Monday, October 15, 2012

ከተሀድሶያውያን ጋር አብረው ሲሰሩ የነበሩት አባ ናትናኤል በወንጀል ተከሰሱ



(አንድ አድርገን ጥቅምት 5 2005 ዓ.ም)፡- ባለፈው ዓመት  የሀዋሳን  ህዝብ  ሲያስለቅሱት  የነበሩት  ደብረ ገነት ቅድስት ሥላሴ ቤተክርስትያን   አስተዳዳሪ  ለአየር ጤና አንቀጸ ብርሃን ኪዳነ ምህረት ቤተክርስቲያን  አስተዳዳሪ ተደርገው  ከቤተክህነት  ተሾሙው እንደነበር በጊዜው ገልጸን መጻፋችን ይታወቃል ፤ ነገር ግን ህዝቡ እኝን አባት አስተዳዳሪ አድርገን አንቀበልም ብሎ እሳቸው በእግራቸው ቢመጡም በኮንትራት ታክሲ ከቤተክርስቲያን አባሯቸው ነበር ፤  በፊት በተሐድሶ እና ከፕሮቴስታንት  አራማጆች  (ተስፋኪዳነምህረት ማህበር እና ከመሰሎቻቸው ) ጋር  በመሆን የእግዚአብሔርን  አውደ ምህረት  እንዲፈነጩበት ካደረጉ ሰዎች መካከል ግንባር ቀደሙን የሚይዙ ሰው ናቸው ፡፡ በጊዜው ገንዘብ አይናቸውን አሳውሯቸው ፤ ለአውደምህረት የማይመጥኑ ፤ ትምህርቱ የሌላቸው  ሰዎችን በመጋበዝ ህዝቡን እዚህ ደረጃ እንዲደርስ ካደረኩ ሰዎች መካከል አንዱ ናቸው፡፡

የአየር ጤና ኪዳነ ምህረት / አስተዳዳሪ ተደርገው ተሹመው የነበሩት አባ ናትናኤል መላኩ  ጥቅምት 2 ቀን 2005 ዓ.ም ከቀኑ 900 አካባቢ በአዋሳ ፖሊሶች ተይዘው ተወስደዋል፡፡ የአዋሳ ቅድስት ሥላሴ አጥቢያ ህዝብ 170 ሺህ ብር በላይ እና በቤተክርስቲያኗ መኪና ዝርፊያ ክስ በመመስረቱና ፍርድ ቤቱ ተይዘው እንዲቀርቡ በማዘዙ  አለምገና አካባቢ ከሚገኘው መኖርያ ቤታቸው ተይዘው ተወስደዋል፡፡ 



በጊዜው አባ ናትናኤል ለአየር ጤና አንቀጸ ብርሃን ኪዳነ ምህረት ቤተክርስቲያን  አስተዳዳሪ ተደርገው ሲመደቡ ፤   የሃይማኖት ሕፀፅ እንዳለባቸው ፤ ሐዋሳ ላይ ከእነ በጋሻው ጋር ግሩፕ በመፍጠር ‹‹ያለ ነውጥ ለውጥ አይገኝም› ብሎ በመስበክ ፤ ሰውን ለአመፅ በማነሳሳት ፤ እና በከፍተኛ ሁኔታ የገንዘብ ምዝበራ ወንጀል ክስ የቀረበባቸው በመሆኑ እንደዚህ ዓይነት ሰው መመደቡ ለቤተክርስቲያኒቱ ከፍተኛ ጉዳት የሚያስከትል በመሆኑ በጊዜው እንዲመለሱ እንዲደረግ በማለት ለሕዝቡ አስፈላጊው መግለጫ ከተደረገ በኋላ ሕዝቡም የ‹‹አንፈልጋቸውም›› ድጋፉን  በመግለጹ በመጡበት እግራቸው በሰላም ሌላ ብጥብጥ በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ ከመከሰቱ በፊት  ሸኝተዋችዋል ነበር ፤


በጊዜው የቤተክርስቲያኗ አባቶች ተሰብስበው ቤታቸው ያለ አስተዳዳሪ በመቆየቱ ቤተክህነት ድረስ በመሄድ “አባት ይሾምልን ያለ አስተዳዳሪ ወራት ቆጠርን” ብለው በአንድነት ጥያቄያቸውን አቅርበው ነበር፡፡ ከቀድሞ ፓትርያርክ ከአቡነ ጳውሎስ የተሰጣቸው መልስ ግን ‹የተሸመላችሁን አባት ለምን አልተቀበላችሁም› የሚል ነበር ፡፡ ያልተቀበሉበትን ምክንያት አስረግጠው በመነጋገር “በቃ እሺ ይሾምላቿል” ብሏቸዋቸው ካበቁ በኋላ  ‹‹ማነው ደግሞ አልቀበልም ያለው›› ብለው በፊት የሾሟቸውን የተሀድሶ አቀንቃኝ አባ ናትናኤልን ደግመው ሾመውላቸዋል፡፡ እሳቸውም እስከ አሁኑ ሰዓት ድረስ አስተዳዳሪ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ 


ጊዜያት ሊያልፉ ይችላሉ ወራት ሊፈራረቁ ይችላሉ ዓመታትም ሊቆጠሩ ይችላሉ ፤ ሰዎች ግን ቤተክርስቲያን ላይ በፈጸሙት ወንጀል ተጠያቂ የማይሆኑበት አንዳች ምክንያት አይኖርም፡፡

No comments:

Post a Comment