Thursday, May 29, 2014

የቅዱስ ሲኖዶስ “ሰብኣዊ ገጽ”


በታደሰ ወርቁ ተጻፈ
(አንድ አድርገን ግንቦት 21 2006 ዓ.ም)፡- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በኦሪት የታዘዘውን ፤ በወንጌል የተፈጸመውን መሠረታዊና አማናዊ ሕግ በተገቢው መልኩ ስትፈጽም ቆይታለች፡፡ በዚህ አግባብም ካህናቷንና ምዕመኗን  ለዘመናት ስታስተዳድር ቆይታለች፡፡ዐይነተኛ አገልግሎቷም እስከ ዘመናችን ድረስ ጉልህ ሆኖ ይታያል፡፡

ቤተ ክርስቲያኒቱ በየጊዜው የደረሰባት መስክ ወለድ ትግልና ድካም አሸንፋ ፤ መንፈሳዊ አገልግሎቷ እስከ ጽንፍ ኢትዮጵያ እና ዓለም ዳርቻ ሲሰማና ሲነገር ፤ ሲመለክና ሲከበር የኖረው ሰብኣዊ ገጻቸውን በሃይማኖት ገጽ ልዕልና ባሸነፉ አባቶቿ ነጻ ፤ ጠንካራ እና ቆራጥ አመራር ነው፡፡የቤተ ክርስቲያኒቱ ዐይናማ ሊቃውንት ሰብኣዊ ገጻቸውን በመንፈስና በሞራል ልዕልና ገርተው ለአንድ ሺህ ስድስት መቶ ዓመታት ቤተ ክርስቲያቱን ተጭኗት የነበረውን የግብጻውያንን ቀንበር በማወገድ “ለአንዲት ነጻ አገር አንድ ፓርላማ እንዳላት ሁሉ ለአንዲት ነጻ ቤተ ክርስቲያን አንድ ቅዱስ ሲኖዶስ ብቻ” በሚል የራሷ ቅዱስ ሲኖዶስ እንዲኖራት አስችለዋታል፡፡


በዚህ የሃምሳ ዓመታት የቅዱስ ሲኖዶስ ታሪክ ውስጥ ቢያንስ ቢያንስ የምልዓተ ጉባኤውን መንፈሳዊ እና አስተዳደራዊ ልዕልና በጉልህ የሚያስረግጡ ድርጊቶችን መኖራቸው ድርስ ነው፡፡ በዚህ የታሪክ ሂደት ውስጥ ቅዱስ ሲኖዶስ ታሪካዊ ባላደራነቱን ፈትነው የጣሉት ኹነቶች አልነበሩም  ማለት ግን አይደለም፡፡ እርሱንም ቢሆን ተሻግረው ቤተ ክርስቲያቱን ከነሙሉ ክብሯ አዚህ ዘመን አድርሰዋታል፡፡ያም  ሆነ ይህ ግን የችግሩ ሰበዝ እንደዘመናችን አንዳንድ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት የመንፈሳዊ ሕይወት ባዳነትና  የሕሊና ራቁትነት እንዳልሆነ በደምሳሳው እርግጠኛ መሆን ይቻላል፡፡ ይህ አጉል ድፍረትም ንቀትም አይደለም፡፡ ሆኖ ያየሁት ይህንኑ ነው፡፡
በእኛ አገር በቅርቡ ወይም አዲሱን ታሪክ ከመጠን በላይ አግዝፎ ለማቅረብ የቀደመው ማሳነስ የተለመደ ስለሆነ “እበላ ባይ ጸሐፊዎች” ምንኛ የታሪክ ምዝገባ ሓላፊነታቸውን እንዳልተወጡ የአምስተኛው ዘመነ ፕትርክና ድርሳናት ያገላበጠ ሁሉ ያውቀዋል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የአንዳንድ ጥቡዓነ ልብ-አበው አስተዋጽኦ የቤተ ክርስቲያኒቱን ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ገድል እንዳይሸፍነው እየተባለ ታሪካቸው ለትውልድ ሲነፈግ ቆይቷል፡፡ በዚህም  የተነሣ የርእሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ ታሪክ ጸሐፊዎች ሰብኣዊ ገጻቸው አይሎባቸው ፤ በሰብኣዊ ገጽ ስሌት ከሥር ሆነው ታሪክ የሠሩትን አባቶች ታሪክ ለትውልድ ሳያስተዋውቁ  ቀርተዋል፡፡ በዚህ ምክንያት የትውልዱም ንጽጽራዊ እይታው  እንዲጠብ የሆነ ይመስለናል፡፡

ስለዚህ በአሁኑ ዘመን ታሪክ ጸሐፊዎች ትከሻ ላይ የተጫነው ሸክም ስንዴውን ከግርዱ የመለየትና እስከ አሁን የጎደለንን ሁሉ የማቅረብ ሓላፊነት ነው፡፡ ይልቁንም ስለ ቅዱስ ሲኖዶስ ታሪክ በሚገባ የምናውቀው ነገር የለም፡፡ ማን ፤  እንዴትና በምን  አግባብ እንደተሾመ በየትኛው ሲኖዶስ ? በየትኛው ጉዳይ  በምን ሁኔታ እንደተወሰነ የምናውቅበት መንገድ የለም ፤ ይኼ ጉድለታችን ነው፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስ መንፈሳዊና አስተዳደራዊ ልዕልና ቀጣይነትና ተከታታይነት ባጣበት ፤ ዐይናችንን የአበው ረሃብ በሚሰቃይበት በዚህ ዘመን ሁሉ አቀፍ ታሪኮች ያስፈልጉናል፡፡ አለበለዚያ ግን የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ሰብዓዊ ገጽ እያየለ ሔዶ ሲኖዶሳዊ ይዘቱንና ቅርጹን እንዳያሳጣን ያሰጋል፡፡ አሁን እየሆነ ያለው ይኼው ነው፡፡

በዚህ ዘመንም ቤተ ክርስቲያቱ የሚሞቱላትን ብጹዓን አበው አጥታ እደማታውቅ ሁሉ የሚያዋርዷትንም ተቸግራ አታውቅም፡፡ የቤተ ክርስቲያናቸውን ክብርና ልዕልና ላለማስነካት ሲሉ በሰማዕትነት ፤ በክብር ለመውደቅ የተዘጋጁ እጅግ ጥቂት አባቶች የመኖራቸውን ያህል ከአባቶቻችን መካከል “የምሞትላትና የምታገልላት ቤተክርስቲያን የለችኝም” ለማለት የዳዱም አልጠፉም፡፡አሁን ግን እንደ ቀደሙት ዘመነ አበው ለቤተ ክርስቲያኒቱ ክብርና ልዕልና የሚታገሉ አባቶች መኖራቸውን ሳላስረግጥ አላልፍም፡፡ 

ምእመኑ ለሚቀጥለው ትውልድና ስለ ነገይቱ ቤተ ክርስቲያን ህልውና ሲጨነቅ አንዳንዶቹ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ዛሬ ሊያገኙ ስለሚጓጉት ተጨማሪ ሹመት ፤ ቤት ፤ መኪና እንቅልፍ ትተው ይጨነቃሉ፡፡ እንዲህ አይቱ ሰብኣዊ ገጻቸው ወደ ማኅበራዊ ትምክተኝነት እንዲዘቅጡ ከማድጉ በተጨማሪ ምጣኔ ሀብታዊ ቅርምት ውስጥ ሊከታቸው ይችላል፡፡ውጤቱ ደግሞ ለቤተ ክርስቲኒቱ መተረማመስ አስተዋጽኦ ያደረጉ የጥፋት ኃይሎች በእነርሱ ትከሻ ላይ ታዝለው እንዲመጡ ረድቷቸዋል፡፡ የሚያስጨንቀውም የእነርሱ መምጣት ሳይሆን የአባቶቻን ሰብኣዊ ገጻቸው አይሎ የተውኔቱ አባላት መሆናቸው ነው፡፡

በዚህ መልኩ በሩ የተከፈተላቸው አተራማሽ ኃይለ ግብር ቁስላችንን ዘወትር እያሰፉት ይገኛሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያቱን ከኦርቶዶክሳዊት መዳፍ ውስጥ ፈልቅቀው በማውጣት እና ዘላለም በሰማዕታትነት ከአከበሯት አባቶች ብብት ውስጥ በመስረቅ አይሆኑ ሆና እንድትኖር ግዴታ እየጣሉባት ነው፡፡ በዚህ ሁሉ ግን የሚደንቀው እነዚህ ሰዎች ሌላ መሠረተ እምነት የለንም የሚሉ ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ለሚሏት ቤተ ክርስቲያን ጥቅም አልቆሙም፡፡ ኦርቶዶክሳዊያን ናቸው ተብለው እንዲገመቱ መስለው በመገኝት ታማኝነታቸውና አገልጋይነታቸው ግን ለሌሎች ነው፡፡

ይህ ሲሆን ግን የአንዳንድ አባቶች ከለላ ሰጪነት ይህቺ ቤተ ክርስቲያን ጨርሶ ወደማጥፋት ፤ ወደ ውድመት የመሄዷ ማስረጃ አይደለምን ? እንዲህ አይነቱን የኋላ ሩጫ ከጀመርነው ይኽው ሃያ ሁለኛ ዓመት ጀምረነዋል፡፡ ሆኖም ግን የሰማዕታቱ ቤት ፤ የነጻዎቹ ሊቃውንት ቤተ ክርስቲያን እስከ አሁን ፈርሳ አላበቃችም፡፡ በእርግጥ ግን ተዋርዳለች፡፡ ውርደቷም በእርሷ ስም ያሉት መሪዎቿ  መዋረድ ነው፡፡ እነርሱ ምንም ይሁኑ ምን ፍርዱን ከእግዚአብሔር የሚያገኙት ሲሆን የሚያሳዝነው ግን ለቤተ ክርስቲያኒቱ ክብር መጣኝ ባልሆኑ ድርጊቶቻቸው  በሌላው አለም ፊት ተዋርደው የኛኑ ቤተ ክርስቲያን ማዋረዳቸው ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ ከእነርሱ መኖሪያ ቤት ክብር በታች ስትታይ ምእመኑ ምን ይሰማዋል? የቆራጦቹ ሰማዕታት ቤት ፤ የነጻዎቹ ሊቃውንት ቤት ተዋረደች አያሰኝም?

በሌላ በኩል ደግሞ ቤተ ክርስያቱንና ገበናዋን ለሌላው በመክፈታቸው ፤ ጠንካራውን ኦርቶዶክሳዊ ኩራትና ክብርን በማዳከማቸው የሚታሙት የቀድሞ ቅዱስነታቸውም ቢሆኑም ዳሩ ግን ሒሳቡን ስታሰሉት የእኛው ፓትርያርክ ከአተራማሹ ኃይለ ግብር ከሚያገኙት ጥቅም ይልቅ ለዚህ አተራማሽ ኃይለ ግብር የሚያበረክቱት አገልግሎት ልቆ እናገኝዋለን፡፡ በእርግጥ ነገሩ ሁሉ የተበላሽው አሁን አይደለም፡፡ ሢመተ ጵጵስናው ክብር ሲያጣ ፤ የምልመላው መስፈርት ቦታ ሲያጣና በሕጉ መሠረትያለ ምእመናን ይሁንታ ሲታደል ነው፡፡

እናም በመንፈስ ቅዱስ የሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ ፤ የመንበረ ሐዋርያት ወራሽ የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ ፤ ከማንኛውም የቤተክርስያቱ የሥልጣን መዋቅር ሁሉ የበላይ የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ  ፤ በእንደዚህ አይነት ሰብኣዊ ገጽ መታጀሉ እጅግ ያሳዝናል፡፡ ለእኔ የቅዱስ ሲኖዶስ ገጽ ይኼ ነው፡፡ ለእኔ አሁንም ሰብአዊ ገጹ አይሏል፡፡ መንፈሳዊ ገጹ ኮስምኗል፡፡

የዘወትር ምኞቴም ሆነ መሻቴ እንደ ዘውድ የተቆጠረው ቆብ ተገቢው ቦታና ሰው እንዲያገኝ ነው፡፡ የዘወትር ህልሜ እውነት ሸባቢው “ዘውድ” ወልቆ እውነት አናጋሪው ዘውድ እንዲጫን ነው፡፡ ይህም እውን የሚሆነው የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ሰብኣዊ ገጽ ወደ መንፈሳዊ ገጽ ሲለወጥ ነውና ይህንንም እናፍቃለሁ፡፡
  

8 comments:

  1. የዘወትር ምኞቴም ሆነ መሻቴ እንደ ዘውድ የተቆጠረው ቆብ ተገቢው ቦታና ሰው እንዲያገኝ ነው፡፡ የዘወትር ህልሜ እውነት ሸባቢው “ዘውድ” ወልቆ እውነት አናጋሪው ዘውድ እንዲጫን ነው፡፡ ይህም እውን የሚሆነው የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ሰብኣዊ ገጽ ወደ መንፈሳዊ ገጽ ሲለወጥ ነውና ይህንንም እናፍቃለሁ፡፡

    ReplyDelete
  2. የባሰ አታምጣ

    ReplyDelete
  3. የዘወትር ምኞቴም ሆነ መሻቴ እንደ ዘውድ የተቆጠረው ቆብ ተገቢው ቦታና ሰው እንዲያገኝ ነው፡፡ የዘወትር ህልሜ እውነት ሸባቢው “ዘውድ” ወልቆ እውነት አናጋሪው ዘውድ እንዲጫን ነው፡፡ ይህም እውን የሚሆነው የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ሰብኣዊ ገጽ ወደ መንፈሳዊ ገጽ ሲለወጥ ነውና ይህንንም እናፍቃለሁ፡

    ReplyDelete
  4. የዘወትር ምኞቴም ሆነ መሻቴ እንደ ዘውድ የተቆጠረው ቆብ ተገቢው ቦታና ሰው እንዲያገኝ ነው፡፡ የዘወትር ህልሜ እውነት ሸባቢው “ዘውድ” ወልቆ እውነት አናጋሪው ዘውድ እንዲጫን ነው፡፡ ይህም እውን የሚሆነው የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ሰብኣዊ ገጽ ወደ መንፈሳዊ ገጽ ሲለወጥ ነውና ይህንንም እናፍቃለሁ፡፡

    ReplyDelete
  5. yasaznal eskemeche betekrstian tebezebezalech?!!

    ReplyDelete
  6. እውነት ብለሀል ወዳጃ !!! የብዙወች ምኞት ያንተ ምኞት ቢሆንም ብፁዐን አባቶችና የቤተ-ክህነት አባቶች ይህንን አልተገነዘቡም፡፡ ቤተክርስቲያን የኃሊት ጉዞ ላይ መሆኗን አልተረዱም፡፡ እኔ እንጃ ምን ዓይነት ድብርት ውስጥ እንደገቡ፡፡ እንደ ኦርቶዶክሳዊነት የሚያኮራ እምነት የምንመካበት አምላክ ይዘን እውነተኛ ኖላዊ ግን ከወደት እናግኝ??……..እኔ እንዚህ ዘመን ስለቤተ-ክርስቲያኔ ሁለንተናዊ ክብርና ልዕልና ጨንቆኝ አያውቅም፡፡ ወደትስ አቤት ይባላላ??? ወደ ቤተ-ክህነት???? ‘’ሌባው እያፋለገ በሬው ከወደት ይገኛል??’’ ነው ያለው ያገሬ ሰው፡፡ መመኪያችን እርሱ እግዚአብሔር ይርዳን እንጂ፡፡

    ReplyDelete
  7. እዉነት ብለሃል በሰዉ መንፈስ የተቃኘ ሳይሆን በመንፈስ ቅዱስ የተቃኘ ያስፈልገናል፡፡

    ReplyDelete
  8. የዘወትር ምኞቴም ሆነ መሻቴ እንደ ዘውድ የተቆጠረው ቆብ ተገቢው ቦታና ሰው እንዲያገኝ ነው፡፡ የዘወትር ህልሜ እውነት ሸባቢው “ዘውድ” ወልቆ እውነት አናጋሪው ዘውድ እንዲጫን ነው፡፡ ይህም እውን የሚሆነው የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ሰብኣዊ ገጽ ወደ መንፈሳዊ ገጽ ሲለወጥ ነውና ይህንንም እናፍቃለሁ፡፡

    ReplyDelete