Tuesday, November 6, 2012

የኃይለማርያም አጣብቂኝ በመንፈሳዊ ሕይወትና በፖለቲካዊ ማንነት ውስጥ

ከአዲስ ጉዳይ መጽሄት
ቅጽ 6 ቁጥር 136 ጥቅምት 2005 ዓ.ም

  • እኔ ችግር ያለብኝ እናቴ አልዳነችም› ማለታቸው ላይ ነው ፤ እንደዚህ ማለታቸው ሌሎቹም ሁሉ እንዳልዳኑና እሳቸው ብቻ እንደዳኑ የሚያረጋግጥ ሃሳብ ነው፡፡” ፕሮፌሰር መስፍን
  • አቶ ኃ/ማርያም ለቀድሞ ጠ/ሚኒስትር ዘላለማዊ  ክብር እመኛለሁማለታቸውን እንደተጸጸቱበት ተናግረዋል፡፡
  • “እናቴ አልዳነችም”  ብለው መናገራቸው ራሱ በጣም የሚያሳዝንና  ሞኝነት ጭምር ነው፡፡  ይህ እኮ ሁላችንም ማለትም ኦርቶዶክስም ፤ ሙስሙና ካቶሊኩ በሙሉ አለመዳናችንን የገለጹበት ቀላል አሽሙር ይመስለኛል” ዶ/ር ያእቆብ
  • “አቶ ኃይለማርያም የአቶ መለስን ራዕይ ለማስጠበቅና በሃይማኖተኛነት መካከል እየዋለሉ የሀገሪቱን ሕገ መንግስት ሊጥሱ ይችላሉ” ዶ/ር ያእቆብ
  • ዛሬ ስለ ሃይማኖት መጠቃቀስ የጀመሩት የአገር መሪ ነገ ደግሞ  ስልጣናቸውን ተጠቅመው እግዚአብሔርን ማገልገል በሚል ሰበብ  ሃይማኖታቸውን ለማስፋፋት ምን ያዳግታቸዋል?

(አንድ አድርገን ጥቅምት 27 2005 ዓ.ም)፡- ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ስልጣናቸውን ከተረከቡ ወዲህ ህዝብ ስለ እኚህ አዲሱ መሪ ስብዕና የተለያዩ አስተያየቶችንና ቅድመ ግምቶችን ሲያንጸባርቅ ቆይቷል ፡፡ መገናኛ ብዙሃኑ በተለይም የህትመት ሚዲያው እንዲሁም ድህረ ገጹ በአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር የፖለቲካ ብቃትና የፊት ለፊት ተግዳሮቶች ዙሪያ ያላቸውን አስተያየት በመረጃና ትንተና ላይ ተመርኩዘው ለንባብ አብቅተዋል ፡፡ ሰውየው ወደ ስልጣን ከወጡ ብዙም ጊዜ አላለፈምና አሁንም አዲስ ተብለው ቢጠሩ አይገርምም ፤ አዲስ ነገር ደግሞ ሁሌም በውስጡ የሚነገር ወሬ አያጣውም ፡፡ አዲስ ጉዳይ እስከ አሁን ስለ ኃይለማርያም ደሳለኝ ለንባብ ካበቃቻቸው ጉዳዮች ውስጥ የዛሬውን ርዕሰ ጉዳይ ለዳሰሳ መርጦት አያውቅም፡፡ ይህም የሆነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚከተሉት ሃይማኖት የግል በመሆኑና ይህም እምነታቸው በፖለቲካ ህይወታቸው ውስጥ ጣልቃ ገብቶ ለንግግር የሚያበቃ ጉዳይ እስካልፈጠረ ድረስ ነገሩ እንደ አንድ ጉዳይ አንስቶ ማራገብ ፋይዳ የለውም ተገቢም አይደለም በሚል እምነት ነው፡፡

ዛሬ ግን አቶ ኃይለማርያም እምነታቸውንና ፖለቲካቸውን የሚያቆራኝባቸው ነገር ፈጥረዋል “በጠቅላይ ሚኒስትርነት ከተሸሙ በኋላ ለአንድ ሃይማኖት ሚዲያ በሰጡት ቃለ ምልልስ” በሚል ሰንደቅ ጋዜጣ ላይ የወጣው ይህ ቃለ ምልልስ ጉዳዩን ከእሳቸውና ከድረ-ገጽ ታዳሚያን የእምነቱ ተከታዮች አልፎ ወደ መነጋገሪያ ርዕስነት ተቀይሯ ፡፡ በዚህ ጉዳይ የተነሳ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝን የዛሬ ጽሁፋችን መዳረሻ አድርገናቸዋል፡፡
ሃይማኖት የግል ሐገር የጋራ ነው
ማንኛውም ሰው በግሉ ድህነትን ያስገኝልኛል የሚለውን እምነት ያለማንም ጣልቃ ገብነት የመከተልና የማክበር መብት አለው ፡፡ ይህ የማይጣስ ሕገ መንግስታዊ መብቱ ነው ፡፡ ማንም ሰው በሚከተለው እምነት ሳቢያ መገለል ወይም አድልዎ አይደረግበትም ፡፡ ይህም እውነት ነው ፡፡  በደርግ ዘመን የቀድሞውን የመንግስት አመራር ለማጥፋት እንዲሁም ኮሚኒስታዊ አስተሳሰብ ለማስረጽ ተብሎ የመንግስት ባለስልጣናት በሃይማኖት ነክ ጉዳዮች ላይ ጫፋቸውን እንዳያስነኩ በጥብቅ መመሪያ ተሰጥቷቸው ነበር ፡፡ ጉዳዩ ከዚህ አልፎ “እንደምን አደርክ” ሲባሉ “እግዚአብሔር ይመስገን” የሚለው ቃል ተናግረው አማኝነታቸውን እንዳያሳዩ በማለት “እናሸንፋለን” የሚል ምላሽ እንዲሰጡ ይታዘዙ ነበር፡፡ የተወካዮች ፊት ለፊት ያለውን ሥላሴ ቤተክርስቲያን እንኳን “ ሃይማኖትንና መንግስትን ለመለያየት” በሚል ሰበብ በግንብ ታጥሮ ነበር ፡፡ የደርግ ካድሬዎችና ባለስልጣናት ቤተክርስቲያን ሲሳለሙ ከተገኙ ከባድ ግምገማና ቅጣት ይጠብቃቸውም ነበር ፡፡ ይህ እጅግ የከፋና ፍጹም የማይገባ የሰብአዊ መብት ጥሰት ነው፡፡ ሰውን መንፈሳዊ ነጻነት አሳጥቶ መንግስሥትህን አገልግል ማለት ረግጦ ከመግዛት አይተናነስም፡፡
እነሆ የኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት መንግሥትና ሃይማኖት የተለያዩ መሆናቸው ቢያውጅም የግለሰቦችን የእምነት ነጻነት ግን ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ አረጋግጧል፡፡ በዚህም አንድ ዜጋ ተራም ይሁን የሃገሪቱ ቁንጮ ያሻውን ሃይማኖት የመከተልና ባሻው መንገድ የእምነት ነጻነቱን የሌላውን እምነት እስካልነካ ድረስ የመፈጸም መብት አለው፡፡  ለዚህም ማረጋገጫ አቶ መለስና ሌሎች ባለስልጣናት ቤተክርስቲያን ሲሳለሙ ባናያቸውም ከጳጳሳቱ እጅ መስቀል ሲሳለሙ የተነሱት ፎቶ በአደባባይ አይተናል፡፡ ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣናት መስኪድ ሲገቡ ባያጋጥሙንም በተለያዩ የሙስሊም በአላት ላይ ስታዲየም ተገኝተው ሲሰግዱ አስውለናል፡፡
ባለፉት 21 ዓመታት የመንግስት ባለስልጣናት የሚከተሉትን እምነት በተመለከተ ከዚህ የዘለለ ምንም ነገር የማናውቀው በአንደበታቸው ጉዳይም እንደ ርዕስ ሲያወሩ ስላልሰማን ነው፡፡ በቅርቡ ምናልባት ለመጀመሪያ ጊዜ ከአቶ ጁነዲን ሳዶ የሰማነውና “መስኪድ እያሰራን ነው” የሚለውን ቃል ባለቤታቸው ከታሰሩ በኋላ  ለሚዲያዎች በጻፏቸው ደብዳቤዎች ለንባብ ሲያበቁ በብዙዎች ዘንድ ግርምት ፈጥሮ ነበር፡፡ ባለስልጣናት በሃይማኖት ጉዳይ በግላቸው የሚያደርጉት ነገር በተመለከተ ሲናገሩ ተደምጦ ስለማያውቅ የሚኒስትር ጁነዲን ተግባር “ የመንግሥትን ሥራ መስራት ወይስ ሃይማኖትን ማስፋፋት” የሚል መነጋገሪያ አጀንዳ ሆኖም ነበር፡፡ በዚህና በተያያዥ ነገሮች የተነሳ ጉዳይ ጦዞ ሚኒስትሩ ዛሬ ከፓርቲው አመራር ኃፊነታቸው ተነስተው ተራ አባል ተደርገዋል፡፡ በሚኒስትርነታቸው መቀጠላቸውም አጠራጣሪ እየሆነ ነው፡፡
እምነትና አቶ ኃይለማርያም
ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የክርስትና ስማቸውን የወረሰው መጠሪያ ስማቸው በኦርቶዶክስ እምነት አካባቢ ያሉ ቢያስመስላቸውም የሐዋርያት እምነት ተከታይ መሆናቸው ስልጣን ላይ እንደወጡ ሰሞን ነው የታወቀው፡፡ ተጠባባቂ ጠቅላይ ሚኒስትር ተብለው የተሾሙበት የመጀመሪያ ቀናት  ባደረጉት የመጀመሪያ ንግግር “በሙላት ፤ መገለጥ” እና ሌሎችንም ሃይማኖታዊ አገባብ ያላቸውን ቃላት መጠቀማቸውን ያስተዋሉ እምነታቸው አካባቢ ጠበቅ ያሉ ሰው መሆናቸውን  ገምተዋል፡፡  የርሳቸው ጠቅላይ ሚኒስትር መሆን አስመልክቶ  ከሃገር ውስጥ የተላከ  ይፋዊ የደስታ መግለጫ መልዕክት ከነበረም ብቸኛው ከርሳቸው ሃይማኖት ቤተክርስትያን የተላከና አዲስ ዘመን ጋዜጣ ላይ የታተመው መግለጫ ነበር፡፡
ብዙም መነጋገሪያ ያልነበረው ይህ ጉዳይ ወደ ርዕስነት የተቀየረው ኃይለማርያም ጠቅላይ ሚኒስትር ከሆኑ በኋላ  ፤ ፓርላማ ቀርበው ለጥያቄዎች ምላሽ ከመስጠታቸው በፊት ፤ ለጋዜጠኞች ይፋዊ የፕሬስ መግለጫ ሳይሰጡ በፊት ፤ ከአንድም የመንግስት ሆነ የግል ሚዲያ ጋር ልዩ ቃለ ምልልስ ሳያደርጉ በፊት በሚከተሉት እምነት ዙሪያ ከሚዘጋጅ አንድ መንፈሳዊ የፕሮቴስታንት ሚዲያ ጋር አደረጉት በተባለው ቃለ ምልልስ የተነሳ ነው ፡፡
የአቶ ኃይለማርያም ቃለ ምልልስ በህዝብ ዘንድ  ትኩረት እንዲያገኝ ያደረገው ምክንያት ሰውየው በመግለጫቸው ባቀረቡት አዲስ የለውጥ ሃሳብ ወይም ፖሊሲ ማሻሻያ ሳይሆን ከተለመደው አሰራር ውጪ በመሄድ የተለያዩ ሃይማኖቶችና እምነቶችን በሚከተል ፤ ከሰማንያ በላይ ብሔርና ብሔረሰቦች ባቀፈና ከሰማንያ ሚሊዮን በላይ ቁጥር ያለው ህዝብ ሃገር መሪ ሆነው ሳለ በማይጠበቅ ሁኔታ በብዛት ሃይማኖት ላይ ያተኮሩ አስተያየቶችን በመሰንዘራቸው ነው፡፡
አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓለማዊውንና አጣዳፊውን የህዝብ ጉዳይ ትተው ሃይማኖታቸውን በተመለከተ አስተያየት በመስጠት እንደዚህ መትጋታቸውንና መጣደፋቸውን በእርግጥ ግር የሚያሰኝ ነገር ነው፡፡ የህዝቡን አጣዳፊ ችግሮች የሚፈቱበትን መንገድ በተመለከተ የመንግስትንም ሆነ የግል ሚዲያውን ከመቅረባቸው በፊት መንፈሳዊ ሚዲያዎችንና ድረ ገጾች ላይ ማተኮራቸው ሲታሰብ ደግሞ የአቶ መለስ ግልባጭ ናቸው ብሎ ለሚያስባቸው ሰው ከአቶ መለስ ስብዕና ጋር የማይገናኝ ባህሪ ያላቸው መሆኑን እንዲረዳ ያደርገዋል፡ አቶ ኃይለማርያም ካደረጉትና ለዚህ ጽሁፍ አስፈላጊ ሆነውን ብቻ ከዚህ በታች በተቀመጡት ርዕሶች ስር እያነሳን የምንተነትነው ይሆናል፡፡
አፍ ሲያመልጥ ፤ ራስ ሲመለጥ
የአቶ ኃይለማርያም ወላጅ እናት የሚከተሉት ሃይማኖት እምነት ሰውየው ከሚከተሉት የተለየ በመሆኑ ሳቢያ በአቶ ኃይለማርያም ዐይን እናታቸው “አልዳኑም”፡፡  በቃለ ምልልሳቸው የተናገሩትንም ይህንኑ ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የእናታቸውን አለመዳንና እየጸለዩላቸው ስለመሆኑ ፤ ከራሳቸው ጀምሮ እስከ ቤተሰባቸው የእለት ተእለት መንፈሳዊ ህይወት በተመለከተ ፤ ለቀድሞ ጠ/ሚኒስትር “ዘላለማዊ ክብር እመኛለሁ” ማለታቸውን እንደተጸጸቱበት ተናግረዋል፡፡ በዚች አጭር ጊዜ ውስጥ አቶ ኃይለማርያም ሃይማኖት ሃይማኖት የሚሸቱ ሃሳቦችን በፌስ ቡክ አድራሻቸው ሳይቀር በመጻቸው ሃላፊነት በጎደለው ሁኔታ ሃይማኖትንና የመንግስት ስራን እያደበላለቁ ነው ተብለው ተተችተዋል ፤ አለበለዚያም ሃይማኖትን በተመለከተ የመንግሥት አሰራር ካስቀመጠው መመሪያና መንፈስ ውጪ እየሄዱ ነው ተብለው የማኅበራዊ ገጾች የጋዜጦችና የህዝብ መዘባበቻ ሆነው ከርመዋል፡፡  በተለይ በቅርቡ ማንም ሰው መንፈሳዊ ጉዳዮችን በተመለከተ በመዝሙር በተለጣፊ ጽሁፎች በልዩ ልዩ መንገዶች ጭምር በስራ ቦታዎች ፤ በህዝብ መገልገያ ቦታዎች እንዲሁም ትራንስፖርት መኪኖች ውስጥ እንዳይጠቀም ለማገድ መመሪያ ይወጣል እየተባለ ባለበት በዚህ ወቅት የጠቅላይ ሚኒስትሩ ሃይማኖት ነክ ጉዳዮች ላይ ተሳትፎ ማብዛት አስደማሚ ሆኗል፡፡
ይህን በተመለከተ ለአዲስ ጉዳይ ሃሳባቸውን ያካፈሉት ፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያም ጠቅላይ ሚኒስትሩን ከፖለቲከኛነት ይልቅ ሃይማኖተኛ ሆኖ ለመታየት የሚያደርጉትን ጥረት እንዳልወደዱት ይናገራሉ ፤

“የራሳቸውን ሃይማኖት የተለየ እንደሆነ አድርገው መግለጻቸው ላይ ችግር የለብኝም ፤ እኔ ችግር ያለብኝ ‹እናቴ አልዳነችም› ማለታቸው ላይ ነው ፤ እንደዚህ ማለታቸው ሌሎቹም ሁሉ እንዳልዳኑና እሳቸው ብቻ እንደዳኑ የሚያረጋግጥ ሃሳብ ነው ፤ ከዚያ ውጪ ራሳቸውን የተለዩ አድርገው ማየታቸው ከመሪ የሚጠበቅ ተግባር አይደለም፡፡  እንደ መሪ ለቤተሰብ ጋር የምታወራውን ህዝብ ላይ መገልበጥ ተገቢ አይደለም፡፡ ስሜት ሊጎዳ ይችላል ብሎ ጥንቃቄ መውሰድ ይኖርበታል፡፡ በሌላ መንገድ ከተመለከትነው ሰውየው ገና አዲስና በሃይማኖት ውስጥ ሲመሩ የቆዩ በመሆናቸው የእግዚአብሔርን ስም የሚጠራ ሰው ብቅ ማለቱ ደህና ነው፡፡ ግን የቱን ከየቱ እንደሚያያይዙት ገና ያልገባቸው ይመስለኛል ፤ ለዚህ ትንሽ ጊዜ መስጠት እንዳለብን ይሰማኛል ፡፡ ስለ ሃይማኖት የተናገሩትና ፓርላማ ውስጥ የሚናገሯቸው ሃሳቦች አብረው የሚሄዱ አይደሉም ፤ ሃይማኖተኝነታቸውን አጉልተው ማሳየታቸውን ፖለቲከኝነታቸው ላይ ትልቅ የጥያቄ ምልክት አስቀምጦባቸዋል” ብለዋል

የሕግ ምሁሩ ዶ/ር ያእቆብ ወልደማርያም በበኩለላቸው ለአዲስ ጉዳይ እንደገለጹት “አቶ ኃይለማርያም የአቶ መለስን ራዕይ ለማስጠበቅና በሃይማኖተኛነት መካከል እየዋለሉ የሀገሪቱን ሕገ መንግስት ሊጥሱ ይችላሉ” በማለት ስጋታቸውን ያስቀምጣሉ ፡፡

አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር አዲስ ሃሳብ ይዘው መጥተው ሀገሪቱን ለመለወጥ ሳይሆን አቶ መለስን ራዕይ ለማሳካት ቦታውን እንደተረከቡት በየጊዜው የሚናገሩት ማድመጥ ብቻ በቂ ነው፡፡ አንድ ሰው ለአንድ ሀገር ያለው ራዕይ ለማሳካት ዝም ብሎ ቆሞ የሚጠብቅ ሳይሆን በየጊዜው የሚለዋወጥ መሆን ይገባዋል  ፡፡ በአንድ ራዕይ ደርቄ እቀራለሁ ማለት ካለሁበት አልንቀሳቀስም የረገጡትን እረግጣለው ማለት ተገቢ አይደለም ፡፡ ይህንን ሃሳብ በፍጹም አልስማማበትም ፤ ለአንድ ሀገር ያለህን ራዕይ እየተቀየረ እየተሻሻለ ከጊዜ ሂደት ጋር እያስማሙ መሄድ ያስፈልጋል እንጂ አንድ ራዕይ በድንጋይ ተቀርጿል ከዚያ በላይ የሚለወጥ ነገር የለም ማለት በጣም ስህተት ነው፡፡ አንድን መሪ እንደ መሪ ከጊዜው ጋራ እያስማሙ ጊዜ የሚጠይቀውን እየፈጸመ እና እያስተካከለ ይሄዳል እንጂ ባለበት መርገጥ ከሆነ መሪ ሊባል አይገባል ፡፡ መሪ ፈጣሪ እና ህዝቡን ወደ ፊት የሚያራምድ መሆን መቻል አለበት” ነው ያሉት፤ ዶ/ር ያዕቆብ የሃይማኖትን ጉዳይ በተመለከተ ሲናገሩ እንዲህ ብለዋል ፡፡


“አንደ ሀገር መሪ የአንድን ሃይማኖት ሃሳብ ብቻ ማንጸባረቃቸው ተገቢ አይመስለኝም፡፡ ሃይማኖት የግል ጉዳይ ነው ከፖለቲካ ጋር ሊጣበቅ አይገባም ፡፡ ሕገ መንግስቱ ላይ ‹መንግስት በሃይማኖት ጉዳይ ውስጥ ጣልቃ አይገባም፡፡ ሃይማኖትም  በመንግስት ውስጥ ጣልቃ አይገባም በሚል ተቀምጧል ፡፡ እንዲህ ብለው መናገራቸው  በተዘዋዋሪ  የሚከተሉትን ሃይማኖት እንደመስበክ ነው የሚቆጠረው፡፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር እንደመሆናቸው መጠን በሌላው ላይ ተጽህኖ ማሳረፍ የለባቸውም፡፡ እንደሚዘምሩ አገልጋዮች ቤታቸው ውስጥ ጸሎት እንደሚያደርጉላቸውና ሃይማኖታዊ ትምህርት እንደሚሰጧቸው ተናግረዋል፡፡ ግን ይህ ሁሉ ነገር ለእኛ ምን ያደርግልናል ? ምንስ ይጠቅመናል  ? ጊዜ ከመግደል ውጪ ለኢትዮጵያ ህዝብ አንድም የሚፈይደው ጉዳይ የለም፡፡ “እናቴ አልዳነችም”  ብለው መናገራቸው ራሱ በጣም የሚያሳዝንና  ሞኝነት ጭምር ነው፡፡  ይህ እኮ ሁላችንም ማለትም ኦርቶዶክስም ፤ ሙስሙናቶሊኩ በሙሉ አለመዳናችንን የገለጹበት ቀላል አሽሙር ይመስለኛል” ብለዋል፡፡

እንደ መሪ የቋንቋ ፕሮቶኮል ሊኖራቸው አይገባም ? በሚለው ሐሳብ ላይም ዶ/ር ያዕቆብ አስተያየት አላቸው፡፡ “እርግጥ  ወደ ሕዝብ የሚያስተላልፉት ሐሳብ ከሀገሪቷ  ሁኔታና ዓላማ  ጋር የተመዛዘነ መሆን አለበት እንጂ ሌላ ነገር ማንጸባረቅ አይኖርባቸውም፡፡ ቋንቋ መግባቢያ ነው ፡፡ ብሔረሰቦች በቋንቋቸው ሊናገሩ ሊጽፉ ይችላሉ፡፡ ከዚያ ውጪ ሕዝብ የማያምንበት እንዲከተል መቀስቀሻ አይደለም፡፡” ብለዋል፡፡
ከላይ የተጠቀሱት የህዝብና የሚዲያ አስተያየቶች በሙሉ መሰረተ ቢስ ናቸው ማለት አይቻልም፡፡ ለምሳሌ ያህል አቶ ኃ/ማርያም በጠቅላይ ሚኒስትርነት የተረከቡትን የመንግሥት ኃላፊነት ከሃይማታዊ ተልዕኮ ጋር ደባልቀውታል ለማለት ከመንፈሳዊ ሚዲያ ጋር ያደረጉት ቃለ ምልልስ ማየት ይጠቅማል ፡፡ በዚያ ቃለ ምልልስ ውስጥ ስለሳቸው የሕይወት ጥሪ ተጠይቀው ሲመልሱ ፤ “እንግዲህ ጥሪ የተለየ ነው፡፡ ሁላችንም መሰዊያ ላይ ቆመን አንሰብክም፡፡ እኔን ደግሞ የተሰጠኝ የሚመስለኝ ፀጋ ህዝብንና አገርን በመልካም አስተዳደር ማገልገል ነው፡፡ ስለዚህ ለእኔ ሥራዬን ሥራ ብቻ ሳይሆን አገልግሎትም ጭምር ነው ብዬ ነው የተቀበልኩት” ብለዋል፡፡ በሌላ አነጋገረር የመንግስት ኃላፊነታቸውን የመንፈሳዊ አገልግሎት አንዱ መገለጫ ነው ማለት ነው፡፡ አገርን ማገልገል ከህዝብ ሳይሆን ከእግዚአብሔር የተሰጣቸው ጸጋ ነው፡፡ እንደሳቸው አስተያየት ከሆነ “መልካም አስተዳደር” የሚባለው ዓለማዊ የፖለቲካ ዘይቤ የሃይማኖታዊ ፀጋ መገለጫ ነው፡፡
ልዩ ትኩረት የሳበው የአቶ ኃይለማርያም ነገር
“ዘላለማዊ ክብር” ለአቶ መለስ በመመኝት ፓርላማ ውስጥ የተናገሩት ቃል ነው፡፡ ቃለ ምልልሱን ያከናወነው መንፈሳዊ ሚዲያ ስለዚህም ጉዳይ ጠይቋቸው ነበር፡፡ እሳቸውም በመሰጡት መልስ በተናገሩት ቃል መፀፀታቸውን አረጋግጠዋል፡፡ የመለስን ራዕይ ለማሳካት ቆርጠው መነሳታቸውን የተናገሩት ሰው የፖለቲካ ንግግራቸው ከሃይማኖታው ጋር ተጋጭቶባቸው ይቅርታ አስጠይቋዋል፡፡ የእናታቸውን አለመዳን በተመለከተ የተናገሩት ከእሳቸው እምነት ውጪ የሌላ እምነት ተከታዮች አለመዳን ጋር ተተርጉሞና ተገናዝቦ መቅረቡን በተመለከተ ይቅርታ ይጠይቁ ይሆን? 
“…. ጌታ እስከፈቀደ አሁንም ወደፊትም ያን የትላንቱን አምላክ ማምለኬ እንደ ግለሰብ ተጠብቆልኝ በአንጻሩ ደግሞ የ80 ሚሊየን ህዝብ አደራና ኃላፊነት ስላለ የሁሉንም እምነትና ሃይማኖት ማክበር ግዴታ አለብኝ” ብለዋል፡፡ ይህን ካሉ ደግሞ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ መንገድ ስለ ራሳቸው እምነት ሲያወሩ የሌሎችን እምነት መንቀፍ “አልዳኑም ማለት” ተገቢ አለመሆኑን መገንዘብ ነበረባቸው፡፡ “አልዳኑም” የተባሉት የአቶ ኃይለማርያም እናት ቢሆኑም እሳቸው የሚከተሉትን እምነት የሚከተሉ ብዙ ሚሊዮኖች አሉና ንግግሩ የጅምላና የአግቦ እንደሆነ ተደርጎ ቢታሰብ አይገርምም፡፡
እግዚአብሔርን ማገልገልና አገርን ማገልገል
የአቶ ኃ/ማርያምን ጠቅላይ ሚኒስትር መሆን ራሳቸውም ሆኑ የእሳቸው ሃይማኖት ተከታዮች ብዙ ነገሮችን መናገራቸው በየሚዲያዎቹ ተጠቅሷል፡፡ በቅርቡ በተለያዩ ሚዲያዎች እደተነበበው ከሆነ አቶ ኃለማርያም ወደ ፖለቲካው እንዲገቡ የተደረገላቸውን ጥያቄ በተመለከተ የሃይማኖት አባታቸውን አማክረው የሰጧቸው መልስ  አሁን ላሉበት ቦታ እንደመመሪያቸው  የሆነ ይመስላል፡፡ የሃይማኖት አባታቸው “እንደዚያ ብለው ጠሩህ? እንግዲያውስ ከሆነ ሂድ እግዚአብሔርን ባለስልጣን ሆኖም ማገልገል ይቻላል” እንዳሏቸው ተናግረዋል፡፡ እንደዚህ ከሆነ እንግዲህ አቶ ኃ/ማርያም ወደ ፖለቲካው የገቡት ሆነ የጠቅላይ ሚኒስትርነት ሹመታቸውን የተቀበሉት እግዚአብሔርን ለማገልገል በማለት ነው፡፡ አገርንና ህዝብን ማገልገል ደግሞ የተለየ ነው፡፡ ሁለቱንም በአንድ ጊዜ የማገልገል ፍላጎት በዘመናችን የመንግስት አመራር የታየው አክራሪነትን የሚከተሉና የእግዚአብሔርን መንግስት በምድር ላይ ለመመስረት  ከሚፈልጉ አማኞች አካባቢ  ብቻ ነው፡፡ አቶ ኃ/ማርያም ደግሞ በዚህ መስመር ውስጥ አይደሉምና ንግግራቸው የተጠና ነው ማለት አይቻልም፡፡
የመንግስትን ስልጣን አቋርጦ እግዚአብሔርን የማገልገል አዝማሚያ ከሕገ መንግስታዊ መርህዎች ጋር የሚጣረስ ብቻ ሳይሆን ሕገ መንግስታዊ እና ሪፐብሊካዊ መርህዎችን ጨርሶ የሚንድ  አዝማሚያ ይሆናል  የሚሉ ሰዎች አሉ፡፡ በቅርቡ ከፓርቲያቸው ስልጣን የተነሱት አቶ ጁነዲን ሳዶ የመንግሥት ስልጣናቸውን ተጠቅመው ሃይማኖታዊ ተልዕኮ ለማራመድ ሞክረዋል  ተብለው እንደሆነ ስናስታውስ  ስልጣንን ያለ አግባብ በመጠቀምና  ሃይማኖትን ያልሆነ ቦታ በመዶል መካከል ምን ያህል ቅርርቦሽ እንዳለ  ለመገንዘብ አያዳግትም፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ሃይማኖታዊ አስተያየቶች አድማጩን የሚያሰጉትም ለዚህ ይመስላል፡፡ ዛሬ ስለ ሃይማኖት መጠቃቀስ የጀመሩት የአገር መሪ ነገ ደግሞ  ስልጣናቸውን ተጠቅመው እግዚአብሔርን ማገልገል በሚል ሰበብ  ሃይማኖታቸውን ለማስፋፋት ምን ያዳግታቸዋል? የሚል ጥያቄ ቢነሳ  ምላሹ ምን ሊሆን እንደሚችል መገመት አያዳግትም፡፡
ኢህአዴግ የአገራችንን እምነት ነጻነት አለና የፈለገ ሰው የፈለገውን ሃይማኖት መከተል ይችላል በሚል ዲሞክራሲያዊ የመሰለ አባባል ነገሩን በቸልታ መመልከት አይገባውም ፡፡ በእርግጥ ማንም ሰው የፈለገውን እምነት የመከተል መብት አለው፡፡ ነገር ግን አንድ ሰው የመንግሥት ባለስልጣን ሆኖ ሃይማኖቱን በአደባባይ ማራመድ የሌሎችን መብት ሊጋፋ ስለሚችል ሕገ መንግስቱ የሚፈቅድለት አይሆንም፡፡
ቀጣይ ክፍል

  • የአገር መሪዎች አይነኬዎች አይደሉም…
  • መጽሀፍ ቅዱስና አብዮታዊ ዲሞክራሲ
  • የአቶ ኃለማርያም አመራረጥ ችግር
  • የመንግስትና የሃይማኖት መለያየት 

5 comments:

  1. ትዝብታችሁ መልካም ነው ፡፡ እንደምረዳው ግን ሃይማኖተኛ ናቸው መባሉ የሚጠቅመው ለስልቻነት (ለመሸፈኛ) ነው ፡፡ ምክንያቱም እንደተባለው በእርግጥ የወንጌል ቃልን ዕለት ተዕለት የሚያነቡ ፣ በየዋኀነት የሚያምኑበትና የሚጸልዩ ቢሆን ኖሮ ፣ በደልንና ኃጢአትን ስለሚፈሩ ከዚህ ቀደም ያስተዳድሩ የነበረውን የአዋሳንና አካባቢውን ሕዝብ ፣ በግፍ አያስጨፈጨፉትም ነበር ፡፡

    ስለርሳቸው ማንነትና ምንነት የሚያስረዳውን የሥልጣን እድገታቸውን ደግሞ አስቡት ፤ ከኮሌጅ መምህርነት ወደ ብሔረሰብ መሪነት ፣ ከዛም ወደ ተጠባባቂ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ፣ ዛሬ ደግሞ ለባለ ሙሉ ሥልጣን ጠቅላይ ሚኒስትርነት ደረጃ ሁሉ የበቁት በእምነት ጥንካሬአቸው ምክንያት ሳይሆን በፖለቲካ አመለካከታቸውና ለአለቆቻቸው ታማኝ አገልጋይ በመሆናቸው ነው ፡፡ በደርግ ጊዜ ኢህአፓ ነህ ተብሎ ሲመረመር አይ እኔ ክርስቲያን ነኝ ፤ ኢየሱስን በማለት ከፖለቲከኛነት ጎራ ነጻ ነው የመባል ዕድል ነበር ፡፡ ዛሬም የርሳቸው ሃይማኖተኛነት የሚነሳው ለይስሙላ የህዝብን ቀልብ ለማለዘብ ካልሆነ በስተቀር በግፍ የታሠሩትን አላስፈታም ፤ ያለፍርድ መታገትን አላስቀረም (የቃሊቲ እሥር ቤት አካባቢ የሰላማዊ ሰልፈኛ መሰብሰቢያ አደባባይ እስከሚመስል ድረስ እየተጨናነቀ ይገኛል) ፤ የንጹሃን ደም ያለፍርድ ማፍሰስን አላስቆመም (በወሎ የተፈጸመውን ግድያ ያስቡታል) ፡፡

    በአጠቃላዩ ሰው እንደ ጨርቅ ተለክቶ ይሠራ ይመስል በሥርዓቱ ልኬት ተበጅተው ቀርበውልናልና ፣ ሃይማኖተኛ ስለሆኑ አይጠጡም ፤ አይዋሹም ፤ አይበድሉም ፤ አይሠርቁም ፤ ያለፍርድ አይገድሉም ማለት ራስን ማጃጃል ነው ፡፡ ቀደም ብሎ እምነታቸው መነሳቱ ለምግባራቸው ስልቻነት እንዲያገለግል ስለሚጠቅም ፣ ግፋ ቢል ደግሞ ሌላውን ወገን ለማስኰረፍ ታስቦ ብቻ ነው ፡፡ የማነበው ወንጌል ለመበለቲቱና ለደሃ አደጉ መቆምን ፣ ለተበደሉት ፍትህ መስጠትን ነው የሚያስተምር ፡፡ የሳቸውስ ? አሁንም እግዚአብሔር በቃችሁ ይበለን ፤ ለርሳቸውም ልቦና ይስጥልንና መልካም መሪ ይሁኑልን !!!

    ReplyDelete
  2. If you don't know Jesus,and more importantly believing that he died for you, you are not Christian. What much you know about his mother? she might be physically sick or she might also worship devil, probably he used the word that his mother is not cured. Don't be cynical!

    ReplyDelete
  3. ይህ፡ድረ፡ገጽ፡የተዋህዶ፡እምነታችንን፡በሚመለከቱ፡ጉዳዮች፡ላይ፡ቢያተኩር፡ጥሩ፡ነው፡፡ለነገሩ፡እናንተስ፡ምን፡ሆናችሁ፡ነው፡ውስጥ፡ውስጡን፡አምላክን፡የሚፃረር፡ሀሳብ፡የሞላበት፡ጽሑፍ፡የምታቀርቡት፡፡በተለይ፡ያእቆብ፡የተባለው፡ሰው፡የተናገራቸውን፡ነገሮች፡በሚገባ፡መርምሯቸው፡፡ጠ/ሚኒስትሩ፡መናፍቅ፡እንደሆኑ፡ማናችንም፡እናውቃለን፡ገና፡ለገና፡እሳቸውን፡የተቃወመ፡ሁሉ፡ወዳጃችን፡ነው፡ማለት፡አይደለም፡፡በሚናገሩት፡ወይም፡በሚጽፉት፡ውስጥ፡እንክርዳድ፡እየጨመሩ፡ያሉ፡ሰዎች፡ከሚከሱት፡መናፍቅ፡ወይም፡ከሀዲ፡ሰው፡ልዩነት፡የላቸውም፡፡እናንተም፡ፈጣርያችንን፡የሚያስከፉ፡አባባሎችን፡እንደ፡ገደል፡ማሚቶ፡ባታስተጋቡ፡ጥሩ፡ነው፡፡

    ReplyDelete
  4. ato hailemariam once said, "THE POLICY OF eprdf is one and the same to my religion".These words are enough to know where the guy dwells.

    ReplyDelete
  5. Siyume Egziabher ato Hailemaryam Desalegn Vs prime minister ato Hailemaryam Desalegn! Huletegnaw yemibejen yimeslegnal...

    ReplyDelete