተክርስቲያን አስተምህሮ ምን ምላሽ ይኖረዋል?

አቡነ ሳሙኤል፡- ይህንም ከሕገ ተፈጥሮ ውጪ ስለሆነ ኦርቶዶክሳዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አትቀበለውም፡፡ ምክንያም በሌላ ሴት ማሕፀን ተከራይታ ልጅ ለማግኝት የምትፈልገዋ ሴት  የመጸነስን ፤ ዘጠኝ ወር በማሕጸን አርግዞ ፤ በእትብት አምጦ የመውለድን ፤ አጥብቶ የማሳደግን ጸጋ  የማቃለልና በሌላ ሰው ድካም ልጅ ለማግኝት መፈለግ በሃይማኖት ፤ በተፈጥሮ ሕግ ፤ በሕብረተሰብ ባሕልና ሞራልም የማይደገፍ ኢ-ተፈጥሮአዊ ስለሆነ ነው፡፡ ማሕፀኗን የምታከራየዋ ሴትም  አምላክ በተፈጥሮ ባደላት አንድ ወንድ ለአንዲት ሴት ባለው መሰረት  አግብታ የራሷን ልጅ ጸንሳ መውለድና ማሳደግ ሲገባት ፤ ማሕፀኗን እንደ ግኡዝ ማኅደር በማድረግ ለገንዘብ ስትል ለሌላ ዘር ማከራየቷ በተፈጥሮ ያገኝችውን በራስ ጸንሶ የመውለድ ፀጋ የማቃለልና ተገቢ ያልሆነ ጥቅም ፍለጋ ስለሆነ ይህን ቅድስት ቤተክርስቲያን አትደግፈውም፡፡

ሜዲካል፡- ደም መስጠትና መቀበል በቤተክርስቲያን አስምህሮ ምን ይመስላል ?

አቡነ ሳሙኤል፡- ደም የመስጠትና የመቀበል ተግባር ሕይወትን ለማትረፍና በሕይወት ለማቆየት የሚፈጸም ምግባረ ሰናይ ስለሆነ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አትቃወምም፡፡ በመሆኑም በመጀመሪያ ደም ምንድነው? የሚለውን ማየት ተገቢ ይሆናል፡፡

ደም በመጽሐፍ ቅዱስ እንደሚያስረዳው የሥጋ ሕይወት(ነፍስ) በደም ውስጥ ነው የምትኖረው ፤ ‹‹እስመ ደም ነፍሱ ውእቱ ለኵሉ ዘሥጋ ደም›› የሥጋዊ ፍጥረት ሁሉ ነፍስ(ሕይወት) ነውና ፤›› ዘሌ 17፤ 10-14) ሕይወት ላላቸው እስሳ ሁሉ የሕይወታቸው መሠረት ደም ነው፡፡ የእንስሳ ሕይወት ደመ ነፍስ የምትባል ስትሆን  ፤ የሰው ሕያዊት ነፍስም በደም እንደምታድር መጽሐፈ ኵፋሌ ያስረዳለ(ኵፋ 7፤8)፡፡ በመሆኑም ሕያዊት ነፍስ በሥጋ ውስጥ አድራ ሥጋን ሕያው የምታደርግበት ፤ ሰው ከሚመገበው እህልና ውሃ እየተጣራበሰውነት ውስጥ የሚገኝ ፈሳሽ ንጥረ መባልዕት ነው፡፡

ስለዚህ በሕክምና ተግባር ደምን መለገስም ሆነ መቀበል የሚደገፍ መልካም ተግባር ነውለለ ይኽውም ፡- አንደኛ ለመድኃኒት እንጂ ለምግብነት አይደለምና፡፡ ሁለተኛ ፡- የሰውን ሕይወት ለማትረፍ ደማችንን ብቻ ሳይሆን ሕይወታችንንም  ቢሆን የመስጠት ክርስያናዊ ግዴታ አለብንና፡፡ ሦስተኛ ፡- በደም ለጋሽም ሆነ በደም ተቀባይ ላይ የጤና ችግር በማያስከትል መንገድ የሚከናወን የበጎ አድራጎት ነው፡፡ አራተኛ፡- በአርኣያ እግዚአብሔር ለተፈጠረ ፤ የተፈጥሮ ወንድማችን ለሆነ የሰው ልጅ ሁሉ ያለንን ፍቅርና ርኅራኄ የሚገልጽ ተግባር ነውና፡፡(ማቴ 19፤19 ዮሐ 15፤13) ‹‹ ነፍሱን ከወዳጆቹ ከመስጠት የበለጠ ፍቅር ለማንም የለውም›› ከሚለው አምላካዊ ቃል እንጻር ሲታይ  የሰውን ሕይወት ለማትረፍ የለጋሹ ጤንነት በማይጎዳ  የሕክምና ጥበብ የሚደረግ ፤ የደምም ሆነ የሌሎች ክፍለ ሕዋሳት ልገሳ የሚደገፍ የምግባረ ሰናይ ተግባር ነው፡፡ ስለዚሀ ቅድስት ቤተክርስቲያን አትቃወምም፡፡


ሜዲካል፡-   ከኤች አይቪ ቫይረስ ጋር የሚኖሩ ወገኖች መድኃኒቱንና ጸበሉን አንድ ላይ እንዲጠቀሙ ቤተ ክርስቲያኗ ልዩ አስተያየት ማድረጓ ይታወቃል፡፡  ስለ ፅንስ ማቋረጥና የቤተሰብ ምጣኔ አስተምህሮዋን ወይም ዶክትሪኗን ብታሻሽል ምን ችግር አለው ?

አቡነ ሳሙኤል፡- ይህ ትክክለኛ መነጻጸሪያ አይደለም፡፡ በሌላ አነጋገር ሎጂካል አይደለም ማለት እችላለሁ፡፡ ጸረ-ኤች አይቪ መድኃኒት ከጠበል ጋር መውሰድ ከፅንስ መቋረጥና ከቤተብ ምጣኔ ጋር በፍጹም ፤ በፍጹም አይዛመድመ፡፡ የመጀመሪያ ሕይወትን ለማዳን ሲሆን ሁለተኛው ግን ተቃራኒ መፈጸም ማለት ስለሆነ የሚሻሻል ነገር የለም፡፡ ቤተክርስቲያን የፈጣሪን ሕግ ተቀብላ ታስተምራለች እንጂ ቅዱስ ቃሉን የመቀነስ ፤ የመጨመርና የማሻሻል ተግባር አትፈቅድም፡፡ ምክንያቱም ‹‹ብዙ ተባዙ›› ያለውን አምላካዊ ትእዛዝ ማፍረስ ስለሚሆንና ሁለተኛም ‹‹ነፍስ አትግደል›› ያለውን ማፍረስ ስለሚሆን ነው (ዘፍ 10፤28 ዘጸ 20፤13)   

ሜዲካል፡-  በቤተክርስቲያኗ አስተምህሮ ግብረሰዶም ኃጥያት እንደሆነ ይታወቃል ፤ በሀገራችን ላይ ድርጊቱ ተስፍቶ ይገኛል፡፡ ሁኔታው የቤተ ክርስቲያኗን ተሰሚነት እየሸረሸረው አይመስሎትም? 

ሜዲካል፡- በሳይንስ ዓለም ነፍስ እንዳለች የሚያምኑና የማያምኑ ሳይንቲስቶች አሉ፡፡ ግን እንደ ቤተ ክርስቲያን ነፍስ የሚባል ነገር አለ? ስለ መጠኗና ስለ ባሕርይዋ በሊቃውንት ወይም በመጽሐፍ የተሰጠ ማብራሪያ ካለ ቢያስረዱን ?

14 comments:

  1. hurry up please for the answers

    ReplyDelete
  2. We are waiting for the responses eagerly!

    ReplyDelete
  3. ቃለ ህይወትን ያሰማልን አብዝተን አናመሰግናለን ቀጣዩን ጽሁፍ እየጠበቅን ነው ወይ የመቼ ጋዜጣ እንደሆነ ጠቁሙን እና እናፈላልግ ወይ ደግሞ በነካ እጃችሁ ጨርሱልን

    ReplyDelete
  4. egezabher ragem edmana yagalglot zman yestlem labatachen aman!!

    ReplyDelete
  5. እግዚአብሔር አምላክ አባቶቻችንን ይጠብቅልን። እንዲህ ነው ከመፅሐፍ ቅዱስ ቃል አለመውጣት ማለት እመቤታችን ወላዲተ አምላክ በአማላጅነቱአ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሐይማኖታችንን ትጠብቅልን አሜን።

    ReplyDelete
  6. የሰውነት አካላት ልገሳ እና የዓይን ንቅለ ተከላን በተመለከተ ይህን ዓይነት ገቢ ሰናይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አትቃወምም፡፡ ነገር ግን ኩላሊት የሚለግሰው ለጋሹ በሕይወት እያለ ስለሚሆን ለጋሹን በማይጎዳ መልኩ በለጋሹ ሙሉ ፍቃደኝነት ላይ የተመሰረተ መሆን ይኖርበታል፡፡ በዚህ አይነት መልኩ የሚደረግ የአካል ክፍል ልገሳ ምግባረ ሰናይን ፤ አፍቅሮ ቢጽን የሚገልጽና ሌላውን የማዳን መልካም ስራ ስለሆነ ቅድስት ቤተክርስቲያን አትቃወምም፡፡ (ዮሐ 15፤13 ገላ 4፤15)

    ?????????????????????????????????????????????????????

    ReplyDelete
  7. Thank you for this wonderful discussion, if possible please ask Abune Samuel this further question:-
    At times a pregnancy can occur in a female's body part other than the womb (uterus) most commonly in the 'fallopian tube' (yemehatsen genda) and in rare cases the abdominal cavity outside of the uterus, these are called 'ectopic pregnancies'.
    In such cases, the mother almost always bleeds to death due to hemorrhage before the pregnancy comes to term.
    The question to his holiness is this:-
    if I, as an obstetric surgeon remove this ectopic fetus before it ruptures in the mother's vital organs and causes her death, would that be considered as sin upon us, I as her physician and the mother who agrees to the removal?

    This question is very important to me ( and to everyone else, I think) and I await for a response in accordance with the beliefs and teachings of the Ethiopian Tewahedo Church.

    Thank you,
    Tensae- Berhan Tsegaye MD



    ReplyDelete
    Replies
    1. I AM JUST A STUDENT, BUT THAT IS GREAT DOCTOR ?

      Delete
  8. gibre hawaryat 15:21 ke dem mekebel gar endet yismamal?

    ReplyDelete
  9. ቃለ ህይወትን ያሰማልን አብዝተን አናመሰግናለን

    ReplyDelete
  10. ለ ህይወትን ያሰማልን አብዝተን አናመሰግናለን ቀጣዩን ጽሁፍ እየጠበቅን ነው ወይ የመቼ ጋዜጣ እንደሆነ ጠቁሙን እና እናፈላልግ ወይ ደግሞ በነካ እጃችሁ ጨርሱት

    ReplyDelete
  11. ብፁዕ ኣብኑአን ሳሙኤል የሰጡት ትምህርት በጣም ጠቃሚ እና ኣስተማሪም ነው፣
    ጊዜ እና ሁቤታ የእግዚኣብሔር እውነትነት መለወት የማችል ቢሆንም፥ ካለው የሕብረተ ሰቡ ኣኗኗር ጋር ሲነጻጽር፥ በበዓላትና በጾም ኣራርቆ መውለድ ይቻላል ከሚለው ግን ይከብዳል።
    ለምሳሌ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ኣጽዋማት፥ በዓላት ወርሓዊ ኣበባ በሚመለከት ጉዳይ፥ ባለፈው ዓመት እንደ ኤውሮጳውያን ኣቆጣጠር ጾም ብቻ ከ365, 194 የቀረ ቀን 171 ቀናት ነው በዓላት ሌሎችም ሳንስገባ እሁድ፥ ቅዳሜ፥ ሚካኤል፥ ማርያም መድሓኔ ዓለምና በዓለወልድ ብቻ ጾም ከሚውልበት ቀን እያስወጣን ስንቆጥረው 87 ቀናት፥ ይህም ሌሎች ተጨማሪ በዓላት፥ ዓመታዊ በኦኣላት፥ ለምሳሌ፥ የሥላሴ የኣቦ፥ የተክለሃይማኖት፥ ጊዮርጊስ ቁስቋም፥ ልደታ፥ በዓታ፥ ጽንሰታ፥ ወዘተ በዓላትን ሳናስገባ ነው፥ የወር ኣበባ ከጾም ከበዓላት ከሚውሉበት ቀናት ውጭ ስንቆጥር ከ22-25 ቀናት ይሆናሉ ማለት ነው።
    ስለዚህም 171-87-22= 62 ቀናት ብቻ በዓመት ኣንድ ወንድ ከሚስቱ ጋር ሥጋዊ ግኑኝነት ይችላል ማለት ነው። በዚህ መሠረት ኣንድ ወንድ ከባለቤቱ ጋር ሥጋዊ ሩካቤ ለማድረግ፥ በሳምንት 1 ብቻ መሆኑ ነው። ይህ ለሌላ ፈተና ኣይጋብዙም ወይ፥ ይቅር ልጆች ኣንድ ሊጅ መውለድስ ይቻላል ወይ? በዓላቱ በሚገባ ይከበሩ ከተባለ፥ 87 ብቻም ኣይደሉም፥ እና ይሄ ነገር ኣራርቆ ለመውለድ ፈተናም ነው፥ የሴት ልጅ የምታረግዝበት ቀናትን በወር 8-14 1ቀናት ናቸው። ሁላችን ተሰባስበን ገዳም መግባት ካልሆነ በቀር በእኛ የበዓላትና፥ የኣጽዋማት ኣቆጣጣር ሴት ኣግብቶ መኖር ምንም ፋይዳ ሊኖረው ኣይችልም፡ ሰውን እያታለልን ከመኖር በስተቀር።

    ReplyDelete
  12. @asbet dngl, Medical Magazine(Not newspaper), Vol.1 No.10, January 2007 E.C.

    ReplyDelete