from Deacon Henock Haile
አንድ አድርገን መስከረም 13 2007 ዓ.ም

በፈረንጆቹ አቆጣጠር በ1950 ዓ.ም. በካይሮ በሚገኝ አንድ ሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ አንድ አገልጋይ ቆመና ‹‹ለገጠር አገልግሎት መመዝገብ የምትፈልጉ ....›› የሚል አንድ ማስታወቂያ ተናገረ፡፡ የገጠር አገልግሎት ማለት የከተማ ሰንበት ትምህርት ቤት አገልጋዮች ወደ ገጠር መንደሮች እየሔዱ የሚያስተምሩበትና የሚያገለግሉበት የአገልግሎት መስክ ነበር፡፡ ይህ ማስታወቂያ ሲነገር በወቅቱ የሃይስኩል ተማሪ የነበረ አንድ የ14 ዓመት ልጅ ተመሥጦ ይሰማል፡፡ ይህ ልጅ የሰንበት ትምህርት ቤት የሕጻናት መምህራን ሆነው ከተመለመሉ ልጆች አንዱ ነበር፡፡ ስለዚህም ወደ ገጠር ሔዶ ለማገልገል ከሌሎች ጓደኞቹ ጋር ይመዘገባል፡፡
ጊዜው ሲደርስም እንደ ሐዋርያት ሁለት ሁለት እየሆኑ ወደ ገጠር ከሚዞሩት የሰንበት ተማሪዎች አንዱ ሆኖ ማገልገሉን ቀጠለ፡፡ በዚህም ወቅት የጀመረው ሌሎችን የማገልገል ፍላጎት በጣም በመጨመሩ የዩንቨርሲቲ ትምህርቱን አጠናቅቆ በህክምና እስከተመረቀበት ጊዜ ድረስም ይህን አገልግሎቱን አላቋረጠም፡፡ ትምህርቱን ሲጨርስ ግን የህክምና ሙያውን ተጠቅሞ አገልግሎቱን ማስፋት ተመኘ፡፡ ሌሎችን የማዳን ፍላጎቱን ለማርካት ግን የግብፅ ምድር አልበቃችውም፡፡ በአፍሪካ ሀገራትም ለማገልገል ቆርጦ ተነሣ፡፡ የመጀመሪያ ጉዞውንም ወደ ኢትዮጵያ አድርጎ በአሥመራና በደብረ ብርሃንና በአዲስ አበባ እስከ 1966 ድረስ አገለገለ፡፡ ከዚያም ወደ ግብፅ ተመልሶ መነኮሰ፡፡ ከምንኩስናው በኋላም የአገልግሎት ጉዞውን ቀጠለ፡፡ ከአስቄጥስ ገዳም ተነሥቶ ወደ ናይሮቢ ኬንያ ፣ ከናይሮቢ ወደ ዛምቢያው ሉሳካ ፣ ከሉሳካ ወደ ዚምባብዌው ሐራሬ ፣ ከሐራሬ ወደ ዛየር ኪንሻሳ ፣ ከኪንሻሳ ወደ ቦትስዋና ፣ ከቦትስዋና ወደ ማላዊ ሌሴቶ ከዚያም ወደ ሌሎች ሀገራት.... በአጠቃላይ ወደ 23 የአፍሪካ ሀገራት ተጓዘ፡፡ አብያተ ክርስቲያናትን ፣ ገዳማትን ፣ መንፈሳዊ ኮሌጆችን አቋቋመ፡፡ በየሀገራቱ ቋንቋዎች በመቶዎች የሚቆጠሩ መጻሕፍትን ተርጉሞ አስተማረ፡፡ በዐሥራ አራት ዓመቱ በልቡ የተጫረው የመንፈሳዊ አገልግሎት እሳት በብዙ ቋንቋዎች እና ባህሎች ውስጥ እየተቀጣጠለ ብዙ አፍሪካውያንን ወደ ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን እንዲገቡ አደረገ፡፡ ያ የካይሮ ሰንበት ትምህርት ቤት ትንሹ አገልጋይ በፎቶው ላይ የምትመለከቷቸው የዛሬው የየኮፕቲክ ቤተ ክርስቲያን የአፍሪካ ጉዳዮች ሊቀጳጳስ ብፁዕ አቡነ አንቶንዮስ ማርቆስ ናቸው፡፡



