Sunday, May 13, 2012

ከዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ ዝግጅት ጀርባ


(ደጀ ሰላም፤ ግንቦት 5/2004 ዓ.ም፤ May 13/ 2012/ READ this article IN PDF)፦ በ56ኛ ዓመት ቁጥር 126፣ ሚያዝያ ግንቦት 2004 ዓ.ም ታትሞ በወጣው ዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ ላይ “የአባቶች ገበና በሕገ ቤተ ክርስቲያን ሲጋለጥ” በሚል ርእስ ስለ ሰፈረው ርእሰ አንቀጽ፣ “ቤተ ክርስቲያንንና መንጋዎቿን ከወቅታዊ አደጋ ለመታደግ ከግንቦቱ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚጠበቅ የህልውና ውሳኔ” በሚል ርእስ ስለተዘጋጀው ሐተታ አስተያየታቸውን የተጠየቁት ዋና አዘጋጁ መጋቤ ምስጢር ወልደ ሩፋኤል ፈታሒ “እኔ ማንንም አልፈራም፤ ጽሑፉ አያስጠይቀኝም እንጂ ብጠየቅበት አልፈራም፤ በይዘቱ አዲስ አይደለም፤ የተለያዩ ግለሰቦች በየራሳቸው አቀራረብ ሲጽፉት የቆዩት ነው፤ እኔ ለመጻፍ የሞከርኹት የቤተ ክርስቲያን ህልውና እየተነካ ነው ብዬ በማምንበት ስለ ጳጳሳት ንብረት ጉዳይ ነበር፤ አባ ጳውሎስ ግን በሲኖዶስ ስብሰባ ሕገ ቤተ ክርስቲያን ይሻሻል አሉ፤ እውነቱን ለመናገር ግን ጽሑፉ ከውጭ የመጣ እንጂ በዝግጅት ክፍሉ የተጻፈ አይደለም፤ በስሜ እየተነገደብኝ ነው፤” ብለዋል፡፡



ዋና አዘጋጁ ጽሑፉ ከውጭ ተዘጋጅቶ እንደመጣ የተናገሩትን መነሻ በማድረግ አዘጋጁን አካል ለማወቅ በተደረገ ጥረት÷ “አባ ጳውሎስን ደግፋችኹ ከጻፋችኹ ማንም አይነካችኹ፤ ከተነካችኹም እኛ አለንላችኹ፤ ሁሉም ወንጀለኛ ነው” በሚል የጥቅም ማበረታቻ የተቀበሉት የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ ዋና ሓላፊ እስክንድር ገብረ ክርስቶስና እንደ ቀበሮዋ ዘለው ዘለው የሻቱትን ማዕርገ ጵጵስና ቢያጡት የተሾሙትን አባቶች ማሸማቀቅ የመረጡት አባ ሰረቀ፤ ለዚህም የገንዘብ ድጋፍ የሰጡት አባ ፋኑኤልና ዦቢራው ኀይለ ጊዮርጊስ ጥላሁን መኾናቸው እየተነገረ ነውየአባ ጳውሎስ አይዟችኹ ባይነት (ቡራኬ) ሳይዘነጋ ማለት ነው፡፡ ይኹንና የዝግጅት ክፍሉም በጽሑፉ ላይ ማሻሻያ በማድረግና እንዲታተም በመፍቀድ፣ ምናልባትም የጥቅሙም ተካፋይ በመኾን መጠየቁ እንደማይቀር ግልጽ ነው፡፡

በጋዜጣው ላይ አስተያየት እንዲሰጡ የተጠየቁ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምንጮች“ጋዜጣው የደገፈውንና የነቀፈውን አያውቅም፤ ለምሳሌ አባ ፋኑኤል ስለ ራሳቸው እያወሩና ቀሲስ ዶ/ር መስፍንን ከስሰው የከበሩ ቢመስላቸውም በውስጥ ገጽ በተጻፈው ጽሑፍ ደግሞ ‹በእግዚአብሔር ገንዘብ የግል ቪላ ገንብተው ያከራያሉ፤ እንደ ዓለማዊ ሰው ለአባት የማይገቡ ዘመናዊና ከፍተኛ ዋጋ ያለው መኪና ገዝተው ያሽከረክራሉ፤ ሌላም፣ ሌላም ተብለው የተወነጀሉት ዋነኛው ራሳቸው ናቸው፤” በማለት ተችተዋል፡፡

ቸር ወሬ ያሰማን፣ አሜን

1 comment:

  1. ለመሆኑ ማነኛው አባት ነው ትክክለኛ እኛ እኮ ግራ ገባን በሀሜትም ቢባል አባቶቻችንንም ካለማክበር ቢባል በሀጢአቱም ቢባል በሁሉም መስክ ለሞት እየተጋለትን ነው፡፡ እባካችሁ እናንተ አባቶቻችን ፍቅርና ሰላምን አንድነትን አስተምሩን፡፡ ጥልና ክርክሩን መለያየቱንና ሀጢአቱን እኛ ምእመናን እናውቀዋለንና አዲስ አይሆንብንም፡፡ እባካችሁ ሰው ሆናችሁ ሰዎች አድርጉን፡፡ ቅዱሳን ሆናችሁ ቅዱሳን አድርጉን፡፡ ታርቃችሁ ታራቂዎች አድርጉን፡፡ከዚያም ለሀገራችንና ለቤተክርስቲያናችን ኩራት እንሆናለን፡፡ ካለዚያ ግን በሰማይም ሆነ በምድር ማፈሪያዎች ሆናችሁ አታሳፍሩን፡፡ ሞታችሁ አትግደሉን፡፡ ጠፍታችሁ አታጥፉን፡፡ ራሳችሁን አክብራችሁ አስከብሩን፡፡

    ReplyDelete