Saturday, October 3, 2015

‹‹ቅድስናን በገንዘብ?›› መጋቤ ሀዲስ እሸቱ አለማየሁ

መጋቤ ሀዲስ እሸቱ አለማየሁ  ዳላስ ውስጥ በነበረ አንድ ሀይማኖታዊ የምክክር መድረክ ላይ ዘመኑን የመሰሉ ጥያቄዎች ከአንዳንድ ወገኖች ቀርቦላቸው ነበር፤
ጥያቄ :- (በዘመናችን ዝናቸው ስለ ገነነው አንድ አጥማቂ ነበር) በአንዳንድ ሊቃነ ጳጳሳት ዘንድ የተወገዙ ሆነው ሳለ በአንፃሩ ደግሞ ሌሎች ሊቃነ ጳጳሳት ተቀብለዋቸዋል፡፡ ያም ሆነ ይህ መጋቢ ሀዲስ በዚሁ ዙሪያ ያሎት አቋም ምንድነው? ይህ ነገርስ ከትውፊት ውጪ ከሆነ ለምንስ ብዙ ሰው ግራ ገብቶት እያለ እናንተ መምህራን ዝምታን መረጣችሁ? የሚል ነበር።
መጋቤ ሀዲስእሸቱ አለማየሁ፦ ማንም ሰው ጳጳስ ስላወገዘ ወይንም ስለተቀበለ አይደለም እውነታን ማወቅ የሚችለው። ሁሉም እኮ ከቤተ ክርስቲያን በታች ነው። ፓትርያርኩም ቢሆኑ። ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርኩን አፈራች እንጂ የትኛውም ፓትርያርክ ቤተ ክርስቲያንን አልመሰረተም። ስለዚህ ለጥያቄዎች ሁሉ ጳጳስ እንዲህ አለ፣ ሰባኪው ይሄን አለ ሳይሆን ወንጌል ምን አለ? በአፀደ ነፍስ ያሉት፣ በገድል በትሩፋት ያለፉት የቅዱሳኑ ታሪክ ምን አለ? ማለት ነው ያለብን እንጂ እገሌ እንዲህ አለ ማለት ከንቱነት ነው። ሰው ሊስት ይችላል፤ በስጋ ያለ ሰው ጳጳስም ቢሆን ሊሳሳት ይችላል፣ መሳሳት አይደለም ሀይማኖቱን ሊክድ ይችላል ያኔ ግን ጳጳስ የምንከተል ሰዎች እነርሱም ሲክዱ እኛም አብረን እንክዳለን ማለት ነው።

በዘመኑ የምናየውን የማጥመቅ አገልግሎት ስህተት ነው አትከተሉ ብዬ በአውደ ምህረት ከመስበኬ በፊት መጀመሪያ የእኔን ጉድፍ ስመለከት አዝንና ስለሌላው ጉድፍ እንዴት ብዬ አውደ ምህረት ላይ ወጥቼ ልስበክ? ብዬ እተወዋለው። (ትህትናዊ መልስ) አዎ በዘመናችን ያሉ የመቁጠሪያ ንግድን የያዙ፣ የፀጉር ቅባትን ቅባ ቅዱስ ነው ብለው የሚሸጡ፣ የአጋንንት ምስክርነትን በሲዲ በመሸጥ የሚኖሩ፣ ተአምራትን በመስራት ኑሮአቸውን የሚገፉ ሰዎች አሉ። ምዕመኑም በእነዚህ ሰዎች ጠንቅ መፅሀፍ ቅዱስን ትራሱ አድርጎ ከሰይጣን ምስክርነት እማራለው ብሎ ሲዲ ገዝቶ ቁጭ ብሎ ሲያዳምጥ ነው የሚውል። "ተአምረ ለእግዚትነ ማርያም" ሲባል ጆሮውን እያከከ በሀሳብ ቤቱ ውስጥ ስላለው ሲዲ ያስባል።
የእኛ ምዕመን ቤተክርስቲያን ለካህናት ክብር ብላ የዘረጋችውን ጥላ ዘቅዝቃ ስትለምን ዝም ያለ አንድ ተአምር መስራት ቻልኩ ያለ ግለሰብ ወይንም ባህታዊ ሲመጣ አስራት በኩራት ማውጣት ይጀምራል። ቤተ ክርስቲያን ጹሙ፣ ፀልዩ፣ ቁረቡ ብላ ስታስተምር ጆሮው የተከደነበት ሁሉ ተአምር ማድረግ የሚጀምር ሰው ሲመጣ ‹‹እኔ ወንጌልን ያስተማረኝ እርሱ ነው›› ማለት እንጀምራለን፣ እንከተላለን፣ ከዛም..... የጌታን ተአምር ሰምቶ የተከተለው አይሁድ ይሰቀል ብሎ ለመካድ ቅርብ ነበር፤  ከቅፅረ ቤተ ክርስቲያን ውጪ በየሜዳው የፀበል አገልግሎት በቤተክርስቲያናችን ይፈቀዳል እንዴ? ክርስቶስ ደዌ ዘስጋ፣ ደዌ ዘነፍስም ሲያደርግ አጋንንቶች እንዲመሰክሩ፣ የሰዎቹም ሀጢያት በአጋንንቱ አማካኝት በመድረክ ላይ እንዲናዘዙ መቼ ፈቀደ? መቼስ አደረገ? እንደውም ከፈወሰ በኋላ ለማንም እንዳትናገሩ እያለ ሲልካቸው እንደነበረ ነው እኔ የማውቀው። (በግል ካህን አግኙ ከማለት በስተቀር።) በዘመናችን ያለክህነት ማጥመቅ እየተለመደ መጥቷል፤ እንደውም አንዳንድ ዝነኛ አጥማቂዎች የክህነት ስም በአቋራጭ (በገንዘብ) ያገኛሉ ወይ? ለሚለው ጥያቄ አዎን በሚገባ ያገኛሉ።
 ይህንን እኛ ጠንቅቀን እናውቃለን። ዛሬ የቤተ ክርስቲያን አበሳዋ በዝቷል። በዚህ ተሀድሶው፣ በዚያ ሙሰኛው፣ በዚያ ጠንቋዩ... እንደ በረዶ የነጣችው ይቺ ቤተ ክርስቲያን የቡና ፍንጣሪ ሲነካት ጥቁሯ ነጥብ ጎልቶ ይታይባታል። ለዚያ ነው ብዙዎች ተሰናክለው የሚጠፉት። እኔ ለነገሩ ከእነዚህ ነጋዴ አጥማቂ ነን ባዮች ይልቅ ለቤተ ክርስቲያኗ ስጋት የሆኑ ሌሎች አካላት አሉ። ለምሳሌ ተሀድሶ!! እነዚህ ሲዲ ነጋዴዎች ዛሬ ታይተው ነገ ይጠፋሉ። ብዙ ባህታውያን ነን ባዮች ከዚህ በፊት ብዙዎችን ተከታይ አድርገው አልፈዋል፤ ብዙ አጥማቂ ነን ባዮችም ከዚህ በፊት ተነስተው አልፈዋል። እነዚህም ያልፋሉ፣ ከዚህ ይበልጥ የሚያሰጋኝ በቤተክርስቲያናችን ውስጥ መርዝ የሚተክሉ፣ አስተምሮዋን የሚበርዙ፣ በውስጥ ለውስጥ ስር እየሰደዱ ያሉትን ተሀድሶዎች ናቸው። እነርሱን አጥብቀን መቃወም ነው ያለብን። 



ዳላስ ቴክሳስ September 7, 2015

1 comment:

  1. lik new memihir yagelgilot zemeniwon yarzimilin!!!! kale hiwotin yasemalin!!!

    ReplyDelete