Wednesday, December 11, 2013

ተሐድሶን የማጽዳጽ ዘመቻ ንቅናቄ በደብረ ብርሃን



(አንድ አድርገን ታህሳስ 2 2006 ዓ.ም)፡-  ዝዋይ ፤ ናዝሬትና ፤ ደብረ ዘይት በማመስ በስተመጨረሻ ደብረ ብርሃን ላይ ሥራው የተጋለጠበት ‹‹አባ›› ማርቆስ ጉዳዩ ከአዲስ አበባ በጠቅላይ ቤተክህነት በተላኩ ሰዎች መታየቱን ከቦታው የደረሰን ማስረጃ ያመለክታል፡፡

በ1446 ዓ.ም የካቲት 2 ቀን በደብረ ብርሃን ላይ ‹‹ለማርያምና ለመስቀሉ አንሰግድም›› የሚል አባ እስጢፋኖስ የተባለ ሰው  ደቀ መዛሙርቶቹን ይዞ ትምህርቱን ሲያስፋፋ ጉዳዩ ጆሮአቸው የገባ ንጉስ ዘርዓ-ያዕቆብ ጉዳዩ የሃይማኖት በመሆኑ ለሚመለከታቸው የኃይማኖት አባቶች ሊቃውንተ ቤተክርስቲያናት በመስጠት ሁለቱ የሃይማኖት መሪዎች እንዲነጋገሩና እንዲተማኑ የተሸነፈው ለአሸናፊው እንዲገዛ ትዕዛዝ ሰጥተው መድረኩን ለቀቁ ፡፡

 ከዚያም  የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሊቃውንት ቢረቷቸውም ደቂቀ እስጢፋኖስ አንቀበልም በማለታቸው ለፍርድ ፤ ሃገሪቷም ለክብር በቅታለች፡፡ ታሪክም ታሪክን ሲደግም ዳግማዊውን ደቂቀ እስጢፋኖስ “አባ” ማርቆስ ደቀ-መዛሙርቶቹን ደቂቀ ማርቆስን በማስተባበር የምንፍቅና ትምህርቱን በለሰለሰና በጣፈጠ አንደበት እንደ አርዮስ ሲዘራ በቆየበት ዘመን አፄ ሱስንዮስ  በ15ኛው ክ/ዘመን አልፎንዙሜንዴዝ ‹‹በኢትዮጵያ ላይ ሁለት የማይነቃነቅ እሾክ ተክያለሁ›› እንዳላቸው ኤዎስጣቴዎስና ቀረንጭ  ተክለሃይማኖት እንዲሁም የዘመናችን አልፎንሜንዴዝ “አባ” ማርቆስ ያጠመቃቸውና የተከላቸው ሁለት ቀንዶች ደብሩ በደብረ ብርሃን መሃል ከተማ እያሰራ ባለው ሁለገብ ባለ 4 ፎቅ ሕንጻ ገንዘብ ያዥ ፤ በጥቅም /ሙስና/ የተሳሰረው “ኤዎስጣቴዎስ” አቻሜለህ መሰረት እና “ቀረንጭ ተክለሃይማኖት” አሻግሬ በየነን በመያዝ የምንፍቅና ትምህርቱን ሲዘራ የነበረውን ማንም አስተባባሪና ሰብሳቢ የሌለው የፀረ-ተሐድሶ ንቅናቄ ቡድን ይህን መናፍቅ እጁን ይዞ ለብጹ አቡነ ኤፍሬም አስረክቧል፡፡

ደገኛው የሃይማኖት አባትም ‹‹ይህ የሃይማኖት እንጂ የግልና ፤ የአስተዳደር ጉዳይ አይደለም›› በማለት ሲንቀሳቀሱ የነበሩትን ደቂቀ “አባ” ማርቆስን በመገሰፅ አለ የተባለውን የሃይማኖት ህፀፅ በሊቃውንቱ በማስመስከርና በማረጋገጥ ግለሰቡን ከስራና ከደመወዝ በማገድ ጉዳዮ በሊቃውንት ጉባኤ እንዲታይ ወደ ጠቅላይ ቤተ-ክህነት እንደተመራ መግለጻችን ይታወቃል፡፡ 

 እንዲሁም ይህን በተመለከተ ጉዳዩን እየተከታተልን በዝርዝር በተደጋጋሚ ማቅረባችንና ለአንባቢም የጉዳዩን መጨረሻ ተከታትለን እንድናቀርብ መጠየቃችሁ የሚታወስ ነውና የዚህ ሰሞኑን ሁኔታ ልናቀርብላችሁ ወደድን፡፡

ደቂቀ “አባ” ማርቆስ በኤዎስጣቴዎስ አቻሜለህ መሰረትና በቀረንጭ ተክለሃይማኖት  አሻግሬ በየነ መሪነት ‹‹አባ›› ማርቆስን ወደ ቀድሞ የአስተዳዳሪነት ቦታቸው ለመመለስ  ያሰባሰቡትን የሃሰት ፊርማ በመያዝ  “ሞኝ ባል ያቀፈ መስሎት ሚስቱን አንቆ ይገድላል” እንደሚባለው በ17/03/2006 ዓ.ም ‹‹አስተዳዳሪያችን ይመለሱ›› የሚል ጥያቄ አዲስ አበባ ጠቅላይ ቤተ ክህነት በመሄድ ጥያቄ አቅርበው ነበር፡፡  ጥያቄያቸውን የተቀበሉት የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አብነ ማቴዎስ እናንተ የመጣችሁት ማን ወክሏችሁ ነው?  ሀገረ ስብከቱ ነው ? ሰበካ ጉባኤውን ነው ? ወይስ ማነው ? በማለት ትክክለኛና ህጋዊ ጥያቄ የጠየቋቸው ሲሆን ደቂቀ “አባ” ማርቆስ መልስ ማጣታቸው በጊዜው ተስተውሏል፡፡ 

ጠቅላይ ቤተክህነቱ ጉዳዩ እንደደረሰው ጉዳዩን እንዲያጣሩ በ27/06/2006 ዓ.ም  ሁለት ልዑካን ወደ ሰሜን ሸዋ ሃገረ ስብከት ደብረ ብርሃን ቅድሥት ሥላሴ በመላክ  በ27/03/2006 ዓ.ም ሰበካ ጉባኤውን ፤ በ28/03/2006 ዓ.ም ጠዋት ካህናቱን ፤ ሊቃውንቱን /የብሉይና ሃዲስ ፤ የቅኔ ፤ የአቋቋም ፤ የዜማ መምህራንን/  በማወያየት ሙሉ በሙሉ “አባ” ማርቆስ ያስተማሯቸው ትምህርት የምንፍቅና ትምህርትና ከቤተክርስቲያን የሃይማኖት ትምህርት ያፈነገጠ  መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡

ለአብነትም ያህል እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የፀነሰችው በመንፈስ ቅዱስ ሆኖ ሳለመንፈስ ቅዱስ ብለው ለወልድ ስጋዊ አባት እንደ መስጠት ያለ ትምህርት መስጠታቸውንና ይህንም በሊቃውንቱ ሲጠየቁ ይህን የመሰለ ከባድ የክህደት ትምህርት እንዳስተማሩ ማመናቸውን ጨምረው ግለሰቡ “አባ” ማርቆስ መናፍቅ ተሃድሶ እንደሆኑ ያረጋገጡ ሲሆን የባህሪያቸውም የትዕቢት መንፈስ ‹‹ከቆብ በላይ ትዕቢት›› የሚል ስምም ተሰጥቷቸዋል፡፡

 በተጨማሪም  ልጆቻቸው በግለሰቡ ትምህርት የተበከሉባቸውና ወደ አዳራሽ የገቡባቸው እናቶች ከአዲስ አበባ ወደ ተላከው አጣሪ ቡድኑ በመቅረብና እንባቸውን በመርጨት ቆባቸውን በማየት ‹‹እንዲማሩልን ልጆቻችንን ወደ እርሳቸው ብንልክ ክራቸውን አስበጥሰው አስክደውብናል›› በማለት መስክረዋል፡፡ 

እንዲሁም በተመሳሳይ በግል ያስተማሯቸው “ኤልሻዳይ” የተባለውን የመናፍቃን የቴሌቪዥን ፕሮግራም እንዲከታተሉና ሃይማኖታቸውን እንዲቀይሩ ከተሰበኩትና ነገር ግን ከዳኑት ግለሰቦችም በአካል በመቅረብ ቃላቸውን ለአጣሪዎቹ ሰጥተዋል፡፡  ከሊቃውንተ ቤተ-ክርስቲያኑ ጀምሮ የተሰጠውን ምስክርነት በአጽንኦት የተከታተሉት አጣሪ ልዑካን በነገሩ በጣም አዝነው ‹‹በአፄ ሱስንዮስ ዘመን ታላላቅ አድባራትና ገዳማት ሳይቀሩ በቅባትና በፀጋ ሃይማኖት ሲበረዙ ይህ ደብር ያልተደፈረ መሆኑን በመግለጽ በዚህ ዘመን ይህ መከሰቱ በጣም የሚያሳዝን መሆኑን››ቢገልጹም ታሪክ ራሱን ይደግማልና የአባቶቻችሁን ደግማችኋል በማለት ሊቃውንቱን አመስግነው ፤ ህዝቡን በኦርቶዶክስ ሃይማኖተቸው ፀንተው እንዲኖሩ ትምህርት ሰጥተው ፤ ስለ “አባ” ማርቆስ ከጠበቅነውና ከበቂ በላይ መረጃውን የያዝን ሲሆን ለውሳኔ ለላከን ክፍል እናቀርባለን በማለት ሕዝቡንና ሊቃውንቱን ተሰናብተዋል፡፡

 የ“አባ” ማርቆስ ሁለት ቀንዶች በጥቅም የተሳሰሩ አቻሜለህ መሰረትና  ” አሻግሬ በየነ  ፤ ተከታዮቻቸውን በማስከተል ‹‹አለቃችን ይመለሱ›› የሚል የይግባኝ ጥያቄ ያቀረቡ ሲሆን ልዑካኑ እነርሱንም በአጽንኦት ከሰሙ በኋላ ‹‹አቤቱታውን ተልእኮ ለሰጠን ክፍል እናቀርባለን›› በማለት አሰናብተዋቸዋል፡፡  

እንግዲህ የእውነተኛይቷ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖት የድንግል ማርያም የአደራ ልጆች የሆናችሁ ሁሉ ለቤተክርስቲያናችን በአሁኑ ሰዓት የተነሳባትን ፈተና ሐዋርያዊ ተልዕኮዋ በተቀላጠፈ መልኩ እንዳታከናውን እንቅፋት የሆነባት የተሀድሶ ፤የሙስና ፤ የአስተዳደራዊ በደል ግብራቸውን እያቀያየሩ ለክርስቲያን የማይስማማ ሆዳቸው አምላካቸው በሆኑ ሰዎች ዙሪያዋን ተተብትባለች፡፡  ነገር ግን እንዲህ ያለው ስርዓት በዘርዓ - ያዕቆብ ሃገር በደብረ-ብርሃን ቦታ እንደሌለው ብፁዕ አብነ ኤፍሬም ያረጋገጡ ሲሆን ይህ ሁኔታ ያስደነገጣቸው “አባ” ማርቆስና ተከታዩቻቸው ‹‹ባል በላውም ጭሬ ላፍስሰው›› በሚል የተስፋ መቁረጥ ስሜት ውስጥ በመሆን የብጥብጥና የአመጽ እንቅስቃሴ ለማስነሳት ቅስቀሳ የጀመሩ ሲሆን ይህ ጉዳይ የመንግስት አካላት በጥብቅ ፤ ምዕመኑም በአጽንኦት እንዲከታተል እየጠቆምን ለብጹዕ አባታችን አቡነ ኤፍሬም እድሜና ጸጋውን እንዲሰጣቸው እንዲሁም የፀረ-ተሐድሶ አራማጆችን ያለምንም ሰብሳቢና ቀስቃሽ የሚንቀሳቀሱትን በጸሎታችሁ እንድናባቸው እያልን “አባ”ማርቆስንም ሆኑ እያወቁትም ሆነ ሳያውቁት እየወገኑ ያሉትን ደቂቀ “አባ” ማርቆስ ግለሰቦች ለንስሐ እንዲያበቃቸውና ወደ ተዋህዶ ሃይማኖታቸውና ወደ ቅድስት ቤተክርስቲያናቸው እንዲመልሳቸው የሁላችሁ ጸሎት አይለይ እያልን በቅርቡ የድምጽና የምስል ማስረጃዎችን የምናቀርብ መሆናችንን እንገልጻለን፡፡

1 comment:

  1. የአባቶቻችን አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ለእናቱ ለድንግል ማርያም የሰጣትን ቅድስት ሀገር ኢትዮዽያንና ቤተክርስቲያናችንን ይጠብቅልን። አሜን

    ReplyDelete