Saturday, March 8, 2014

ፓትርያርኩ ‹‹ቤተ ክርስቲያን በዩኒቨርስቲ ምሩቃን አትመራም” ማለታቸው ቅሬታ ፈጠረ


  • ስለማኅበራት የሰጡትን አስተያየት መልሰው እንዲያጤኑት ተጠየቀ
  • ‹‹ማኅበራትበትኩረትሊመሩናጉዟቸውምእየተፈተሸሊስተካከልይገባል›› - መንግሥት
(አዲስ አድማስ የካቲት 29 2006 ዓ.ም)፡- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ‹‹ከዩኒቨርስቲ ተመርቀው ቤተ ክርስቲያንን እንምራ እያሉ ነው፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ ትውፊትና ሥርዓት አላት፤እንዲህ ማለት አይችሉም›› በማለት የሰጡትን አስተያየት መልሰው እንዲያጤኑት በንግግራቸው ቅር የተሰኙ የመንፈሳውያን ማኅበራት አገልጋዮች ጠየቁ፡፡

አገልጋዮቹ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፣ አቡነ ማትያስ ይሄን አስተያየት የሰነዘሩት በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት /ቤት የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ከኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር ጋር በመተባበር የካቲት 21 እና 22 ያዘጋጁት ሀገር አቀፍ የስብከተ ወንጌል የምክክር ጉባኤ በተካሔደበት ወቅት ነው፡፡

Thursday, March 6, 2014

አደናጋሪው የ‹‹መጋቢ ሐዲስ››ነት ጉዳይ

  • መጋቢ ሐዲስ ለመባል ምን ያስፈልጋልመጋቢ ሐዲስ የሚል መአረግ ለተሰጠው አገልጋይ ከእሱ ምን ይጠበቃል?
  • ቤተ ክርስትያን ለምን አይነት መምህራን መጋቢ ሐዲስ የሚል የመአረግ ስም ትሰጣለች ?


(አንድ አድርገን የካቲት 28 2006 ዓ.ም)፡- ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ሲሠራ የቅዱሳን መጻሕፍት ሃሳብን መነሻ አድርጎ የሚወጣው ሥርዓት ምን አይነት የሥጋ ወይም የነፍስ ትሩፋት እንደሚያሠራን ከየትኛው ፈተና እንደሚጠብቀን ወይም ለየትኛው የሰይጣን ወጥመድ በር እንደማይከፍት በማጥናት ይዘጋጃል፡፡ በነቢያትና በሐዋርያት የነበሩ የእግዚአብሔር ቅዱሳን የሠሯቸውን ሥርዓቶችን ያጸናል፡፡ ያሉና የነበሩ ሥርዓቶችንም ሸክም የሚሆንባቸውና ወደ ተሻለ መልአካዊ ሥርዓት እስኪደርሱ ድረስ ሊጨነቁ የሚችሉ አዲስ አማኞችን በክርስትና አምልኮ ውስጥ ተሳታፊ ለማድረግ የነበረውን ሥርዓት ተሻሽሎ እና ዘመኑን ዋጅቶ ለእነርሱ ሊሰራላቸው ይችላል፡፡ እነዚህ ሁሉ መንገዶች ግን እግዚአብሔር ወደሚወደው የቅዱሳን ኑሮ የምዕመናንን ሕይወት ማሳደግና ለመልካም ሕይወት ማዘጋጀት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ለ3ሺህ ዘመን ከቆየችበት የአምልኮ ሥርዓት አንፃር የተመሰከረላት እና የምዕመናንን ሕይወት በመጠበቅና በማሳደግ በመንከባከብ ጠብቃ እንድትኖርና ከብዙ የፈተና እሳቶች እንደ ወርቅ ነጥራ እንድትወጣ ሊቃውንቶቿ ያደረጉት አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነው፡፡ ቤተክርስቲያኒቱ ባስቀመጠችው የእውቀት ልኬት መሰረት ለመምህራኖቿ ለዘመናት ምዕመኑን እንዲያንጹ እና እንዲያገለግሉ የምትሰጣቸው የአገልግሎት ማዕረጎች ያሏት ሲሆን አሁን አሁን እነዚህ በአበው የቆዩት ሥርዓቶች ስልጣንና ፍቅረ ንዋይ ባወራቸው ሰዎችና የተሸከሙት የኃላፊነት ክብደት ምን ያህል መሆኑን ባልተገነዘቡ አንዳንድ አባቶች አማካኝነት በአንድም በሌላ መንገድ ማዕረጋቱ ሲመዘበሩ እየታዩ ይገኛሉ፡፡

Wednesday, March 5, 2014

ለክርስቲያን ጎሳው ማነው?



ዳንኤል አዲስ
(አንድ አድርገን የካቲት 26 2006 ዓ.ም)፡- ለክርስቲያን ጎሳው ማነው? ዘሩስ ከወዴት ነው? ወገንተኝነቱስ ለየትኛው ብሔር ነው? አለም በዲያቢሎስ ሃሳብ ታነክሳለች ፤ በክርስቶስ ሃሳብ ግን ትፀናለች አለም በዲያቢሎስ ወሬ ትከፈላለች  በክርስቶስ ግን አንድ ትሆናለች ዘርህ ማነው? ይሉኛል፡፡ እኔ ግን የክርስቲያን ዘሩ ምንድን ነው? እላቸዋለሁ፡፡ አማራ ነህ ? ይሉኛል አዋ አማራ ወገኔ ነው እላቸዋለሁ፡፡ ትግሬ ነህ? ይሉኛል አዋ ትግሬም ወገኔ ነው እላቸዋለሁ፡፡ ኦሮሞ ነህ? ይሉኛል አዋ ኦሮሞም ወገኔ ነው እላቸዋለሁ፡፡  ለትግሬ አድልቼ አማራን ጎድቼ ቢሆን ለአፍንጫዬ አድልቼ አይኔን እንደማጥፋት በቆጠርኩኝ ለአማራም አድልቼ ኦሮሞን ጎድቼ ቢሆን ለቀኝ እጄ አድልቼ ግራ እጄን እንደማስቆረጥ በቆጠርኩኝ፡፡ ነገር ግን እኔ ክርስቲያን ነኝ ክርስቲያንም ለመሆን ውዴታ አለኝ ክርስቶስንም ስለመምሰል ስራ አለብኝ እንግዲህ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ምናዊ ናቸው? እኔ ግን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ልጅ ነኝ ይህን እምነቴን የሚወስድብኝ አንዳች እንኳን ኃይል የለም ፡፡ ወይንስ አቡነ ሀብተ ማርያም ምናዊ ናቸው? እኔም የአቡነ ሀብተ ማርያም ልጅ ነኝ ይህን እምነቴን የሚቀማኝ አንዳች እንኳን ኃይል የለም ወይንስ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ምናዊ ናቸው? እኔም አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ልጅ ነኝ ይህን እምነቴንም የሚቀማኝ አንዳች እንኳን ኃይል የለም፡፡

Tuesday, March 4, 2014

የፓትርያርኩ የለውጥ ተግዳሮትና ተስፋ - በአንደኛ ዓመት በዓለ ሢመት ዋዜማ

  • የብልሹ አሠራርና ሙስናን ችግር በዐደባባይ የተናገሩ የመጀመሪያው ፓትርያርክ ናቸው
  • ፓትርያርኩ ጽኑ አቋም ስለሌላቸው ለጣልቃ ገብነት የተመቹ ኾነዋል
  • ጣልቃ ገብነቶችን መቋቋምና የቅ/ሲኖዶሱን የውሳኔ ልዕልና ማስከበር ይጠበቅባቸዋል
  • ፓትርያርኩ ዙሪያቸውን መፈተሽ አለባቸው
  • ብቃት ያለው የአማካሪ መዋቅር  ያስፈልጋቸዋል
(አዲስ አድማስ የካቲት 22 2006 ዓ.ም የካቲት 21 ቀን 2005 . ለስድስተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ምርጫ ከቀረቡት አምስት ዕጩዎች መካከል በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ አቡነ ማትያስ በከፍተኛ ድምፅ መመረጣቸው ተነገረ። ሊቀ ጳጳሱ በቤተ ክርስቲያኒቱ የፓትርያርኮች ምርጫ ታሪክ ከፍተኛውን የመራጮች ድምፅ በማግኘት አሸናፊ መኾናቸው በተገለጸበት ወቅት የብዙዎችን ትኩረት በሳበ ኹኔታ በመስቀላቸው ሲያማትቡ ታዩ።