Friday, September 6, 2013

ሟችም ከመሞቱ በፊት ይህን ሲል ነበር




 

(አንድ አድርገን ጳግሜ 1 2005 ዓ.ም)፡- ሰሞኑን የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ባዘጋጁትና ‹‹አገር አቀፍ የሰላም እሴት ማጎልበቻ ጉባኤ›› ከነሀሴ 21 እስከ 24 2005 ዓ.ም በአፍሪካ ሕብረት መሰብሰቢያ አዳራሽ ማዘጋጀታቸው ይታወቃል፡፡ በዚህም ጉባኤ ከተለያዩ የእምነት ተቋማት እና ከፍተኛ የሚባሉ የመንግሥት ባለስልጣናት ተገኝተውበታል፡፡ በጉባኤው መክፈቻ ስነስርዓት ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት ጀምሮ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የቀጥታ ሽፋን ማግኝት ችሎ ነበር ፤ በጉባኤው ላይ የተጋበዙት እንግዶችና ከሃይማኖታዊ ሁኔታዎች ጋር ቀጥተኛ ተያያዥነት ያላቸው ጉባኤተኞች ከአምስት ያላነሰ ጥናቶች ላይ እንደሚወያዩ መርሀ ግብሩን ከሚመሩት ሰዎች ምልከታ ተሰጥቶ ነበር፡፡ በመጀመሪያ ንግግር እንዲያደርጉ የተፈቀደላቸው ሁለት አባቶች ውስጥ አንዱ ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያት ነበሩ፡፡ እርሳቸውም በትምህርተ መስቀል ካማተቡ በኋላ ያዘጋጇትን ሶስት ወረቀት ለታዳሚው በንባብ አቅርበዋል፡፡ ቅዱስነታቸው ለታዳሚያን ያቀረቡት የጽሁፍ ንግግር ፌደራል ጉዳዮች እንዳሰበው መንግሥት እንደሚለፈልፈው ከአሸባሪነት ጋር በቀጥታ የተያያዘ አልነበረም ፤ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖት ወክለው ንግግር ሲያደርጉ ባለስልጣናቱ አሁን ይታያል የተባለውን አሸባሪነት ለፖለቲካ ገብአት ይሆናቸው ዘንድ እንዲያወግዙላቸው ነበር፡፡ በዚህም መንግሥት ቅር ሳይሰኝ እንደማይቀር አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች ሲናገሩ ተሰምቷል፡፡ ኢቲቪም ንግግራቸውን በመቆራረጥ በጣም አጭሩን ክፍል ብቻ በመውሰድ ለዜና ግብአት ሲጠቀምበት ተስተውሏል፤ ቅዱስነታቸው የንግግሩን ስረ መሰረት ከአሸባሪ ጋር ቢያያይዙት ኖሮ ሙሉ ንግግራቸው ከዜና በኋላ በተላለፈ ነበር ፤ ነገር ግን ይህ ሲሆን አልተስተዋለም ፤ ቅዱስነታቸው አሁን ያለው ችግር በሆደ ሰፊነት በጥንቃቄ እንደሚፈታ ሃሳባቸውን አቅርበዋል፡፡  በዚህም ንግግራቸው አቦይ ስብሀት አይናቸውን አተኩረው ቀልባቸውን ሰብስበው ሲያደምጧቸው እንደነበር ከቴሌቪዥን መስኮቱ ላይ ለመመልከት ተችሏል ፤ቅዱስነታቸው ያቀረቡት ንግግር በጠቅላላ ማለት ይቻላል ከ‹‹ሰላም›› አስፈላጊነት ጋር የተያየዘ እና ቤተክርስቲያን በወቅታዊ ሁኔታው ያላትን አቋም የሚያንጸባርቅ ሆኖ ታይቷል ፡፡ ከቅዱስነታቸው ውጪ ንግግር እንዲያቀርቡ የተጋበዙ የእስልምና እምነት ተወካይ ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃ/ማርያም ደሳለኝ ፤ እና የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር በጠቅላላ ንግግራቸው ሁሉ ‹‹አሸባሪ›› ፤ ‹‹አሸባሪ›› ፤ ‹‹አሸባሪ›› ከማለት በተጨማሪ ሕገ- መንግሥቱ ለእምነቶች ነጻነት ሰጥቷል የተባለውን አንቀጽ ደጋግመው ሲያነሱም ነበር ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አያይዘው ከእነዚህ ጸረ ሰላም ኃይሎች ጋር አብሮ የሚሰሩ አንዳንድ የፖለቲካ ፓርቲዎችንም ጠንከር ያለ ማስጠንቀቂያ አዘል መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለውም በክርስትና አካባቢ ያለውን አክራሪነት የእምነት ተቋማት ለማክሸፍ ከመንግሥት ጋር ሲሰሩ ለነበሩ አባቶች ምስጋና አቅርበዋል፡፡

 

በክርስትና ስም ፌደራል ጉዳዮች እውቅና ከሰጣቸው ከ178 የእምነት አይነቶች ውስጥ የትኞቹ እንደሆኑ በንግግራቸው ላይ አልተንጸባረቀም፡፡ ነገር ግን የቀድሞ ሟች ጠቅላይ ሚኒስትር ሚያዚያ 9/2004 ዓ.ም ለተወካዮች ምክር ቤት ሪፖርት ሲያቀርቡ በሰፊው ወሀቢዝምን ፤ ሰለፊንና መሰል በእስልምና እምነት ውስጥ ያለውን የአንዳንድ አክራሪዎችን አካሄድ ከነባራዊ የሀገሮች ሁኔታ ጋር ካቀረቡ በኋላ ‹‹ቅዳሴው ቢያልቅበት ቀርቶ ሞላበት›› እንደሚለው የሀገሬ ሰው ሃይማኖትን በመጠበቅ ትውፊትን በማቆየት ሊመሰገን የሚገባውን ‹‹ማኅበረ ቅዱሳን››ን  ስም ጠቅሰው ከእነዚህ በግርብር ከማይመሳሰሉት ጋር ለማመሳሰልና ያደረጉት ንግግር ዛሬ ደግሞ ስም ሳይጠቅሱ አቶ ኃ/ማርያም በደብዛዛው ጠቅሰውት አልፈዋል፡፡

 

መንግሥት አሁንም ከማኅበሩ ጭንቅላት ላይ የወረደ አይመስልም ፤ ሟች ጠቅላይ ሚኒስትር የተናገሩትን ሌጋሲ እንዲያስቀጥሉ የሙሴ በትር የተሰጣቸው ቋሚው ጠቅላይ ሚኒስትር ደግሞ ስሙን ለመጥቀስም ሲዳዳቸው ተስተውሏል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር ደረጃ ባይጠቀስም በሚኒስትር ደረጃ እና አንዳንድ የውስጥ ባንዳዎች የማኅበሩን ስም ለማጥፋት ስብሰባዋን እንደ መልካም አጋጣሚ የወሰዷት ሰዎች በሆነው ባልሆነው ከሳሽ ባልተጋበዘበት ስሙን ሲያወርዱ ሲያወጡ እንደዋሉ አንዳንድ የጉባኤ ተካፋዮች ተናግረዋል፡፡

 

 

ሟች ለፓርላማ ስለ አሸባሪነት ትንተና ከሰጡ በኋላ አድማጪዎቻቸው ያገኟቸው ከሶስት ወር በኋላ ከቅድሥት ሥላሴ ቤተክርስቲያን የመጨረሻው የሽኝት ስነ ስርዓት ላይ ነበር ፤ ስለዚህ አሁንም እየተባለ ያለው ከሳሽ የሚቆፍረው ጉድጓድ በፊት የነበረ ወደፊትም የሚቀጥል መሆኑን ብዙዎች ይስማማሉ ፤ ስለዚህ እድሜ ትምህርት ያልሆናቸው አቦይ ስብሃት ስለዚች ቤተክርስቲያን እና በውስጧ ስላቀፈቻቸው አገልጋይ ማኅበራት መናገር የሚያቆሙት ፤ ስለ አገልጋይ አባቶች መክሰስ እና መሳደብ የሚተውት የቀድሞውን ወዳጃቸውን መንገድ ሲከተሉ ብቻ ነው፡፡ ዛሬ የሚሰማው ክስ ትንሽ የበረደ ይምሰል እንጂ ከዓመት በፊት ሰፊ መነጋገሪያ ሃሳብ እንደነበረ የሚዘነጋ አይደለም ፤ ጠላት ሁሌም ጠላት ነው ፡፡ ዛሬም ነገም ከነገ ወዲያም ጉድጓዶች ሊቆፈሩ ይችሉ ይሆናል ፤ የተቆፈረው ጉድጓድ ውስጥ ላለመግባት ማስተዋልና ጥበብ ያስፈልጋል፡፡ ሟችም ከመሞቱ በፊት ይህን ሲል ነበር፡፡

 

‹‹መባልን ሳይሆን መሆንን ፍራ››

4 comments:

  1. ልክ ነው !!!!ከዝች ቤ/ክ አይናቸውን ካላነሡ ሁሉም በተራ ይጠራል ፡፡፡፡ደግሞ ሢሞቱም ያው ቤ/ክ ነው የሚገቡት

    ReplyDelete
  2. ሟችም ከመሞቱ በፊት ይህን ሲል ነበር

    ReplyDelete
  3. ሟች ለፓርላማ ስለ አሸባሪነት ትንተና ከሰጡ በኋላ አድማጪዎቻቸው ያገኟቸው ከሶስት ወር በኋላ ከቅድሥት ሥላሴ ቤተክርስቲያን የመጨረሻው የሽኝት ስነ ስርዓት ላይ ነበር ፤ ስለዚህ አሁንም እየተባለ ያለው ከሳሽ የሚቆፍረው ጉድጓድ በፊት የነበረ ወደፊትም የሚቀጥል መሆኑን ብዙዎች ይስማማሉ ፤ ስለዚህ እድሜ ትምህርት ያልሆናቸው አቦይ ስብሃት ስለዚች ቤተክርስቲያን እና በውስጧ ስላቀፈቻቸው አገልጋይ ማኅበራት መናገር የሚያቆሙት ፤ ስለ አገልጋይ አባቶች መክሰስ እና መሳደብ የሚተውት የቀድሞውን ወዳጃቸውን መንገድ ሲከተሉ ብቻ ነው፡፡ ዛሬ የሚሰማው ክስ ትንሽ የበረደ ይምሰል እንጂ ከዓመት በፊት ሰፊ መነጋገሪያ ሃሳብ እንደነበረ የሚዘነጋ አይደለም ፤ ጠላት ሁሌም ጠላት ነው ፡፡ ዛሬም ነገም ከነገ ወዲያም ጉድጓዶች ሊቆፈሩ ይችሉ ይሆናል ፤ የተቆፈረው ጉድጓድ ውስጥ ላለመግባት ማስተዋልና ጥበብ ያስፈልጋል፡፡

    ReplyDelete
  4. did u forget? who you are? You are human. So you are mortal.
    As you try to give response for the discussion, pleas try to preach gospel. Truth is always truth. don't confuse our nation.

    ReplyDelete