Sunday, December 16, 2012

ቅዱስ ሲኖዶስ ተመራጩ ፓትርያርክ ኢትዮጵያዊ ዜጋ ብቻ እንዲሆን ወሰነ




አዲስ አድማስ ጋዜጣ እንዳገኝነው

  • ዜግነትን መቀየር ለትውልድ ካለው አርአያነት አንጻር ከአንድ በላይ ዜግነት ያላቸው ጳጳሳት በምርጫው አይካተቱም፡፡
  • መንፈሳዊ እና ማኅበራዊ አገልግሎትን በመፈጸም በቂ ችሎታና ልምድ ከማካበት አንጻር የገዳም መነኩሴ የሚለው እንዲወጣ ተደርጓል

(አንድ አድርገን ታህሳስ 8 2005 ዓ.ም)፡- በፓትርያርክ ምርጫ ሕግ ረቂቅ ላይ ውይይት እያካሄደ የሚገኝው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የተመራጩ ፓትርያርክ ዜግነት ኢትዮጵያዊ ብቻ መኾን እንደሚገባው ወሰነ፡፡

ተመራጩ ፓትርያርክ ሥርዓተ ቤተክርስቲያንን ጠንቅቆ ያወቀ ፤ በትምህርተ ሃይማኖት በቂ ችሎታ ያለውና  በግብረ ገብነቱ የተመሰገነ ፤ በትውልዱም ሆነ በዜግነቱ የውጭ ዜጋ ያልሆነ ለፓትርያርክነት የተቀመጠውን መመዘኛ መሰረት በዕጩነት  ለመቅረብ የሚችበት ዕድል እንዳለ በሲኖዶሱ  መጤኑን የስብሰባው ምንጮች ተናግረዋል፡፡  በትውልዳቸው ኢትዮጵያዊው ኾነው የውጭ ሀገር ዜግነት ያላቸው በቁጥር በአራት ያላነሱ ጳጳሳት እንዳሉ ተጠቁሟል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ የምርጫ ሕግ ረቂቁን መጽደቅ ተከትሎ በሲኖዶሱ እንደሚቋቋም በሚጠበቀው አስመራጭ ኮሚቴ አማካኝነት ይካሄዳል የተባለውን የፓትርያርክ ምርጫ በዕጩነት ሊቀርቡ የሚችሉ አባቶች በዜግነት መመዘኛው ምክንያት ከውድድር ውጪ መኾናቸው ያላስደሰታቸው ወገኖች መስፈርቱን ተቃውመውታል፡፡ ተቀዋሚዎቹ   ቤተክርስቲያን   ሰዎች በክርስቲያናዊ እምነትና ሥነ ምግባር እንጂ በዜግነት  የማይለዩባት ዓለም አቀፋዊት መኾኗን በመጥቀስ ይከራከራሉ፡፡ የአንቀጹን መካተት የሚደግፉት ደግሞ  የኢትዮጵያዊነትን መንፈሳዊ እሴት ፤ ኦርቶዶክሳዊነት ከኢትዮጵያዊነት ጋር ያለውን ታሪካዊና ትውፊታዊ ቁርኝት ፤ በሃይማኖት አባትነት ከራስ ምቾትና ፍላጎት አኳያ ዜግነትን መቀየር ለትውልድ ያለውን አርኣያነት በመጥቀስ ለክርክሩ ምላሽ ይሰጣሉ፡፡

ታኅሣሥ አንድ የተጀመረውና የቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ በጥቅምት ወር በተቋቋመው የፓትርያርክ ምርጫ  ሕግ አርቃቂ  ኮሚቴ ተዘጋጅቶ በቀረበለትና 15 አንቀጾች ባሉት ረቂቅ ላይ መወያየቱን ቀጥሏል፡፡ በአሁኑ ሰዓት 12 ያህል አንቀፆችን ማጽደቁንም ለማወቅ ተችሏል ፤ በምልአተ ጉባኤው ከፍተኛ ክርክር ተደርጎባቸው ከጸደቁ የምርጫ ሕግ ረቂቁ  አንቀጾች  መካከል የፓትያርክ ስያሜ ፤ ምርጫ ወይም እጣ ፤ እንደ ስርዓት የሚካተትበት ኹኔታ አንዱ እንደነበር ተነግሯል፡፡

በረቂቁ መሰረት ከሰባት ያልበለጡ ከሶስት ያላነሱ ዕጩዎች 19 አባላት ባሉት አስመራጭ ኮሚቴው አማካኝነት ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤው ይቀርባሉ፡፡  የመጨረሻዎቹ እጩዎች በምልአተ ጉባኤው ከተለዩ በኋላ በሲኖዶስ አባላት ፤ ከጠቅላይ ቤተክህነት ጀምሮ በየደረጃው በሚገኙ  ኃላፊዎች ፤ በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጪ አህጉረ ስብከት በተወከሉ የገዳማት አበምኔቶችና እመምኔቶች ፤ የካህናት ፤ ሰንበት ትምህርት ቤት ፤ ምዕመናንና ዕውቅና በተሰጣቸው መንፈሳውያን ማኅበራት ተወካዮች አማካኝነት በሚስጥር በሚሰጠው ድምጽ ከፍተኛ ድጋፍ ያገኝው ዕጩ ለፓትርያርክነት ይበቃል፡፡ በሲኖዶስ ውሳኔ መሰረት ምርጫ ዋነኛው ሥርዓት ሆኖ የተወሰደ ሲሆን ከእጩዎቹ መካከል እኩል ድምጽ ያገኙ ቢኖሩ በእጣ የሚለዩበትና ተመራጩ ፓትርያርክ የሚታወቅበት አሠራር እንደሚኖር ተገልጧል፡፡

በቤተክርስትያን የስርዓት መጽሐፍ መሠረት ለፕትርክና በዕጩነት የሚቀርበው ጳጳስ ዕድሜ 50 ዓመትና ከዚያ በላይ መሆን ስለሚገባው በረቂቁ የቀረበው የ45 ዓመት መነሻ መለወጡ ተመልክቷል፡፡  በሕጉ ረቂቅ የገዳም መነኩሴን ጨምሮ ኤጲስ ቆጶስ ፤ ጳጳስና ሊቀ ጳጳስ በእጩነት መቅረብ እንደሚችሉ ተገልጦ የነበረ ቢሆንም  መንፈሳዊ እና ማኅበራዊ አገልግሎትን በመፈጸም በቂ ችሎታና ልምድ ከማካበት አንጻር የገዳም መነኩሴ የሚለው እንዲወጣ መደረጉ ሂደቱ ተከታታዮች አነጋግሯል፡፡ በሰሜን አሜሪካ የስደት ሲኖዶስ ካቋቋሙ ጳጳሳት ጋር ከኅዳር 26 -30 ቀን 2005 ዓ.ም በዳላስ ቴክሳስ የተካሄደው ውይይት ተስፋ ሰጪ የሰላምና አንድነት ፍላጎት በታየበት መልክ መካሄዱ በተነገረበት ወቅት ቅዱስ ሲኖዶስ በፓትርያርክ ምርጫ ሕገ ደንብ ላይ የሚያካሂደው ውይይት  የበለጠ ጊዜ እንዲሰጠውና ትዕግስት እንዲደረግበት አስተያየታቸውን የሰጡ የጠቅላይ ቤተክህነት አካላት ጠይቀዋል፡፡  

4 comments:

  1. Addis Patiryarik Lemeretsi New ? Yihun Gin Menifes Kidus Bigebabet Melkam New Edimena Kanika Bicha Beki Ayidelem Kezereginet -Kepoletika Yetseda Bihon Managimentun Lela Akal Biseyemibet Melkam New Abune Merikorewosina Abune Pawilos Yasayunin Sayihon Yeteshale neger Yemiseru

    ReplyDelete
  2. Very good decision. I think anyone who switched nationality has already given up his firstborn blessings and should not qualify even for bishop. It shows a complete absence of Menfesawinet for a clergyman to give up his Ethiopiawinet. It shows that the mysteries of Menfes Kidus weren't revealed to this person in the first place. I think we are living in very strange times to have to witness bishops giving up Ethiopiawinet and seeking other citizenship for the purpose of material gains.

    ReplyDelete
  3. Ere Egziabher yesetenen Yandenet edel endayteb hulachenem betselot enberta
    Lela ketat endaymta metenkek asflagie new.

    ReplyDelete
  4. ይህ መንግስት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን መጥፊያዋን እያዘጋጀ ያለ ይመስላል። የግዚኣብህእርን ፍጡራን በመወለዱ በመከፋፈል ኣንተ በቂ ነህ ኣንተ በቂ ኣይደለህም በማለት ቤተክርስቲያኒቱን ከግዚኣብሄር ጋር ለማጣላት የሚደረግ ነውና ይህንን ህግ የሚያወጣ ሲኖዶስን የሃይማኖት መሪዬ ኣይደለም።

    ReplyDelete