Friday, August 5, 2011

ጠንክሮ ያስወሩት ወሬ እምነት ለመሆን ይበቃል


Birhanu Admas


ጌታችን ከመነሣቱ በፊትም ሆነ ከተነሣ በኃላ አይሁድ አንድ ወሬ አሰወርተዉ ነበር፡፡ በመጀመሪያ ይሰረቃል እንጂ አይነሣም እያሉ አስወሩ፡፡ ወሬዉን ማስወራት የጀመሩት ጌታ ከተሰቀለ በኃላ ቢሆንም በዚያች አንድ ቀን ተኩል ዉስጥ እንኩአን ያላመኑትን ደቀመዛሙርቱን ሳይቀር አጠራጥሮ ነበር፡፡ ሉቃስ እና ቀልዮጳ ነገረ ትንሣኤዉን ከሰሙ በኃላም ወደ ኤማሁስ የተጉአዙት በዚሁ ወሬ ምክንያት ከደረሰባቸዉ ጥርጣሬ ...መፈወስ አልችል ብለዉ ነበር፡፡ሦስት ዓመት የተማሩትንም የክርስቶስ ትምህርት የአንድ ቀን የአይሁድ ወሬ ናደዉ፤ መሰረታቸዉንም አስለቀቀዉ፡፡ እርሱ በቸርነቱ ወደ ኤማሁስ ሲሄዱ መንገደኛ መስሎ ባይመልሳቸዉ ከሐዋረያት ጉባኤ ብቻ ሳይሆን በጌታም ከማመን ወጥተዉ ቀርተዉ ነበር፤ ቸር መሐሪና ይቅር ባይ አመላክ መለሳቸዉ እንጂ፡፡መግደላዊት ማርያምም ከመቃብር ባጣችዉ ጊዜ ‹ጌታዬን ማን ወሰደዉ › ያለችዉ ያዉ ይወሰዳል ይሰረቃል የሚለዉ ወሬ አጠራጥሩአት ነዉ፡፡ እነዚህን ብርቱ ሰዎች ይህን ያህል የጠራጠረ ሌሎቹንማ እንዴት አድርጎአቸዉ ይሆን እንድንል ያስገድደናል፡፡ አይሁድ መቃብሩንም ያስጠበቁት እዉነቱን ለመናገር ክርስቶስ እነሣለሁ ሲል ያስተማረዉን ትምህርት በከፊልም ቢሆን አምነዉ ስለነበረ ነዉ፡፡ የፈሩትም አልቀረ በድንግልና እንደተወለደዉ በታተመ መቃብር ተነሣ፡፡ መቃብሩን ይዘዉ አልተነሳም እንዳይሉ መላእክቱ ድንጋዩን አንከባለዉ ኑና እዩ በዚህ የለም፤ እንደተናገረዉ ተነስቶአል እያሉ አጋለጡባቸዉ፡፡ ስለዚህም መነሣቱን እያወቁና እያመኑ እልህ መርፌ ያስዉጣል የተባለዉ ደርሶባቸዉ ተሰረቀ እንጂ አልተነሣም ብለዉ አስወሩ፡፡እነርሱ እንዳሉት ቢሰረቅ ኖሮ ተነስቶ ሊሔድና ሊያስተምርም አይቻለዉም ነበረ፡፡ አረባ ቀናትን አስተምሮ ሲያርግም ከታየ በኃላ ተሰረቀ የሚለዉ ወሬ ቦታ እንደያዘ ቀረ፡፡ በእዉነት የአይሁድ ሊቃነ ካህናት ለስቅላት ለሞት ከማብቃታቸዉ ይልቅ ይህኛዉ ኃጢአታቸዉ ይበልጥባቸዋል፡፡ሕዝቡ መጀመሪያም ባለማወየቅ ተከተላቸዉ አሁንም አደመጣቸዉ፡፡ እነርሱ ግን የሆነዉን በርግጥ አዉቀዉ ሆነ ብለዉ በማስወራታቸዉ ይህችናቱ በደላቸዉ ትከፋለች፡፡ እነርሱ ግነ ወንጌላዊ ማቴዎስ እንደገለጸዉ ወንጌሉን እስከጻፈበት ጊዜ ድረስ ስላስወሩት ለአይሁድ እምነታቸዉ ሆኖ ቀረ፡፡ እኛ ክርስቲያኖች ከዚህ ታሪክ የምንማረዉ ቢያንስ አንድ ታላቅ ቁምነገር አለ፡፡ አይሁድ በዚህ ወሬ አምነዉ የቀሩት ሰዎቹ የተለዩ ክፉዎች ስለሆኑ አይደለም፡፡ ያመኑት ወሬዉን የሚያስወሩት የሚያከብሩአቸዉና የሚከተሉአቸዉ የእምነታቸዉ መሪዎች የቃሉ አስተማሪዎች ስለሆኑባቸዉ ነዉ፡፡ በእንዲህ ያሉ ሰዎች ወሬ እንደመፈተን ያለ ከባድ ፈተና የለም፡፡ ሊቃነተ ኦሪቱ ወሬዉን እንደ ሃይማኖት አስተካክለዉ በብዙ አዉሪዎች አዳረሱት፡፡ሰዎቹ ምን ያድርጉ ያፍሩአቸዋል ያከብሩአቸዋልና ይሄዉ እሰከዛሬ በክርስቶስ ሳያምኑ ይኖራሉ፡፡ በአጭሩ ወሬዉን እምነት ያደረገዉ የአዉሪታዉ ማንነትና አላማ ነዉ ማለት ነዉ፡፡

ሊቃነ ካህናቱ ጥንቱንም ቀንተዉበት ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የተሾመ፣ የሚደነቅ፣ የሚታወቅና የሚታመን ሰዉ የፈለገዉን በጥበብ ካስወራ እዉነት ነዉ እየተባለ ተቀባይነት ያገኝለታልና በቅናተ መሆኑ ሳይታወቅ ወሬያቸዉ ሰመረላቸዉ፤ ነገራቸዉም እምነት መሰለ፡፡ ዛሬ በእኛ ዘመንም ይሄዉ ዘዴ ይሠራበታል፡፡ በአሁኑ ጊዜም ሾልከዉ ያመለጡ፣ እኔን የሚወድ ነግሮኝ እየተባሉ እንደሚወሩት ያለ ማለት ነዉ፡፡ ሹመትን፣ታዋቂነትን፣ በተለያየ ምክንያት የተፈጠረ ተቀባይነትን ተጠቅሞ እንደ አይሁድ የሚያስት መኖሩ የሚጠረጠር አይደለም፡፡ በእዉነት ራሳችንን የምንመለከት ከሆነ በምናከብራቸዉና በምንወዳቸዉ ሰዎች ስለተነገሩን ብቻ እዉነት መስለዉን አጽንተን የያዝናቸዉ ስህተቶች አይኖሩም ትላላችሁ፡፡ በዚህና በዚያ የተከፋፈልነዉ በምን ይመስላችኃል ወደ አንድነትና ወደ ፍቅር ከመመለስ ይልቅ በልዩነት የጸናነዉሰ ስለዚህ ታዋቂና ታላቅ የምንላቸዉን ሰዎች የነገሩንን ብንመረመርና ኅሊናን ለእግዚአብሔር ብናስገዛ ምን ነዉር አለዉ እንደ አይሁድ የተወራልንን አጥንተን እንደ ጥሩ ደቀመዝሙር አስተካክለን የምናስተላልፍ ብቻ ከሆነ አይሁድን ከመሆን አልዳንም፤ እነርሱንም ለመዉቀስ የሞራል ብቃት አይኖረንም፡፡

ዛሬም ሰዎች ሆነ ብለዉና አጠንክረዉ የሚያሰወሮአቸዉ ብዙ ወሬዎች አሉ፡፡ የሚገርመዉ ደግሞ እንደዚህ ያሉ ወሬዎች የሚያሰራጩአቸዉ ደቀመዛሙረት አሉአቸዉ፡፡ሳንመረመር፣ በትዉዉቃችንና በየዋሕነት ብቻ አመነን የምንቀበል ከሆነ ዛሬም ስንስት እንኖራለን፡፡ ያላቸዉን ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ሃይማኖታዊና ሌሎች ተቀባይነት ማግኛቸዉን ተጠቀመዉ ከሚያስቱን ካልተጠበቅን ከዘመነችን ትሩፋነ ሊቃናተ ኦሪት ተጽእኖ አላመለጥንም ማለት ነዉ፡፡ዮሴፍን እንድናደንቀዉ ከሚያደርጉን ነገሮች ዋናዉና ለመመረጥም ያበቃዉ ራሱን ከወንድሞቹ ወሬ መጠበቁ ነዉ፡፡ ይህን ባያደርግ ኖሮ እግዚአብሔርም ለጸጋ አያጨዉም ነበረ፡፡ ከድኅረ ትንሣኤዉ ትምህርቶችም አንዱ በሚወዱት ፣ በሚያምኑት፤ በሚያከብሩት እና በሚያደንቁት ተፈጥሮ ከሚሰጠን የወሬ ደቀመዝሙርነት መጠበቅ እንደ አይሁድም እርሱን አምኖ ከመጥፋት ራስን ማዳን ነዉ፡፡ከአይሁድም ግብር የተረጋገጠዉ ነገርም አጠንክረዉ ካስወሩት በብልሃት የተፈጠረ ወሬ እምነት ሊሆን መቻሉ ነዉ፡፡በእኛ ቤተ ክርስቲያንም ዛሬ ብዙዎቻችን እያሳተ ያለዉ ይሄዉ ግብረ አይሁደ ይመስለኛል፡፡ መልካም በዓል ይሁንላችሁ የምለዉ በምናምነዉ፣ በምናደንቀዉና በምንወደዉ ከሚመጣ ከዚህ የወሬ ፈተና ይጠብቀን በማለት ነዉ፡፡

No comments:

Post a Comment