Wednesday, January 25, 2023

"አባዬ ወዴት ወዴት"


ይድረስ ለአባ ዜና ማርቆስ 

ሊቀ ጳጳሳቱ (ፓትርያርኩ) ካልፈቀዱ ማንም ቢሆን ኤጲስ ቆጶስነት እንዳይሾም ፍትሐ ነገሥቱ ይነግረናል። ከተሾመም ሲኖዶስ ያወግዘዋል ተብሎ በግልጽ አማርኛ ተጽፏል።
                             
ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፭ ቁጥር ፺፩ ወለእመ ኀሠሠ አሐዱሂ ኤጲስ ቆጶስና ወሠምሩ ቦቱ ኵሎሙ ሰብአ ሀገሩ። አንዱ ኤጲስ ቆጶስነት ሊሾም ቢሻ ወሠምሩ ቦቱ ኵሎሙ ሰብአ ሀገሩ የሀገሩ ሰዎች ቢፈቅዱለት። ወኢሠምረ ቦቱ ጳጳሰ ብሔሩ ኢይደልዎ ኤጲስ ቆጶስና። የሀገሩ ጳጳስ ቢፈቅድ ነው እንጂ የሀገሩ ጳጳስ ካልፈቀደለት መሾም አይገባውም። ወዘንተ ለእመ ተዐደወ ሲኖዶስ ያወግዞ ይህን አፍርሶ ቢሾም ጉባዔ ይለየዋል። ወእመሰ ኀብሩ በእንቲአሁ ዘይበዝኁ ብዙዎች አንድ ሆነው ሹመቱን ቢፈቅዱለት ግን ወሠምሩ ቦቱ ጳጳስ ወሊቀ ጳጳሳት ይግበሩ በምክሮሙ ለእለ ይበዝኁ። ጳጳሱ ሊቀጳጳሱ ከወደዱ በብዙዎች ፈቃድ ይሾም። ሲሾምም "፪ ወይም ፫ ኤጲስ ቆጶሳት ይሹሙት" ተብሎ ቁጥር ፺፪ ተጽፏል። አቡነ ዜና ማርቆስ ይችኛዋን ብቻ ይዘው የላይኛውን ትተው እንደ መ*ና*ፍ*kan ግማሹን ይዘው ግማሹን ትተው ሕገወጥነትዎትን ለመሸፋፈን አይሞክሩ። ፍትሐ ነገሥትም ሌላውም ቅዱሳት መጻሕፍት በምልዐት ይጠቀሳሉ እንጂ አንዱን ትቶ አንዱን አንጠልጥሎ አይጠቀስም። ሊቀ ጳጳሳቱ (ፓትርያርኩ) ካልፈቀዱ ማንም ቢሆን ኤጲስ ቆጶስነት እንዳይሾም ፍትሐ ነገሥቱ ይነግረናል። ከተሾመም ሲኖዶስ ያወግዘዋል ተብሎ በግልጽ አማርኛ ተጽፏል። ጵጵስና ሦስት መዓርጋት አሉበት። የመጀመሪያው ኤጲስ ቆጶስ ነው። አዲስ ተሿሚ ነው። ከዚያ የተወሰኑ ኤጲስ ቆጶሳትን አቅፎ መሪ የሆነው ጳጳስ (መጥሮጶሊስ) ይባላል። ከዚያ የጳጳሳትም የኤጲስ ቆጶሳትም የበላይ ደግሞ "ሊቀ ጳጳሳት (ፓትርያርክ)" ይባላል።
                                
ሌላው አቡነ ዜና ማርቆስ ሊያጭበረብሩ የሞከሩት ሥርዐት ስለሚሻሻል ማሻሻል እንችላለን የሚል ምክንያት ጠቅሰው የሰሩትን ሕገ ወጥነት ለማለባበስ ሞክረዋል። እውነት ነው ሥርዐት ከዘመን ዘመን ከቦታ ቦታ ሊለወጥ ይችላል። ለዋጩ ግን ማን ነው? የሚለውን ማወቅ ያስፈልጋል። ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፶፩ ቁጥር ፲፻፰፻፲፮ (1816) ወዘሰ ብውሕ ለሊቅ ዘውእቱ ሊቀ ጳጳሳት ከመ ይወስክ ዲቤሁ ወያንትግ እምኔሁ። በተጻፈው ላይ ይጨምር ዘንድ ከተጻፈው ይከፍል ዘንድ ለሊቀ ጳጳሳት የሚገባው ዝኒ ይህ ነው። ካለ በኋላ ዶግማ እንደማይለወጥ በቁጥር 1817 "በተጻፈው ላይ መጨመር ከተጻፈው መክፈል ግን ለማንም አይገባውም" ተብሎ ተገልጿል። ሊቀ ጳጳሳት ማሻሻል ይችላል የተባለውን ሥርዓት በቁጥር 1818 "ላይ ጉባኤ ያልቆመለት በመጻሕፍት ያልተገለጸ ሥርዐት ከሆነ ነው" ይላል። ይህንን የማድረግ ሥልጣን ያለውም ሊቀ ጳጳሳቱ (ፓትርያርኩ) እንጂ ጳጳስ አይደለም። ፓትርያርክ እንኳ ይህንን ለማድረግ ቅድመ መሥፈርቶች አሉት። እነዚህም ከቁጥር 1821 ጀምሮ ተጠቅሷል። የቅዱሳት መጻህፍትን ትርጓሜ የሚያውቅ ምሁር ይሁን። የቅዱሳን አባቶችን የጉባዔ ውሳኔዎች የሚያውቅ ይሁን። በተጨማሪም ትሩፈ ምግባር የሆነ ደግ ሊሆን ይገባል ይላል። ይህ ሁሉ ሲሆን እንኳ ጳጳሳት ሁሉ ተስማምተውበት እንጂ ብቻውን ፓትርያርክ እንኳ ሥርዐት መለወጥ አይችልም። ፍት. ነገ. ፶፩፣ ፲፻፰፻፳፮ "ይደሉ ከመ ይትጋብኡ በእንቲኣሁ ኤጲስ ቆጶሳት" ስለ ጉዳዩ ኤጲስ ቆጶሳት ይሰብሰቡና ይምከሩበት ተብሏል።
                            
ስለዚህ አቡነ ዜናማርቆስ ያነሱት ሐሳብ ፍጹም የተጭበረበረ። ሕገ ወጥነትዎን ለመሸፋፈን ያቀረቡት ነው። ነገር ግን ፍትሐ ነገሥቱ የእርስዎን ሕገ ወጥነት እንደማይፈቅድ ይመልከቱት።
                            ።
መ/ር በትረማርያም አበባው
(የፍትሐ ነገሥት ትርጓሜ መምህር)

No comments:

Post a Comment