Friday, July 20, 2012

“ማኔ ቴቄል ፋሬስ” ብሎ የሚጽፈው ጣት እንዳይቀርብባችሁ ለራሳችሁ ተጠንቀቁ


(አንድ አድርገን ሰኔ 13 ፤ 2004 ዓ. ም)፡- በአሁን ወቅት ጆሯችን የሚሰማው ፤ ከጋዜጦች የምናነበው ፤ ከድህረ ገጾች የምንመለከተው ነገር የጠቅላይ ሚኒስትሩን መታመም የሚያመላክቱ ምንጫቸው ከተለያዩ ቦታዎች የሆኑ መረጃዎችን ነው ፤ በትላንትናው እለት የመንግስት ኮሙኒኬሽን ሚኒስትር አቶ በረከት ስምኦን ትንሽ የጤና እክል እንዳጋጠማቸው ከሀኪም እረፍት በኋላ በጥቂት ቀናት ውስጥ ወደ ስራ እንደሚመለሱ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል ፤ ከአንድ ቀን በፊት አቶ ስብሀት ነጋ በፌዝ በቪኦኤ እንደተናገሩት “በሚቀጥሉት 10 ቀናት ውስጥ ጠቅላይ ሚንስትሩ ወደ ስራ ገበታቸው ይመለሳሉ” ብለዋል ፤ አይይ…ሰው ከተያዘ በኋላ ፌዝ ምን ይሰራል ? ነገረር ግን ደህና ሆነው ከ10 ወር በኋላም ቢመለሱ መልካም ይመስለናል ፤ ዋናው ጤና ነው ፤ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ስራ መሆኑን እስከ አሁን አናውቅም ነበር ፤ ይገርማል ፤ ለካ የመንግስት ተቀጣሪ ናቸውን ? ሰው በህይወት ዘመኑ በተለያዩ አጋጣሚዎች በሽታዎች ይጎበኙታል ፤ በቀላሉ ደረስ መለስ የሚሉ ህመሞች እንዳሉ ሆነው ከሰው እድሜ ጋር አብረው የሚዘልቁም አይጠፉም ፤ ባሳለፍናቸው 21 ዓመታት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ታመሙ የሚባል ወሬ ሰምተን አለማወቃችን የአሁኑን ሁኔታ የተለየ አይን እንድንመለከተው አድርጎናል ፤ እንደ ፕሬዚዳንት ግርማ ባይታመሙም ለቼካፕ በየጊዜው ሳውዲአረቢያ ቢመላለሱ ኖሮ ህዝቡ ይለምደውና ተሽሏቸው ይመጣሉ ብሎ ለማሰብ መንገድ ይከፍትለት ነበር ፤ ነገርየው ቀልብ እንዲስብ ያደረገው ነገር የህመሙ ሚስጥራዊነት መሆኑን የተገነዘቡት አይመስሉም ፤ በዚህ ላይ የሀገሪቱ በጀት ማጽደቂያ ወቅት እና የህብረቱ መሰብሰቢያ ጊዜ በመሆኑ የነገሩን ምልከታ በሰዎች ዘንድ ቀየረው ፤ አሄሄ “ ሆድ ቁርጠትና ራስ ምታት ቢጤ ቢሆን በሽታቸው መቼ ከማያኑት ቴሌቪዥን ይጠፋሉ” ፤ መሪዎች የህዝቡን ሆድ ይቆርጣሉ የማህበረሰቡን ራስ ያሳምማሉ እንጂ እነርሱ ግን አያማቸውም ይባላል ፤ የጠላት ጆሮ አይስማውና “ለአቶ ግርማ ወ/ጊዮርጊስ የተቆፈረው ጉድጓድ ….” የሚልም አስተያየት ፌስ ቡክ ላይ አንብቤአለሁ ፡፡ ሌላኛው ደግሞ “ዳይት ጀምረው ነው እንዲህ የከሱት….” ብሏል ፤ የእስራኤል አምላክ ፈጽሞ ይማራቸው ፤ እጃቸውንም ከዋልድባ ገዳም ላይ እንዲያነሱ ያድርጋቸው፡፡


ሰው ይወለዳል ፤ ይኖራል በመጨረሻም አፈር ስለሆነ ወደ አፈር ይመለሳል ፤ ይህ የኛ እውቀት ሊለውጠው ወይም ሊያሻሽለው የማይችል አምላካዊ የፍጥረት መንገድ ነው ፤ ሰው ሆነን ስንኖርም ይህን አውቀን መሆን መቻል አለበት ፤ ክርስትያን ስንሆን ደግሞ ከሞት በኋላ ያለውን መንግስተ ሰማያትን ቀን ተቀን እያሰብን በጾም ፤ በጸሎት  ፤ በመንፈሳዊ  መልካም ስራ እየታተርን ልንኖር ግድ ይለናል፡፡  መጽሀፈ ምሳሌ 23፤17 ላይ “ቀኑን ሙሉ እግዚአብሔርን በመፍራት ኑር” ተብሎ ተጽፏል፡፡

ከቀናት በፊት ሃይገር ባስ ውስጥ ከመገናኛ ወደ ኮተቤ ወደ ቤቴ ስጓዝ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ህመም ሰዎች በጣሙን አሳስቧቸው ከዋልድባ ገዳም ጋር አያይዘው ሲያወሩ ሰማሁ ፤ ደግሞ ምኑን ከምኑ አያያዙት ብዬ ጠጋ አልኩኝ ፤ አንዱ ተሳፋሪ “ዋልድባ ገዳም ላይ እጃቸውን አንስተው ምን ሊሆኑ ፈለጉ ታዲያ ?  እዚያ ስንት ጤዛ ልሰው ድንጋይ ተንተርሰው የሚኖሩ የመነኮሳት እንባ ከዚህም በላይ መቅሰፍት ያመጣል ፤ እንባ መጥፎ ነው ፤ እንባ ጉልበት አለው ፤ እንባ ቀጥና መውረዷን አትይ እንዴት እንደምትመለስ ማንም አያውቅም…….”በማለት ውስጡ ያለውን በሚያስቆጣ የፊት ገጽ ተናገረ  ፤ አንዲት እህት ደግሞ “ይገርማል እግዚአብሔር ሳይውል ሳያድር .. የአባቶች ጸሎት መቼ ጠብ ይላል ..  ቤተክርስቲያን ላይ እጅ ማንሳት ጥሩ አይደለም ፤ ምን ላድርግ ብለው ነው ባልጠፋ መሬት እዚያ ገዳም ሄደው ስኳር የሚያለሙት ፤ ሀገሩ ሰው ከሚኖርበት የማይኖርበት እኮ ይበዛል ፤ ታዲያ ዋድባን ለምን ?   እኔ በበኩሌ እሳቸውን እግዚአብሔር ይማራቸው እላለሁ ” በማለት ውስጧ የሚብላላውን ነገር ከተጨማሪ ነገሮች ጋር ስትተነፍስ ባላት መረጃ በጣም አደነኳት ፤ እኔ ይህን ጉዳይ በአግባቡ ማህበረሰቡ የሚያውቅ አይመስለኝም ነበር ፤ ለካ ሁሉም ሲያብላላ ነው የሚከርመው ፤ እንደዚች እህት የሚናገርበት ቦታ አጥቶ ውስጡን በንዴት የሚያቃጥለው እግዚአብሔር ይቁጠረው ፤ ሌላው በጉዳዩ ላይ አስተያየት ሰጪ ተሳፋሪ የጠቅላይ ሚኒስሩን ህመም ከምንም ጋር መያያዝ እንደሌለበት ሰው ስለሆኑ ብቻ ሰው ሊደርስበት የሚችለው ህመም እንዳጋጠማቸው ከምሳሌዎች ጋር አስረዳ ፤ ቀድመው የነበሩት ሁለቱ አስተያየት ሰጪዎች ግን ሊሰሙት አልወደዱም ፤ በጉዞ ላይ ሰዉ ሁለት ቦታ ተከፍሎ ላለመስማማት ነገሩን መወያያ አርእስት አድርጎታል ፤ አንዳንዱ መታመማቸውን ራሱ እዛው የሰማ አለ ፤ እንዲያው ሲያወጡ ሲያወርዱ እርስ በእርስ ለመተማመን ሲሞክሩ እኔ መውረጃዬ ደርሶ ወረድኩኝ፡፡ ከዚያ ወደ ቤቴ ዎክ እያደረኩ ማነው ትክክል ? ስል ከራሴ ጋር ሙግት ገጠምኩኝ፡፡



በመሰረቱ ዋልድባ ገዳም ላይ መንግስት እንደ መንግስት ያደረሰው በደል ቀላል የሚባል አይደለም ፤ መነኮሳት ታስረዋል ፤ ተደብድበዋል ፤ ብዙ ብር ተዘርፈዋል ፤ አካባቢው ላይ ያለ የስኳር ልማት ያለ መነኮሳት ፍቃድ ለመስራት ገዳሙ ታርሷል ፤ በርካታ ወጣቶች በጉዳዩ ላይ ባላቸው አቋም ከመኖሪያ ቤታቸው በመውሰድ ማስጠንቂያ የተሰጣቸውና የታሰሩም እንዳሉ ይታወቃል ፤ መነኮሳት በአግባቡ ከዚህ ቀደም እንደሚያደርጉት ጸሎታቸውን በነጻነት ማድረግ ተስኗቸዋል ፤ በአታቸውን ቆልፈው ቀን ቀን ከሚከታተሏው ሰዎች ከአይናቸው ዘወር በማለት ጊዜውን አሳልፈዋል ፤ ምዕመኑ ከሆነ ቦታ በኋላ ወደ  እንዳያልፍ ተከልክሏል ፤ ለተቃጠሉ ዶዘሮች ሃላፊነት ውሰዱ ተብለዋል ፤ ወጣቶች ቤተክርስቲያን ለመሳለም ወደ ቦታው ሲዘልቁ ያለአግባብ ፍተሻ ይደረግባቸዋል ፤ በጠቅላላ ባሳለፍናቸው አራት ወራት ቦታው ላይ ለእናንተ ለአንባቢያን በየጊዜው የጻፍናቸው ነገሮች ሁሉ ኖነዋል፡፡ ይህ ሁሉ ግፍ እና በደል ከበታች ያሉት የቀበሌና የወረዳ ሰዎች ቢያስፈጽሙትም በደረጃ እስከ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ድረስ ያሉ ሰዎች እጅ ያለበት መሆኑ እሙን ነው ፤ በጊዜው መነኮሳቱም “ልጆቼ እናንተም በጸሎት በርቱ ፤ እኛም በጸሎት እንበረታለን ፤ የእግዚአብሔርን እጅ እንጠብቃለን” በማለት ከጎንደር በሄዱ ምዕመናን መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትሩ መታመም ሰውን በሚመስለው ነገሩን እንዲደመድም እያደረገው ይገኛል፡፡  መጽሐፈ ነገሥት ካልዕ 2 23፤24 ላይ ነብዩ ኤልሳ “ከዚያም ወደ ቤቴል ወጣ በመንገድም ሲወጣ ብላቴኖች ከከተማይቱ ወጥተው። አንተ መላጣ፥ ውጣ አንተ መላጣ፥ ውጣ ብለው አፌዙበት። ዘወርም ብሎ አያቸው፥ በእግዚአብሔርም ስም ረገማቸው ከዱርም ሁለት ድቦች ወጥተው ከብላቴኖች አርባ ሁለቱን ሰባበሩአቸው።” ይላል ፤ ለቅዱሳን አባቶቻችን ጸሎታቸውም ይሁን መርገምታቸውን እግዚአብሔር እንዲህ እንደሚሰማቸው በጊዜውም መልስ እንደሚሰጣቸው መጽሀፉ ይነግረናል ፤  በሐዋርያት ስራ 1፤14 ላይ “በአንድ ልብ ሆነው ለጸሎት ይተጉ ነበር” ይላል ፤ አሁንም በዋልድባ በሺህ የሚቆጠሩ አባቶች “በመከራ ታገሡ፤ በጸሎት ጽኑ” ወደ ሮሜ ሰዎች 12፤12 የሚለውን  የወንጌል ቃል መሰረት በማድረግ፤ ስለ ገዳሙ ህልው ስላጋጠማቸው ፈተና  በአንድ ልብ ሆነው  ቀን ከሌት እየተጉ ይገኛሉ ፤ ይህ ህመም የእግዚአብሔር የምልክቱ መጀመሪያ ይሆንን ? እኛ ምን አውቀን ባለቤቱ ይወቀው እንጂ… በመሰረቱ ሁሉም እንደየስራው እንደሚመዘን እናውቃለን ፤ ነገስታት በእግዚአብሔር ላይ ሲነሱ እጣ ፋንታቸው ሳይታለም የተፈታ ነው….



በጣም የሚገርመው መለስ ዜናዊ ሟች መሆኑን የዘነጉ በርካታ ሰዎች አሉ ፤ አይናቸው በአንድ ሰው ታውሯል ፤ ጆሯቸው በአንድ ሰው ደንቁሯል ፤ አይምሯቸው የአንድን ሰው አይዲዎሎጂ ተጠናውቶታል እግራቸው በአንድ ሰው መንገድ ረዥም ርቀት ተጉዟል ፤ በጠቅላላ የስሜት ህዋሳቶቻቸው ለሚያመልኩት ሰው ተገዥ ሆነዋል ፤ ታዲያ ይህ ሰው ማለት ለእነርሱ የእግዜር በታች ከሰዎች በላይ ሆኖ ለዓመታት ኖሯል ፤ ታዲያ እንዴት አይመለክ!!! ሁሌም ይችን ሀገር እርሱ እስከመጨረሻው እንዲያስተዳድራት የሚፈልጉ ሰዎች አሉ ፤ ይህ ደግሞ ከተፈጥሮ ህግ ጋር ይጣረሳል ፤ ይህ ሰውን ወደማምለክ የተሸጋገረ የተሳሳተ አመለካከት ነው ፤ ይህ የፈጣሪን ቃል የሚጋፋ ሆኖ ያገኙታል ፤ የሰው ልጅ መጨረሻው ሞት መሆኑን ፈጽሞ ልንዘነጋው የሚገባን ነገር መሆን መቻል የለበትም ፤ የሰው ልጅ ከህጻን እስከ አዋቂ የሞት ተራ ጠባቂ ነው ፤ በምድር ላይ የምንሄድባቸው መንገዶች መጨረሻቸውና መደምደሚያቸው ሞት ነው ፤ ሞት ጠቅላይ ሚንስትሩንም ሆነ እሳቸውን የሚሉትን ሰዎች ሊያስፈራ አይገባም ፤ ልንፈራ የሚገባን ንስሀ ካልገባን ፤ ከክፋታችን ካልተመለስን ብቻ ነው ፤ መዝሙረ ዳዊት  90፤10 ላይ ይህን ያገኛሉ “ዘመናችን ሁሉ አልፎአልና፥ እኛም በመዓትህ አልቀናልና ዘመኖቻችንም እንደ ሸረሪት ድር ይሆናሉ። የዘመኖቻችንም ዕድሜ ሰባ ዓመት፥ ቢበረታም ሰማንያ ዓመት ነው ቢበዛ ግን ድካምና መከራ ነው ከእኛ ቶሎ ያልፋልና፥ እኛም እንገሠጻለንና።” በማለት በግልጽ ያስቀምጠዋል፡፡ ክፉ ስራችንን እንፍራ ሞታችንን ግን የማይቀር ጽዋ ስለሆነ ልንፈራ አይገባም ፤ ሰዉ ግራ የገባው በሀገራችን ታሪክ መሪ ታሞ ህዝብ አስታሞ ፤ መሪ ሞቶ ህዝብ ቀብሮ አያውቅም ፤ ይህ ይመስለኛል ጡዘቱን እንዲግል ያደረገው ፤ ምድር እኮ መቆያ እንጂ መሰንበቻ አይደለችም ፤ በዚች አጋጣሚ ሁላችን ራሳችንን ብናይ መልካም ነው ፡፡ ሞት ለማንም መቼም የማይቀር የሰው ልጅ የመጀመሪያ ምፅአት ነው ፤ እንደ አባቶቻችን አስተምህሮ ከተዘጋጁበት ወደ ዘለዓለማዊውና ሕያውነት የምንለወጥበት መንገድ ሲሆን ካልተዘጋጁበት ደግሞ እውነተኛ ወደሆነው የዘላለም ሞት የምንወሰድበት ነው- 'ከሞቱ አሟሟቱ' የሚባለውም ሆነ 'አሟሟቴን አሳምረው' የሚባለው ለዚህ ነው ፤ 


ትንቢተ ዳንኤል 5 23-31 ላይ
የመቅደሱንም ዕቃዎች በፊትህ አመጡ፥ አንተም መኳንንትህም ሚስቶችህም ቁባቶችህም የወይን ጠጅ ጠጣችሁባቸው ከብርና ከወርቅም ከናስና ከብረትም ከእንጨትና ከድንጋይም የተሠሩትን የማያዩትንም የማይሰሙትንም የማያውቁትንም አማልክት አመሰገንህ ትንፋሽህንና መንገድህን ሁሉ በእጁ የያዘውን አምላክ አላከበርኸውም።  ስለዚህም እነዚህ የእጅ ጣቶች ከእርሱ ዘንድ ተልከዋል ይህም ጽሕፈት ተጽፎአል። የተጻፈውም ጽሕፈት። ማኔ ቴቄል ፋሬስ ይላል። የነገሩም ፍቺ ይህ ነው ማኔ ማለት፥ እግዚአብሔር መንግሥትህን ቈጠረው ፈጸመውም ማለት ነው። ቴቄል ማለት፥ በሚዛን ተመዘንህ፥ ቀልለህም ተገኘህ ማለት ነው። ፋሬስ ማለት፥መንግሥትህ ተከፈለ፥ ለሜዶንና ለፋርስ ሰዎችም ተሰጠ ማለት ነው። የዚያን ጊዜም ብልጣሶር ለዳንኤል ሐምራዊ ግምጃ እንዲያለብሱት፥ የወርቅ ማርዳም በአንገቱ ዙሪያ እንዲያደርጉለት አዘዘ በመንግሥትም ላይ ሦስተኛ ገዥ እንዲሆን አዋጅ አስነገረ። በዚያ ሌሊት የከለዳውያን ንጉሥ ብልጣሶር ተገደለ። ሜዶናዊውም ዳርዮስ መንግሥቱን ወሰደ ዕድሜውም ስድሳ ሁለት ዓመት ነበረ

ይህን ታሪክ መጽሀፉ ላይ ሰፍሮ እናገኝዋለን ፤ የናቡከደነጾር ልጅ ብልጣሶር ለእግዚአብሔር መስዋት የሚቀርብበት የመቅደሱን እቃ አውጥቶ እንዴት እንዳቃለለ እግዚአብሔርም ተቆጥቶት ምን እንዳደረገው እናውቃለን ፤  የናቡከደነጾር ልጅ ብልጣሶር  ይህን ተግባር ከማድረጉ በፊት እግዚአብሔር ሁሉን ነገር ማድረግ ይችላል ፤ አሁንም በዋልድባ እየሆነ ያለው ነገር ማኔ ቴቄል ፋሬስ የማያጽፍበት ነገር አይታየንም ፤ በኦሪት ዘመን ስራውን ሲሰራ የነበረው እግዚአብሔር አሁንም ከእኛ ከሀጥያተኞቹ ጋር አለ ፤ ከነብያትና ከሀዋርያት ጋር የነበረው አምላክ አሁንም በመካከላችንን አለ ፤ ማቴዎስ 28 ፤ 20 ላይ ‹‹ እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ። ብሎ ቃል ገብቶልናል ፡፡ ‹‹እግዚአብሔር አምላክም ሰውን ከምድር አፈር አበጀው በአፍንጫውም የሕይወት እስትንፋስን እፍ አለበት ሰውም ሕያው ነፍስ ያለው ሆነ።›› ኦሪት ዘፍጥረት 27  ተብሎ ተፅፏል ፤ የእኛም ይሁን የባለስልጣኖቻችን ነፍስ ይህች ናት ፤ እኛ ግን አላስተዋልንም ፤ በሰው አፍንጫ የህይወት እስትንፋስ የሰጠን አምላክ የማንንም ሰው ነፍስ ለመውሰድም ይህን ያህል ለእርሱ ቀላል ነው ፤ እስክንወድቅ መጠበቅም የለብንም፡፡ ሟችና ሃላፊ መሆናችሁን አውቃችሁ የገዳሙን ህልውና የሚያሳጣ ስራ አትስሩ ፤ የሚበቅለው ሸንኮራ ጣፋጭ ስለመሆኑ እርግጠኛ አትሁኑ ፤ ባለቤቱ ለቤቱ ቀናተኛ መሆኑንም አትርሱ ፤ እግዚአብሔር ደግሞ አይተኛም ተብሎ ተጽፏል ፤ መንፈሳዊነትና አለማዊነት በአንድ ሚዛን ላይ የማይቀመጡ ቢሆኑም እግዚአብሔር መኖር ትጠራጠራላችሁ የሚል ግምት የለንም ፤ ናቡከደነጾር ሲበድል አምላክ ዝም ያለበት ምክንያት ‹‹እግዚአብሔር መሐሪ፥ ሞገስ ያለው፥ ታጋሽም፥ ባለ ብዙ ቸርነትና እውነት፥ እስከ ሺህ ትውልድም ቸርነትን የሚጠብቅ፥ አበሳንና መተላለፍን ኃጢአትንም ይቅር የሚል፥ በደለኛውንም ከቶ የማያነጻ፥ የአባቶችንም ኃጢአት በልጆች እስከ ሦስትና እስከ አራት ትውልድም በልጅ ልጆች የሚያመጣ አምላክ›› ስለሆነ ነው  ኦሪት ዘጸአት 346 እርሱ ታጋሽ በመሆኑ መታገሱን ማወቅ መቻል አለብን ፤ ትንቢተ ኤርምያስ 17፤10 ላይ ‹‹እግዚአብሔር ለሰው ሁሉ እንደ መንገዱ፥ እንደ ሥራው ፍሬ እሰጥ ዘንድ ልብን እመረምራለሁ ኵላሊትንም እፈትናለሁ።›› ተብሎ ተጽፏል አንዳች ከእርሱ የሚደበቅ ስራ ማንም የለውም ፤ በተጨማሪ የዮሐንስ ራእይ 2፤23 ላይ ‹‹ኵላሊትንና ልብን የምመረምር እኔ እንደ ሆንሁ ያውቃሉ፥ ለእያንዳንዳችሁም እንደ ሥራችሁ እሰጣችኋለሁ።›› ይላል ፡፡ ስለዚህ ከእርሱ የተደበቀ ከእርሱ የተሰወረ አንዳች ነገር የለም ዛሬ ላይ ሳታስተውሉ የሚሰራ ስራ  ነገ  በነፍስም በስጋም ከተጠያቂነት ነጻ አያደርግም ፤ ከታሪክ ተወቃሽነትም ወደ የትም አያሸሽም ፤ በስራችን ይመዝነናል ዋጋችንንም ይሰጠናል  ‹‹እግዚአብሔር ፈራጅ ነውና።›› መዝሙረ ዳዊት506 ፡፡ የራሄል እንባ 420 ዓመታት በግብጽ ሲማቅቁ የነበሩትን እስራኤላውያን ለመውጣታቸው መንስኤ ሆኗል ፡፡ ‹‹የዋይታና የመራራ ልቅሶ ድምፅ በራማ ተሰማ ራሔል ስለ ልጆችዋ አለቀሰች የሉምና ስለ ልጆችዋ መጽናናትን እንቢ አለች። ትንቢተ ኤርምያስ 31 ፤15 ፤ አሁንም አባቶች ስለምታደርጉት ነገር እያለቀሱባችሁ መሆኑን እወቁ ፤ እንባቸው ጎርፍ እንዳይሆንባችሁ ስጉ ፤ አምላካችን የራሄልን እንባ ከአይኗ የዳበሰ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር ነው ፡፡‹‹የሠራዊት ጌታ ከእኛ ጋር ነው የያዕቆብ አምላክ መጠጊያችን ነው። ›› መዝሙረ ዳዊት 46 ፤7 ተብሎ ተጽፏል፡፡ በተጨማሪ በትንቢተ ኢሳያስ 1፤24 ላይ ‹‹የሠራዊት ጌታ የእግዚአብሔር ቀን በትዕቢተኛውና በኵራተኛው ሁሉ ላይ ከፍ ባለውም ላይ ይሆናል፥ እርሱም ይዋረዳል›› ይላል ሀይል የእግዚአብሔር መሆኑን እናምናለን ፤ ነገር ግን ስጋውያን ትላንት ታይተው ከደቂቃዎች በኋላ እንደ ጤዛ የሚደርቁ ሰዎች በዘመናችን ቢያጋጥሙን ለሰው ልጅ ጉልበት የሚሆን ጉልበትንም የሚሰብር እርሱ አምላካችን  እግዚአብሔር መሆኑን እንወቅ፡፡ የክርስትያኖች  ጉልበታችን ጾማችን ፤ጸሎታችን ፤ምህላችን ፤ ስግደታችንና ወደ አምላክ የምናፈሰው እንባችን ብቻ ነው፡፡

‹እግዚአብሔር ስለ እናንተ ይዋጋል፥ እናንተም ዝም ትላላችሁ›› ኦሪት ዘጸአት 1414 ፤ ይህን ተግባር መቃወምም ሆነ መግታት ቢያቅተን መጽሀፍ ቅዱስ ‹‹ተሰለፉ፥ ዝም ብላችሁ ቁሙ፥ የሚሆነውንም የእግዚአብሔርን መድኃኒት እዩ እግዚአብሔርም ከእናንተ ጋር ነውና አትፍሩ፥ አትደንግጡም፥›› መጽሐፈ ዜና መዋዕል ካልዕ 20 ፤17 ይላል

አሁንም ተመዝናችሁ ቀላችሁ እንዳትገኙ ለራሳችሁ አስተውሉ ፤ መንግስታችሁንም እንዳይቆርጠው እንደዚያው ፤ ‹እውነተኛ ሚዛንና መመዘኛ የእግዚአብሔር ናቸው›› መጽሐፈ ምሳሌ 16፤11 በእርሱ ሚዛን ተመዝናችሁ እንደ ብልጣሶር  እንዳትቀሉ ለራሳችሁ ብላችሁ ተጠንቀቁ ‹‹እርሱ ታላቅ አምላክ ኃያልም የሚያስፈራም፥ በፍርድ የማያደላ፥ መማለጃም የማይቀበል ነውና››   ኦሪት ዘዳግም 10 ፤ 16 ነውና፡፡እኛ ግን እንደ ክርስትያን ለመሪዎቻችን ማስተዋሉን እና ጥበቡን ስጣቸው እያልን ዘወትር እንጸልያለን ብቻ እጃችሁን ከገዳሙ ላይ አንሱልን

ለጠቅላይ ሚኒስትራችን እግዚአብሔር ምህረቱን ያውርድላቸው...

ቸር ሰንብቱ

22 comments:

  1. ባለ እውነተኛው ሚዛን እግዚአብሔር እንደ ፈቃዱ ያድርግ!

    ReplyDelete
    Replies
    1. ኵላሊትንና ልብን የምመረምር እኔ እንደ ሆንሁ ያውቃሉ፥ ለእያንዳንዳችሁም እንደ ሥራችሁ እሰጣችኋለሁ

      Delete
  2. ‹‹እግዚአብሔር ስለ እናንተ ይዋጋል፥ እናንተም ዝም ትላላችሁ››

    ReplyDelete
  3. ጠቅላይ ሚኒስትርነት ስራ መሆኑን እስከ አሁን አናውቅም ነበር ፤ ይገርማል ፤ ለካ የመንግስት ተቀጣሪ ናቸውን ?

    ReplyDelete
  4. ኵላሊትንና ልብን የምመረምር እኔ እንደ ሆንሁ ያውቃሉ፥ ለእያንዳንዳችሁም እንደ ሥራችሁ እሰጣችኋለሁ

    ReplyDelete
  5. እኛ ግን እንደ ክርስትያን ለመሪዎቻችን ማስተዋሉን እና ጥበቡን ስጣቸው እያልን ዘወትር እንጸልያለን ብቻ እጃችሁን ከገዳሙ ላይ አንሱልን


    ‹እግዚአብሔር አምላክም ሰውን ከምድር አፈር አበጀው በአፍንጫውም የሕይወት እስትንፋስን እፍ አለበት ሰውም ሕያው ነፍስ ያለው ሆነ።›› ኦሪት ዘፍጥረት 2፥7 ተብሎ ተፅፏል ፤ የእኛም ይሁን የባለስልጣኖቻችን ነፍስ ይህች ናት ፤ እኛ ግን አላስተዋልንም ፤ በሰው አፍንጫ የህይወት እስትንፋስ የሰጠን አምላክ የማንንም ሰው ነፍስ ለመውሰድም ይህን ያህል ለእርሱ ቀላል ነው ፤ እስክንወድቅ መጠበቅም የለብንም፡፡ ሟችና ሃላፊ መሆናችሁን አውቃችሁ የገዳሙን ህልውና የሚያሳጣ ስራ አትስሩ ፤ የሚበቅለው ሸንኮራ ጣፋጭ ስለመሆኑ እርግጠኛ አትሁኑ ፤ ባለቤቱ ለቤቱ ቀናተኛ መሆኑንም አትርሱ

    ReplyDelete
  6. እግዚአብሔር ምህረቱን ያውርድላቸው...

    ReplyDelete
  7. አንድ በዋልድባ የሚኖሩ አባት ቪኦኤ ላይ የተናገሩትን ነገር ላስታወሰው ቀኑ መድረሱን ይረዳል ያሉትም እንዲህ ነበር “ዋልድባን የነካ አንድ ዓመትም አይቆይም” ብለው ነበር ይሄው ያሉት ደረስ፡፡

    ReplyDelete
  8. egzyabheyer maton gehanbe esatwen yalbsachew

    ReplyDelete
  9. በእምነት ከጸናን ገና ብዙ እናያለን አምላካችን ሁሉን ማድርግ ይችላል። ልቦና ይስጣቸው

    ReplyDelete
  10. Aba Paulos and aba Fanuel will be next.

    ReplyDelete
    Replies
    1. ante zeregna , christian negn degmo tilaleh? papas egziabher endemishom
      lalefut 100 ametat sitisebku neber eko

      Delete
  11. እኛ ግን እንደ ክርስትያን ለመሪዎቻችን ማስተዋሉን እና ጥበቡን ስጣቸው እያልን ዘወትር እንጸልያለን ብቻ እጃችሁን ከገዳሙ ላይ አንሱልን

    ReplyDelete
  12. Nice article it is. Ya, the GOD of our fathers will not stay silent. I my self believes his illness as a consequence of an evil practice they are doing at waldiba, he and they deserve even more than this... But as we are christians, we pray for him to get mercy, if he can get lesson. May God save our church from the work of devil and bless you brothers in God for your nice speculation.

    ReplyDelete
  13. ቃለ ሕይወት ያሰማልን! መጽሐፍ ቅዱስን ያጣቀሰ በሳል ክርስቲይናዊ ጽሁፍ። እግዚአብሔር አምላክ ቅዱስ ቤቱን ይጠብቅ፣ ለሥሙ ብለው ቤታቸውንና ንብረታቼውን ትተው የተሰደዱትን አባቶች እና ህዝበ ምዕመኑን ያበርታልን፤ ሃገራችን ኢትዮጵያን በምህረት ዓይኑ ይጎብኝልን። አሜን!

    ReplyDelete
  14. ቃለ ሕይወት ያሰማልን! መጽሐፍ ቅዱስን ያጣቀሰ በሳል ክርስቲይናዊ ጽሁፍ። እግዚአብሔር አምላክ ቅዱስ ቤቱን ይጠብቅ፣ ለሥሙ ብለው ቤታቸውንና ንብረታቼውን ትተው የተሰደዱትን አባቶች እና ህዝበ ምዕመኑን ያበርታልን፤ ሃገራችን ኢትዮጵያን በምህረት ዓይኑ ይጎብኝልን። አሜን!

    ReplyDelete
  15. Egziabher Lebonachewun yabra....egziabher tewagi new betekristianachen ytebkelen betselotm yatsnan

    ReplyDelete
    Replies
    1. አቤቱ እግዚአብሔር ሆይ በክንድህ ስያዝ እንዴት እሆን ይሆን?

      Delete
  16. egizabher mihretune yawuredelte, ethiopian yetebk

    ReplyDelete
  17. ድረ ገፃችሁ የሃይማኖት መስሎኝ ባነባት ከሰይፈ ነበልባል ነጎድግዋድ ከሚባሉት የፖለቲካ ማደናገርያ ጋዜጦች ተርታ አገኘክዋት፡፡ አዘንኩባችሁ፡፡ በእግዚኣብሄር ስም በሃይማኖት ስም አልባልታችሁን የምትነዙባት ማፈርያ ሆና አገኘክዋት፡፡

    ReplyDelete
  18. አሉባልታ መሆኗን እንዴት ልትረዳ /ልትረጂ/ ቻላችሁ? ወንድም እህቶቼ

    ReplyDelete
  19. እግዚአብሔር ይስጣችሁ ይሄ በሳል ጽሑፍ ነው
    ቃለ ህይወትን ያሰማልኝ
    ፍርድ የእግዚአብሔር ነውና ሁሉን ለእሱ መተው የክርስቲያን ተግባር ነው
    እግዚአብሔር ይቅርታውን ያዝንምልን የአባቶቻችንን እንባ ያብስ
    ከሰው ልጅ ጥፋት ከብረት ዝገት አይታጣም እንደሚባለው ሁሉ እነዚህ ሰዎች ባለማወቅ የሚያደርጉት ስለሆነ ይቅር ይበላቸው ትክክለኛውን መንገድ ይምራቸው ልቦና ይስጣቸው
    እኛ ጉልበት አጥተን የምናደርገው ጠፍቶን የሚሰማን ታጥቶ ዋልድባ ሲታረስ እጃችን ዝሎ እንዲሁ ዝም ብለን እያየን ነው በፈጣሪያችን ተመክተን ግን አላፈርንም
    እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን!!!

    ReplyDelete