ቅዱስ ጊዮርጊስ ብሩክታይትን ከድራጎን ያዳነበት ስፍራ ፤ ቤሩት
(አንድ አድርገን ጥር 17 2006 ዓ.ም)፡-
ከሃዲ ንጉስ ዱድያኖስ ግንድ አምጥተው ቅዱስ ጊዮርጊስን በግንዱ ላይ እንዲቸነክሩት አዘዘ ፤በላዩም ላይ ሰም አፍስሰው እሳት እንዲያነዱበት አደረገ ፤ ከዚህም በኃላ እንደመጭመቂያ ሆኖ ከተሰራ የስቃይ መሳሪያ ላይ አወጡት ፤ ሰውነቱን እንዲሰነጥቁት እንዲጨምቁት አዘዘ ፤ አንጀቱ ሁሉ ወጥቶ ከምድር ላይ እስኪዘረገፍ ድረስ እንዲሁ አደረጉበት ነፍሱ ከስጋው ተለየች ፤ የሰማእቱን ሰጋ አቃጠሉት ፈጩት አመድም ሆነ ፤ በቀፎ አድርገው ይድራስ ወደሚባል ተራራ ላይ በነፋስ ዘሩት “ደብረ ይድራስ” ማለት ምድረ በዳ የሆነ ቦታ ነው፡፡ ወታደሮቹ የታዘዙትን ፈጽመው ተመለሱ። ያንጊዜም መብረቅ ነጎድጓድ ታላቅ ንውጽውጽታ ሆነ ፤ ምድርም ከመሰረቷ እስክትናወጽ ድረስ ከሰማይ ድምጽ ተሰማ ጌታችን መድሐኒታችን እየሱስ ክርስቶስ መላእክትን አስከትሎ በብሩ ደመና ወረደ በተራራውም ላይ ተቀመጠ ፤ አራቱን የምድር ነፋሳት የሰማእቱን ስጋ እንዲሰበሰቡ አዘዛቸው ከሞትም አስነሳው ኃይሉን አሳደረበት ባርኮትም ወደ ሰማይ አረገ ፤ ከዚህ በኃላ ቅዱስ ጊዮርጊስ እየሮጠ ወታደሮቹን ተከተላቸው “ወንድሞቼ ቆዩኝ ከእናንተ ጋር ልሂድ” እያለ ተጣራ ፤ የእነዚህ የወታደሮች ቁጥራቸው አራት ነበረ ስማቸው ህልቶን ፤ አግሎሲስ ፤ ሶሪስና አስፎሪስ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ይህንን ታላቅ ተአምራት አይተው አምነዋል፡፡ በኋላም በሰማእትነት አልፈዋል፡፡ ይህ የሆነው ጥር 18 ቀን ነው ይህንንም ቀን " ዝርዎተ አጽሙ " ስትል ቤተ ክርስቲያን ሰማእቱን አዘክራ ትውላለች፡፡ በስሙ በታነጹለት አብያተ ክርስቲያናት በሙሉ ታቦተ ህጉ ውጥቶ በደማቁ ተከብሮ ይውላል። ደብረ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያንንን የተከሉት ደጉ ንጉስ እምዬ ምኒሊክ ሲሆኑ የዚህን ታላቅ ደብር መሰረቱን ሲጥሉ የቅዱስ ጊዮርጊስ መቃብር ከሚገኝበት ቦታ አፈሩን በመርከብ አጓጉዘው በበቅሎ በፈረስ አስጭነው የቤተክርስቲያኑን መሰረት አድርገውታል፡፡

